ቻይና፣ ሩሲያና ሌሎች የዓለማችን መሪዎች ማዱሮ ስለመያዛቸው ምን አሉ?

ቬኒዙዌላ ላይ ድንገተኛ የኮማንዶ ጥቃት በመፈጸም አገሪቱ መሪ በአሜሪካ እጅ መግባታቸውን በተመለከተ ፕሬዝንት ትራምፕ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “አስተማማኝ፣ ተገቢ እና ሕጋዊ ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ ቬንዙዌላን አሜሪካ ታስተዳድራለች” ሲሉ በኩራት ተናግረዋል። ማዱሮ መያዛቸውን ተከትሎ የዓለማችን መሪዎች የተደበላለቀ ምላሽ ሰጥተዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ጂቡቲ የሶማሊላንድ ዲፕሎማቲክ ቢሮን ዘግታ ዲፕሎማቶቿን ጠራች

    እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠቷን ተከትሎ ከሐርጌሳ ጋር ውጥረት ውስጥ የገባችው ጅቡቲ፤ የሶማሊላንድ ዲፕሎማቲክ ቢሮን እንደዘጋች እና ዲፕሎማቶቿን ከሀርጌሳ መልሳ እንደጠራች አንድ የአገሪቱ መንግሥት ባለስልጣን ለቢቢሲ አረጋገጡ።

    ማንነታቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የሱማሊላንድ ባለስልጣን በበኩላቸው ሐርጌሳም በተመሳሳይ በጅቡቲ የሚገኙ ዲፕሎማቶቿን ለምክክር እንደጠራች ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    የአሁኑ ሁኔታ እስራኤል ለሶማሊላንድን የአገርነት እውቅና ከሰጠችበት ጊዜ አንስቶ የሁለቱ ተጎራባቾች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እጅግ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ መውረዱን ያሳያል።

    ይህ ዲፕሎማሲያዊ መቃቃር በተለይም ለዓለም አቀፍ ጉዞ የጂቡቲ ፓስፖርትን በሚጠቀሙ የሶማሊላንድ ባለሥልጣናት እና ታዋቂ ግለሰቦች፣ በተለይም በሶማሊላንድ የንግድ ማህበረሰብ አባላት ጉዞ ተጽዕኖ እንደሚኖረው ይጠበቃል።

    እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠቷን በፅኑ ከተቃወሙ የሶማሊያ ጎረቤቶች መካከል ጂቡቲ አንዷ ናት።

  2. “ሶማሊላንድ ዕውቅና ያገኘችው ሦስት ወሳኝ ነጥቦች ላይ ተስማምታ ነው” የሶማሊያ ፕሬዝዳንት

    ሶማሊላንድ ከእስራኤል የአገርነት ዕውቅናን ያገኘችው በምላሹ ሦስት ዋነኛ ስምምነቶችን ተግባራዊ ለማድረግ ተስማምታ ነው ሲሉ የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐሙድ ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ ለአል ጀዚራ የአረብኛ ቴሌቪዥን በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ እንደተናገሩት “ባለን መረጃ መሠረት ሶማሊላንድ ሦስት ዋነኛ እርምጃዎችን ለመውሰድ ተስማምታለች” ብለዋል።

    የመጀመሪያው በማለት የጠቀሱት በሶማሊላንድ ውስጥ ፍልስጤማውያንን ማስፈር፣ ሁለተኛው በኤደን ባሕረ ሰላጤ ዳርቻ ለእስራኤል የወታደራዊ ሰፈር መፍቀድ እና ሦስተኛው ደግሞ ሶማሊላንድ በአብርሃም ስምምነት ውስጥ እንድትታቀፍ ማድረግ ነው።

    ፕሬዝዳንት ሐሰን የእስራኤል ፍላጎቶች ያሏቸውን ሦስት ሁኔታዎችን “ሶማሊላንድ ተቀብላለች” በማለት፤ እነዚህ ተግባራዊ የሚሆኑ ከሆነ “በዓለም ላይ አደገኛ ሁኔታ ይፈጠራል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    በጋዛው ጦርነት ወቅት እስራኤል ፍልስጤማውያንን ከሰርጡ በማስወጣት በሌላ አገር የማስፈር ዕቅድ አላት የሚሉ ዘገባዎች ሲወጡ የነበረ ሲሆን፣ የጦር ሰፈር የምትመሠርት ከሆነ በየመን ያሉትን ባላንጣዎቿ የሁቲ ታጣቂዎችን ለማጥቃት እና የኢራንን እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር ሊጠቅማት ይችላል።

    የአብርሃም ስምምነት ደግሞ የአረብ አገራት የእስራኤልን ኅልውና እንዲቀበሉ እና ግንኙነታቸውን ለማሻሻል እና ለማጠናከር የታለመ የትበብር ስምምነት ነው።

    የአብርሃም ስምምነት በአሜሪካ በኩል ከፍተኛ ድጋፍ ያለው ሲሆን፣ አስካሁንም እስራኤል ከተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣ ከባህሬን፣ ከሱዳን እና ከሞሮኮ ጋር ተፈራርማለች።

  3. የምዕራብ አፍሪካ አገራት ለትራምፕ ውሳኔ አጸፋ በአሜሪካዊያን ላይ የጉዞ ዕገዳ ጣሉ

    አሜሪካ በዜጎቻቸው ላይ የጣለችውን ዕቀባ ተከትሎ ማሊ እና ቡርኪና ፋሶ አሜሪካውያን ወደ አገራቸው እንዳይገቡ እገዳ ጣሉ።

    አገራቱ በአሜሪካዊያን ላይ ዕገዳውን ያሳለፉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቅርቡ ሙሉ የጉዞ ዕገዳ ከጣሉባቸው አገራት መካከል በመሆናቸው በአጸፋው በወሰዱት እርምጃ ነው።

    ማሊ እና ቡርኪና ፋሶ በተናጠል ባወጡት መግለጫ ዜጎቸቻው ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ለተጣለባቸው ዕገዳ አሜሪካዊያንም በተመሳሳይ ወደ ምዕራብ አፍሪካ አገራቱ እንዳይገቡ ክልከላ ተግባራዊ አድርገዋል።

    የቡርኪና ፋሶ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እርምጃውን “የአጸፋ መርኅ” ሲሉት፣ የማሊ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ደግሞ “የጋራ መከባበር እና የሉዓላዊ አቻነት” ያስፈልጋል ብሏል።

    የማሊ እና የቡርኪና ፋሶ ውሳኔ ይፋ የሆነው ጉረቤታቸው ኒጀር ተመሳሳይ የጉዞ ዕገዳ በአሜሪካዊያን ላይ ከጣለች ከቀናት በሏላ ነው።

    ሦስቱ የምዕራብ አፍሪካ አገራት የሚመሩት በመፈንቅለ መንግሥት ሥልጣን በያዙ ወታደራዊ መኮንኖች ነው።

    አገራቱ ከምዕራባውያን እና ከምዕራብ አፍሪካ አገራት ጋር ያላቸው ግንኙነት መሻከሩን ተከትሎ ፊታቸውን ወደ ሩሲያ አዙረዋል።

    ከጥቂት ሳምንታት በፊት የአሜሪካ መንግሥት ማሊ፣ ቡርኪና ፋሶ እና ኒጀርን ጨምሮ በደቡብ ሱዳን፣ በሶሪያ እና በፍልስጤም ዜጎች ላይ ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ሙሉ ዕገዳ መጣሉ ይታወሳል።

    ይህ የአሜሪካ የእገዳ ውሳኔ ከ2026 የመጀመሪያ ቀን አንስቶ ተግባራዊ የሚሆን ሲሆን፣ የአፍሪካ አገራቱ በአሜሪካውያን ላይ ተመሳሳይ ክልከላ የጣሉት ውሳኔው ተግባራዊ ሊሆን አንድ ቀን ሲቀረው ነው።

  4. አዲሱን ዓመት ከሁሉም ቀድማ የምትቀበለው ሀገር የትኛዋ ናት?

    በዓለማችን ከሁሉም ቀድሞ በጎርጎሪዮሳውያን አቆጣጠር 2026ን የተቀበለችው ስፍራ ኪሪባቲ ትባላለች።

    ክሪስማስ ደሴት በተሰኘ ቅፅል ስሟ የምትታወቀው የፓሲፊኳ ኪሪባቲ ክፍል ናት። የሕዝብ ቁጥሯ 7 ሺህ ገደማ ሲሆን ውብ የባሕር ጠረፎቿ የቱሪስት ማዕከል ናቸው።

    ኪሪቲባቲ ግሪንዊች ሜን ታይም በተሰኘው የሰዓት አቆጣጠር +14 ላይ ትገኛለች። ይህ ማለት ከኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር 11 ሰዓታት ትቀድማለች ማለት ነው።

    ኒው ዚላንድ ከቀሪው ክፍለ ዓለም ቀድማ አዲሱን ዓመት የተቀበለች ሌላኛዋ ሀገር ናት። በዋና ከተማዋ ኦክላንድ አዲሱ የአውሮፓውያን ዓመት 2026 በድምቀት እየተከበረ ይገኛል።

    በደሴቲቱ ፊጂ አቆጣጠር አዲሱ ዓመት ተጀምሯል። የፊጂ ነዋሪዎች እኩለ ሌሊትን ጠብቀው 2026ን ተቀብለዋል።

    ፊጂን ጨምሮ ሌሎች የፓሲፊክ ሀገራት እንዲሁም አንዳንድ የሩሲያ ክፍሎች አዲሱን ዓመት ጀምረዋል።

    አውስትራሊያ አዲሱን ዓመት በድምቀት ተቀብላለች። ሲድኒ በችርት መብራት ስትፈካ ሌሎችም የአውስትራሊያ ከተሞች አዲሱን ዓመት እየተቀበሉ ይገኛሉ።

    አውስትራሊያ ከጥቂት ሳምንታት በፊት በቦንዳይ የባሕር ዳርቻ አቅራቢያ የደረሰውን የሽብር ጥቃት ተከትሎ በርካታ ፖሊሶችን አሰማርታለች።

    የአውሮፓውኑ አዲስ ዓመት 2026 በኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ታኅሣሥ 22 ከለሊቱ 6 ሰዓት ይገባል።

  5. "የባሕር በር ማግኘት ትውልድ የሚሻገር ጥያቄ ነው" የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ

    የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጤሞቲዮስ ሀገራቸው የባሕር በር ለማግኘት የምታደርገው ጥረት ከፖለቲካ አቋም የዘለለ ትልቅ ጉዳይ መሆኑን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተናገሩ።

    ሚኒስትሩ ማክሰኞ ታኅሣሥ 21/2018 ከሕዝብ እንደራሴዎች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሲሰጡ ኢትዮጵያ የባሕር በር ለማግኘት የምታደርገው ጥረት "ትኩረቱን ወደ አፈፃፀም አዙሯል" ብለዋል።

    የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ "ትውልድ የሚሻገር ለየትኛው መንግሥት አሊያም የፖለቲካ ፓርቲ ብሔራዊ ጥያቄ ነው" ያሉት ሚኒስትሩ ጉዳዩን "አበረታች ምልክቶች" እያሳዩ መሆኑን ጠቅሰዋል።

    ኃያላን የሚባሉ ሀገራት በቀጣናው ያላቸውን እንቅስቃሴ ከግምት በማስገባት ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እየተመራች ነውም ብለዋል።

    ሚኒስትሩ በቅርቡ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን እውቅና ተከትሎ የኢትዮጵያ ምላሽ ምን ይሆን? እንዲሁም ከሶማሊላንድ ጋር የተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት ከየት ደረሰ? ተብለው ቢጠየቁም ምላሽ ሳይሰጡ እንደቀሩ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ከሁለት ዓመታት በፊት የቀድሞው የሶማሊላንድ ፕሬዝደንት ሙሴ ቢሂ እና የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ኢትዮጵያ የባሕር በር የምታገኝበትን የመግባቢያ ሰነድ እንደተፈራረሙ ይታወሳል። በሰነዱ መሠረት ኢትዮጵያ ለሶማሊላንድ እውቅና እንደምትሰጥ ሙሴ ቢሂ ተናግረው ነበር።

    እስራኤል ለሶማሊላንድ የሀገርነት እውቅና መስጠቷን ተከትሎ ግብፅ፣ ጂቡቲ እና ኤርትራ እንዲሁም ሱዳን የቴል-አቪቭን ድርጊት በፅኑ ቢቃወሙም ኢትዮጵያ ዝምታን መርጣለች።

  6. ኢትዮጵያ ዝምታን የመረጠችበት የሶማሊላንድ ዕውቅና

    ባለፈው ሳምንት ከእስራኤል የአገርነት ዕውቅናን ያገኘችው ሶማሊላንድን በተመለከተ ኢትዮጵያ አስካሁን አቋሟን ሳታሳውቅ ዝምታን መርጣለች።

    ኢትዮጵያ የቅርብ ግንኙነት ካላት እና ከሁለት ዓመት በፊት የባሕር በር የማግኛ የመግባቢያ ሰነድ የተፈራረመቻት የሶማሊላንድ የዕውቅና ጉዳይ በተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ሳይቀር መነጋገሪያ ሆኗል።

    ነገር ግን ኢትዮጵያ በዚህ ጉዳይ ላይ ያላትን ተቃውሞም ሆነ ድጋፍን ሳትገልጽ ከመቆየቷ በተጨማሪ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ለዜናው ሽፋን ሳይሰጡ ቀናት ተቆጥረዋል።

    የቢቢሲ የመገናኛ ብዙኃን መከታተያ ክፍል ቢቢሲ ሞኒተሪንግ እንዳመለከተው የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት፣ የመንግሥት እና ለመንግሥት ቅርበት ያላቸው መገናኛ ብዙኃን በጉዳዩ ላይ ዝምታን መርጠዋል።

    ቢቢሲ ሞኒተሪንግ እንደተከታተለው የመንግሥት ጣቢያ የሆነው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና ለመንግሥት ቅርብ የሆነው ፋና እስራኤል የመጀመሪያ አገር በመሆን ለሶማሊላንድ የሰጠችውን ዕውቅና ሽፋን አልሰጡትም።

    በተጨማሪም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጤሞቲዮስ (ዶ/ር) ማክሰኞ ዕለት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው የነበረ ቢሆንም ስለሶማሊላንድ ጉዳይ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሳይሰጡ ቀርተዋል።

    የእስራኤልን ዕውቅና ተከትሎ የሶማሊያ ፕሬዝዳንት እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በዙሪያቸው ላሉ አገራት መሪዎች እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስልክ በመደወል ድጋፋቸውን እንዲሰጧቸው እና የእስራኤልን እርምጃ እንዲያወግዙ ውይይት ማድረጋቸውን በገጻቸው ላይ አመልክተዋል።

    ባለሥልጣናቱ የሶማሊያ ዋነኛ ተጎራባች እና በአካባቢው ወሳኝ አገር ከሆነችው ኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ጋር ውይይት ስለማድረጋቸው አስካሁን ያሉት ነገር የለም።

    ግብፅ፣ ሱዳን፣ ጂቡቲ እና ኤርትራ የእስራኤልን እውቅና በይፋ የተቃወሙ ሀገራት ሲሆኑ ኢትዮጵያን ጨምሮ የኬንያ እና የኡጋንዳ መንግታት አቋመቸውን እስካሁን አላሳወቁም።

    ነገር ግን እስራኤል ለሶማሊላንድ የአገርነት ዕውቅናን ከመስጠቷ ከቀናት በፊት የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሼክ ሐሰን ሞሐሙድ በአዲስ አበባ የአንድ ቀን ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል።

    ኢትዮጵያ በ2016 ዓ.ም. ነጻ አገርነቷን ካወጀችው ሶማሊላንድ ጋር የባሕር ጠረፍ ለማግኘት በምላሹም ዕውቅና ለመስጠት የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርማ እንደነበር ይታወሳል።

    በዚህም ምክንያት ከሶማሊያ ጋር ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ ገብታ በቱርክ አሸማጋይነት ስምምነት ተደርሷል።

    ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ ቱርክ አንካራ ላይ የተፈራረሙት ስምምነት ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር በፈረመችው ሰነድ ምክንያት በአፍሪካ ቀንድ ተፈጥሮ የነበረውን የዲፕሎማሲ እና የደኅንነት ውጥረት ያረገበ ነው።

    በአንድ ዓመት ውስጥ ተግባራዊ ይሆናል የተባለው አስከ 20 ኪሎ ሜትር የሚደረስ የባሕር ጠረፍ ለኢትዮጵያ ያስገኛል የተባለው ከሶማሊላንድ ጋር የተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት ጉዳይም መቋጫው ዝምታ ሆኖ ቆይቷል።

  7. በምሥራቅ ወለጋ የተፈጸመ የ19 ሰዎች ግድያ እና በስጋት ውስጥ ያሉት ነዋሪዎች

    በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ ዞን ጊዳ አያና ወረዳ "በኦሮሚያ ልዩ ኃይል" ተፈጽሟል በተባለ ጥቃት 19 ሰዎች ሲገደሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ቤቶች ደግሞ መቃጠላቸውን እና መዘረፋቸውን ነዋሪዎች ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ተቃዋሚዎቹ እናት ፓርቲ እና ኢህአፓ ጥቃቱ "በመንግሥት መዋቅር የተፈጸመ" መሆኑን በመግለጽ ሲያወግዙት የክልሉ እና የአካባቢው ባለሥልጣናት አስካሁን ምንም ያሉት ነገር የለም።

    በወረዳው የአማራ ተወላጆች ይኖሩበታል በተባለው ጠጋ ጂጊ (ሻሾ በር) አነስተኛ ከተማ ታኅሣሥ 14/2018 ዓ.ም. አንድ መነኩሴን ጨምሮ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች በስለት እና በጥይት "በአሰቃቂ ሁኔታ" ተደብድበው መገደላቸውን ቢቢሲ ያነጋገራቸው አምስት የዐይን እማኞች እና የሟች ቤተሰቦች አስታውቀዋል።በምሥራቅ ወለጋ የተፈጸመ የ19 ሰዎች ግድያ እና በስጋት ውስጥ ያሉት ነዋሪዎች

  8. እስራኤል በጋዛ እና ዌስትባንክ የሚንቀሳቀሱ ዓለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅቶችን ፈቃድ አገደች

    እስራኤል አዲስ ያወጣችውን ሕግ አላሟሉም ያለቻቸውን በጋዛ እና በወረራ በያዘችው ዌስት ባንክ የሚሰሩ 37 የረድኤት ድርጅቶችን ፈቃድ ልትሰርዝ ነው።

    እንደ አክሽን ኤድ፣ ዓለም አቀፉ የነፍስ አድን ድርጅት እና የኖርዌይ የስደተኞች ድርጅት የመሳሰሉ ታዋቂ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ከአውሮፓውያኑ አዲስ ዓመት የመጀመሪያ ቀን ጀምሮ ፈቃዳቸውን ከሚነጠቁት ውስጥ ናቸው።

    ይህንን ውሳኔ ተከትሎ ድርጅቶቹ ሥራቸውን በ60 ቀናት ውስጥ ያቆማሉ ተብሏል። ተጨማሪ ለማንበብ እስራኤል 37 ዓለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶችን ከጋዛ ልታባርር ነው

  9. አቶ ታዬ ደንደአ "እጃቸው በካቴና እንዲታሰር ባለመፍቀዳቸው" ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀሩ

    የቀድሞው የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ እና የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አባል አቶ ታዬ ደንደአ እጃቸው ላይ ካቴና ለማስገባት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው በፍርድ ቤት ቀጠሯቸው ላይ ሳይገኙ ቀሩ።

    አቶ ታዬ ደንደአ ረቡዕ ታኅሣሥ 22/2018 ዓ.ም. ልደታ በሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የቀረቡባቸውን ሦስት ክሶች ለማየት ቀጠሮ ተይዞላቸው ነበር።

    ፍርድ ቤቱ ቀጠሮ ይዞ የነበረው የዐቃቤ ሕግን ክስ እና የተከሳሹን ተቃውሞ ለመስማት ነበር።

    ይሁን እንጂ የአቶ ታዬ ደንደአ ጠበቆች በችሎቱ ላይ ቢገኙም እርሳቸው ግን ሳይገኙ ቀርተዋል።

    የማረሚያ ቤቱ የፖሊስ መኮንኖች ለችሎቱ አቶ ታዬ ደንደአ እጃቸው ላይ 'ሰንሰለት ለማድረግ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው' ፍርድ ቤት እንደማያቀርቡ ተናግረዋል።

    አቶ ታዬ ቀደም ሲል በአለርጂ ምክንያት ሰንሰለት ማድረግ እንደማይፈልጉ ተናግረው ነበር።

    ፍርድ ቤቱ በበኩሉ የማረሚያ ቤት ፖሊስ ተከሳሹን በ'ጥቃቅን ምክንያቶች' ወደ ፍርድ ቤት አለማቅረቡ ስህተት መሆኑን ተናግሯል።

    ችሎቱ አቶ ታዬ ደንደአ ሐሙስ ታኅሣሥ 23/2018 ዓ.ም. ችሎት ፊት እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

    አቶ ታዬ ከቀረቡባቸው ሦስት ክሶች በሁለቱ ነጻ ሲባሉ የጦር መሣሪያ ሕግን በመተላለፍ በቀረበባቸው ክስ ግን ጥፋተኛ ተብለው የሰባት ዓመት ከሁለት ወር እስር ተፈርዶባቸዋል።

    አቶ ታዬ ነጻ የተባሉባቸው ክሶች "ከጠላት ጋር ማበር" አና የአገር መከላከያ ሠራዊትን ለመምታት "ዝግጅት አድርገዋል" የሚሉት ሁለት ከባድ ክሶች ናቸው።

  10. በሶማሊያ የተለያዩ ከተማዎች የተቃውሞ ሠልፎች ተካሄዱ

    ማክሰኞ ታኅሣሥ 21/2018 ዓ.ም. እስራኤል ሶማሊላንድን እንደ ሉዓላዊ አገር እውቅና መስጠቷን በመቃወም በሶማሊያ በተለያዩ ከተሞች ተቃውሞዎች መካሄዳቸውን የሶማሊያ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    በዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ፣ በጋክኮል ከተማ፣ በአዳዶ፣ በጉሪኤል ከተሞች እና በሰሜን ምሥራቅ ላስ አኖድ ከተማ ሶማሊላንድ ያገኘችውን ዕውቅና የሚቃወሙ ሠልፎች ተካሂደዋል።

    ተቃዋሚዎቹ የሶማሊያን ብሔራዊ መዝሙር እየዘመሩ፣ የሶማሊያን ሰንደቅ ዓላማ እያወለበለቡ እና "ጥቃት" ያሉትን የእስራኤልን ውሳኔ እያወገዙ ታይተዋል።

    በጉሪኤል ተቃዋሚዎች የእስራኤል ሰንደቅ ዓላማ እንዲሁም የጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ፎቶ ላይ በመቆም ተቃውሟቸውን ገልጸዋል።

    ተማሪዎች እንዲሁም የሶማሊያ ወታደሮች በተቃውሞው ሠልፉ ላይ ተሳትፈዋል።

    "እኛ ድጋፍ እንድናደርግ እና ሃይማኖታችንን ለጽዮናውያን እንድንተው አንገደድም" ሲሉ በላስ አኖድ ለተቃውሞ አደባባይ የወጡ ሠልፈኞች ለመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    በሞቃዲሾ አደባባይ የወጡ የተወሰኑ ተቃዋሚዎች የፍልስጤምን ባንዲራ ይዘው ነበር።

    "አይሁዶች ለፍልስጤማውያን ወንድሞቻችን ከሚያደርጉት ነገር የተሻለ አያደርጉም" ሲል በሞቃዲሾ የተቃውሞ ሠልፍ ላይ የተሳተፈ አንድ ተቃዋሚ አስተያየቱን ሰጥቷል።

    ሶማሊያውያን ለተቃውሞ አደባባይ የወጡት እስራኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና መስጠቷ ዓለም አቀፍ ውግዘት ካስከተለ በኋላ ነው።

  11. ኔታንያሁ ለሶማሊላንድ ዕውቅና የተሰጠው በአብርሃም ስምምነት ለመሳተፍ በመፈለጓ ነው አሉ

    ኔታንያሁ ለሶማሊላንድ ዕውቅና የሰጡት በአብርሃም ስምምነት ለመሳተፍ በመፈለጓ፣ ዲሞክራሲያዊ አገር በመሆኗ እና ከእስራኤል ጋር ሰላም ለመፍጠር ፍላጎት ስላላት መሆኑን ተናገሩ።

    ኔታንያሁ አሜሪካ ውስጥ ኒውስማክስ ከተባለ መገናኛ ብዙኃን ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ወቅት ለሶማሊላንድ የሰጡት ዕውቅና በአብርሃም ስምምነት መሠረት “ለዘብተኛ እና ዲሞክራሲያዊ ሙስሊም አገር” ለመደገፍ ባላቸው ውሳኔ የተነሳ መሆኑን ገልጸዋል።

    ኔታንያሁ በሶማሊላንድ ያለው የፖለቲካ ሥርዓት በቀሪው ሶማሊያ ከሚታየው በእጅጉ የተለየ መሆኑን አብራርተዋል።

    ይህንንም ሲገልጹ በቀሪው የሶማሊያ ግዛት ያልተረጋጋ እና በአሸባሪዎች የተወረረ ነው ብለዋል።

    ኔታንያሁ ለሶማሊላንድ ዕውቅና እንዲሰጡ ያደረጋቸውን ሌላ ምክንያት ሲያስረዱ “ሶማሊላንድ ስድስት ሚሊዮን ሕዘብ ያላት አገር ናት፤ ለዘብተኛ ሙስሊሞች ይኖሩባታል። የአብርሃም ስምምነትን መቀላቀል ይፈልጋሉ። ይህ ጥሩ ይመስለኛል። ዲሞክራሲያዊ ናቸው፤ ምርጫም ያካሄዳሉ” ብለዋል።

    "ቀሪው የሶማሊያ ክፍል ግን አሸባሪው አልሸባብ አለ፤ እውነተኛ ምርጫ ለመጨረሻ ጊዜ መቼ እንዳካሄዱ አላውቅም። ምናልባት አስርት ዓመታት ይሆናል፤ በርካታ አሸባሪዎች በዚያ አሉ።"

    እስራኤል ላለፉት 34 ዓመታት እንደ ሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና ለማግኘት ስትጥር ለነበረችው ሶማሊላንድ ባለፈው ሳምንት ዕውቅና ሰጥታለች።

    ይህ ግን ከበርካታ የዓለም አገራት፣ ከአፍሪካ ኅብረት፣ ከአውሮፓ ኅብረት እንዲሁም ከአረብ አገራት ተቃውሞ ገጥሞታል።

    ኔታንያሁ ከኒውስማክስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ወቅት የተለያዩ ጉዳዮችን በማንሳት አብራርተዋል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ እርሳቸው እና ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተመሳሳይ ራዕይ እንዳላቸው የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ "ብዙ ነገር አሳክተናል" ብለዋል።

    ኔታንያሁ ከትራምፕ ጋር ለሐማስ ትጥቁን እንዲፈታ እና ጦርነቱን ለማስቆም በስምምነቱ መሠረት የተጣለበትን ግዴታ እንዲወጣ የ60 ቀናት የጊዜ ገደብ ለመስጠት መስማማታቸውንም በቃለምልልሱ ወቅት ተናግረዋል።።

  12. ቱርክ ከሶማሊያ የባሕር ዳርቻ ነዳጅ ለማውጣት ቁፋሮ ልትጀምር ነው

    ቱርክ በአዲሱ የአውሮፓውያን ዓመት በሶማሊያ የባሕር ክልል ውስጥ ነዳጅ ለማውጣት ቁፋሮ እንደምትጀምር ፕሬዝዳንቷ ረሲፕ ታይብ ኤርዶዋን ተናገሩ።

    ኤርዶዋን ይህንን የተናገሩት እስራኤል ለሶማሊላንድ የአገርነት ዕውቅና መስጠቷን ተከትሎ ድጋፍ ለማሰባሰብ ወደ ተለያዩ አገራት እያቀኑ ያሉት የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሼክ ሐሰን ሞሐመድ በተገኙበት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው።

    ከአንድ ዓመት በፊት በሶማሊያ እና በቱርክ መካከል የተደረሰውን ዘርፈ ብዙ የትብብር ስምምነት ተከትሎ ቱርክ ግዙፍ ነዳጅ አሳሽ መርከቦችን በሶማሊያ የባሕር ክልል ውስጥ አሰማርታ ፍለጋ ስታካሂድ ቆይታለች።

    የቱርክ ፕሬዝዳንት ኢስታምቡል ውስጥ በተካሄደው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ላለፉት ዘጠኝ ወራት የተካሄደው የነዳጅ አሰሳ ተጠናቅቆ በአዲሱ የአውሮፓውያን ዓመት ነዳጅ ለማውጣት ቁፋሮ ይጀመራል።

    በሕንድ ውቅያኖስ ላይ በሚገኘው የሶማሊያ የባሕር ጠረፍ ላይ ሰፊ ቦታን የቱርክ ነዳጅ ፈላጊ አሳሾች ፍለጋ ማካሄዳቸውን የጠቀሱት ኤርዶዋን "ይህ ዓይነቱ ሥራ ለቱርክ አዲስ ነው" ሲሉም ተናግረዋል።

    የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ነዳጅ የማውጣት ቁፋሮው "በቅርቡ" ይጀመራል ሲሉ ኤርዶዋን ደግሞ "በአዲሱ ዓመት" እንደሚጀመር አመልክተዋል።

    ለዚህም የቱርክ ተጨማሪ የነዳጅ መቆፈሪያ መርከቦችን ወደ አካባቢው እንደሚሰማሩ የቱርክ ፕሬዝዳንት ገልጸዋል።

  13. በአውሮፓ በኤሌትሪክ መቋረጥ ምክንያት በሺህዎች የሚቆጠሩ የአዲስ ዓመት መንገደኞች ጉዟቸው ተስተጓጎለ

    የተለያዩ የአውሮፓ ከተሞችን የሚገናኘው ከ25000 በላይ የዩሮስታር የባቡር መንገደኞች በኤሌትሪክ ኃይል መቋረጥ ምክንያት ከጉዟቸው ተስተጓጎሉ።

    በለንደን እና ፓሪስ፣ በብራስልስ እና አምስተርዳም መካከል የሚሄደው የባቡር መስመር ለሰዓታት ተቋርጦ እንደነበር ተዘግቧል።

    በአውሮፓውያኑ አዲስ ዓመት ዋዜማ የዩሮስታር መንገደኞች ለሁለተኛ ቀን በባቡር መተላለፊያ ዋሻ ውስጥ ባጋጠመ የኤሌትሪክ ኃይል መቋረጥ ምክንያት ጉዟቸው መስተጓጎሉ ተገልጿል።

    አንዳንድ መንገደኞች የምሽት የባቡር አገልግሎት ለመጠቀም ወደ ባቡር ጣቢያው ቢመጡም በተፈጠረው መዘግየት የተነሳ ለስድስት ሰዓታት ጉዟቸው መስተጓጎሉን ገልጸዋል።

    ዩሮስታር ጉዞውን ረቡዕ ዕለት እንደሚቀጥል አስታውቆ ነገር ግን የሚሰረዙ እና የሚዘገዩ የጉዞ መስመሮች መኖራቸውን አስታውቋል።

    የጉዞ መስተጓጎሉን የፈጠሩት ለባቡር መንገዱ ኃይል የሚያቀርበው መስመር ችግር ስለገጠመው እና ተበላሽቶ በቆመ ባቡር ምክንያት መሆናቸውን ተገልጿል።

    ከለንደን ወደ ፓሪስ እንዲሁም ከአምስተርዳም ወደ ብራስልስ የሚደረጉ ሁሉም የባቡር ጉዞዎች ተሰርዘዋል።

    የተወሰኑ ዩሮስታር አገልግሎቶች ማክሰኞ ምሽት የቀጠሉ ሲሆን መዘግየቶች አሁንም እንደቀጠሉ ናቸው።

  14. የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ኃይሏን ከየመን እንደምትወጣ አስታወቀች

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ሳዑዲ አረቢያ በየመን ተገንጣይ ቡድን በተያዘ ወደብ ላይ ጥቃት መፈፀሟን ተከትሎ አገሪቱን ለቅቃ እንደምትወጣ አስታወቀች።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የየመን ፕሬዝዳንታዊ ምክር ቤት ሠራዊቷን በ24 ሰዓታት ውስጥ እንድታስወጣ ያቀረበውን እና ሳዑዲ አረቢያ የመደገፈችውን ይህንን ውሳኔ በየመን የቀራትን ኃይል እንደምታስወጣ ተናግራለች።

    ኤምሬትስ ይህን ያለችው በሳዑዲ የሚመራው ጥምር ጦር አቡ ዳቢ በምትደግፈው ተገንጣይ ቡድን የመሣሪያ ጭነት ላይ ሙካላ በተባለ ወደብ የአየር ጥቃት ከፈፀመ በኋላ ነው።

    አረብ ኤምሬትስ ጭነቱ የመሣሪያ መሆኑን ያስተባበለች ሲሆን፤ በሳዑዲ ክስ “ጥልቅ ሐዘን” እንደተሰማት ገልፃለች።

    ሳዑዲ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ባለፈው አስር ዓመት በኢራን የሚደገፈውን የየመን ሁቲዎች ቡድንን በመዋጋት አጋር ነበሩ።

    ይሁን እንጂ አገራቱ በሚደግፏቸው የየመን ተፎካካሪ ቡድኖች ምክንያት ልዩነታቸው እየሰፋ ነው።

  15. ቱርክ በአንድ ቀን ከ350 በላይ ተጠርጣሪ የአይኤስ አባላትን ያዘች

    የቱርክ ፖሊስ በመላው አገሪቱ ባካሄደው ዘመቻ ከ350 በላይ ተጠርጣሪ የአይኤስ ቡድን አባላትን በቁጥጥር ሥር አዋለ።

    ማክሰኞ ጠዋት በ21 የአገሪቱ ግዛቶች ውስጥ በተካሄደ የተቀናጀ አሰሳ 357 ተጠርጣሪዎች መያዛቸውን የቱርክ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ የርላይካያ ገልጸዋል።

    እነዚህ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር የዋሉት በሰሜን ምዕራብ የአገሪቱ ከተማ ያሎቫ ውስጥ ከሦስት ቀናት በፊት ለስምንት ሰዓታት በቆየ ከበባ ሦስት ፖሊሶች እና ስድስት ተጠርጣሪ ታጣቂዎች ከተገደሉ በኋላ ነው። በዚህ ክስተት ሌሎች ስምንት የፖሊስ እና የደኅንነት አባላት ቆስለዋል።

    በገና በዓል እና በአዲስ ዓመት ወቅት ሙስሊም ያልሆኑ ሰዎች ላይ ጥቃት ለመፈጸም አቅደዋል የተባሉ 115 ሰዎች ባለፈው ሳምንት ተይዘዋል።

    የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኤክስ ገጻቸው ላይ እንዳሉት በመቶዎች የሚቆጠሩት ተጠርጣዎች የተያዙት አንካራ እና ኢስታምቡልን ጨምሮ በአገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች ውስጥ በተካሄደ ዘመቻ ነው።

  16. ጊኒ ቲክቶክን፣ ዩቲዩብን እና ፌስቡክን አገደች

    ምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር ጊኒ ታዋቂ የማኅበራዊ ሚዲያ የትስስር መድረኮች የሆኑትን ቲክቶክ፣ ዩቲዩብ እና ፌስቡክን አገደች።

    በዓለም ዙሪያ የኢንተርኔት አገልግሎትን የሚከታተለው ድርጅት ኔትብሎክስ እንዳለው በርካታ ተጠቃሚ ያላቸው እነዚህ የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮችን ለጊኒ የኢንተርኔት አገልግሎት በሚያቀርቡት ኦሬንጅ እና ኤምቲኤን በኩል ማግኘት አይቻልም።

    ይህ የማኅበራዊ ሚዲያ አገልግሎቶች መቋረጥ የተከሰተው ባለፈው እሁድ የተደረገው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ውጤት እየተጠበቀ ባለበት ጊዜ ነው።

    ሰኞ አመሻሽ ላይ ይፋ የተደረጉ የመጀመሪያ ደረጃ የምርጫ ውጤቶች ከአንድ ዓመት በፊት በመፈንቅለ መንግሥት ሥልጣን የያዙት ጄነራል ማማዱ ዱምቡያ በሰፊ ውጤት ልዩነት እየመሩ መሆናቸውን ማሳየታቸውን የፈረንሳይ ዜና ወኪል ዘግበዋል።

    በምርጫው የዋነኛው ተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች እንዳይሳተፉ ተከልክለዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ስለተጣለው ዕገዳ ከመንግሥት በኩል የተሰጠ አስተያየት ባይኖርም፤ ተቺዎች ግን እርምጃው በምርጫው ውጤት ላይ የሚሰነዘሩ ትችቶችን ለመቆጣጠር በወታደራዊው መንግሥት ሆንተብሎ የተወሰደ እርምጃ ነው ይላሉ።

  17. ቲክቶከር እና ዩቲዩበሮች "የንግድ ሥራ ገቢ ግብር" ሊከፍሉ ነው

    ግብሩ የሚከፈለው እነዚህ ግለሰቦች ወይም ድርጅቶች "በኦንላይን መድረኮች ላይ የዲጂታል ይዘትን በመፍጠር እና በማሠራጨት" ከሚያገኙት "ማንኛውም ገቢ" ላይ እንደሆነም ተጠቅሷል። ይህ ገቢ "በጥሬ ገንዘብ ወይም በዓይነት የሚገኝ" ሊሆን እንደሚችልም ያስገነዝባል።

    "ማስታወቂያዎች እና ስፖንሰርሺፖች" እንዲሁም "የገንዘብ ስጦታዎች እና የብዙኃን የገንዘብ ማሰባሰብ" ግብር ከሚከፈልባቸው የገቢ ምንጮች መካከል ተጠቅሰዋል።

    ይዘት ፈጣሪዎች "በማስተዋወቂያ እንቅስቃሴ ምትክ" ከሚያገኟቸው "ዕቃዎች ወይም አገልግሎቶች" እንዲሁም ከሚፈጽሟቸው "የምርት ስም ስምምነቶች እና ድጋፎች" ግብር እንዲከፍሉ በአዋጁ ግዴታ ተጥሎባቸዋል።

    ግብር የሚከፍሉት ከምን ያህል ገቢ ጀምሮ የሚያገኙ ይዘት ፈጣሪዎች እንደሆነ የተገለጸው ደግሞ አሁን በተዘጋጀው የገቢ ግብር ረቂቅ ደንብ ነው። ሙሉውን ዜና እዚህ ያንብቡ → በዓመት ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ የሚያገኙ ቲክቶከር እና ዩቲዩበሮች "የንግድ ሥራ ገቢ ግብር" ሊከፍሉ ነው

  18. የዓለማችን ቢሊየነሮች ቁጥር 3,028 ደረሰ

    እየተጠናቀቀ ባለው የአውሮፓውያን ዓመት በዓለም ላይ በተለያዩ አገራት ውስጥ ከ16 ትሪሊየን ዶላር በላይ ሀብት ያላቸው 3,028 ቢሊየነሮች እንዳሉ ፎርብስ ዘገበ።

    ይህ የባለጸጎች ቁጥር ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት ከነበሩት ቢሊየነሮች ላይ 247 ባለሀብቶች በቢሊዮኖች ማማ ላይ በመውጣታቸው ጭማሪ አሳይቷል።

    እነዚህ የዓለማችን ቢሊየነሮች በተለያዩ መስኮች በሥራ ፈጣሪነት፣ በመዋዕለ ነዋይ አፍሳሽነት እና በውርስ ባገኙት ገንዘብ ነው ቀዳሚ የሀብታሞች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት።

    ከዓለም አገራት መካከል ከፍተኛው የቢሊየነር ቁጥር ያላት አሜሪካ ስትሆን 902 ቢሊየነሮች አሏት። ሁለተኛዋ ደግሞ ቻይና ስትሆን ከዜጎቿ 516ቱ ቢሊየነሮች ናቸው።

    ከደረጃ አንጻርም በቢሊየነሮች ዝርዝር ከላይኛው ደረጃ ላይ የሚገኙት የአሜሪካ ባለፀጎች ሲሆኑ፣ እስከ 20ኛ ባለው ደረጃ ላይ ከተቀመጡት ቢሊየነሮች መካከል 15ቱ የአሜሪካ ዜጎች ናቸው።

    የዓለማችን ቁጥር አንዱ ቢሊየነር ደቡብ አፍሪካ የተወለደው የኤክስና ስፔስኤክስ ባለቤቱ ኢላን መስክ ነው።

  19. በኢራን ላይ ተጨማሪ ጥቃት ሊፈጸም እንደሚችል ትራምፕ ተናገሩ

    ኢራን የባለስቲክ እና የኒውክሌር ጦር መሳሪያዎች ግንባታ መርሃ ግብሮቿን መልሳ የምትጀመር ከሆነ የሚፈጸምባትን ሌላ ዙር ከባድ ጥቃት አሜሪካ እንደምትደግፍ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ ከእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ ኢራን የኒውክሊየር ጦር መሳሪያዎችን ለመገንባት ከዚህ ቀደም ዒላማ ከተደረጉት ውጪ ሌሎች ቦታዎችን እየተጠቀመች መሆኗ ከተደረሰበት አሜሪካ ተጨማሪ ጥቃት እንደምትፈጽም ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለሰነዘሩት ዛቻ የኢራን ጠቅላይ መሪ ከፍተኛ የፖለቲካ አማካሪ አሊ ሻምኻኒ በኤክስ ላይ በሰጡት ምላሽ በኢራን ላይ የሚሰነዘር የትኛውም ዓይነት ጠብ ጫሪ ጥቃት “ፈጣን እና የከፋ ምላሽ” ይሰጠዋል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ትራምፕ ባለፈው ዓመት ሰኔ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸሙት የአየር እና የሚሳዔል ጥቃት የአገሪቱ የኒውክሌር ተቋማት “ፈራርሰዋል” ቢሉም፤ ኢራን ግን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እየገነባች አለመሆኑን ገልጻለች።

    "መልሰው ለመገንባት ሙከራ እያደረጉ እንዳልሆነ ተስፋ አደርጋለሁ፣ እየገነቡ ከሆነ ግን ከማጥፋት ውጪ ምንም ዓይነት አማራጭ የለንም" ብለዋል ትራምፕ።

    ፕሬዝዳንቱ ኢራን ባለፈው ዓመት ከተመቱባት ቦታዎች ውጪ ለጦር መሳሪያ ግባታ ሌሎች “ቦታዎችን እየተጠቀመች መሆኑን [የሚያመለክቱ መረጃዎች] እያነበብኩ ነው” በማለት እየወጡ ያሉ ዜናዎችን ጠቅሰዋል።

    ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር ላይ ለ12 ቀናት የዘለቀ ጦርነት ከእስራኤል ጋር ያደረገችው ኢራን፣ የጦር መሳሪያ ተቋማቷን መልሳ እየገነባች መሆኑን የሚያመለክቱ ዘገባዎችን በማውገዝ “የሥነ ልቦና ዘመቻ” እየተካሄደባት መሆኑን ገልጻለች።

    ጨምራም እራሷን ለመከላከል ሙሉ ለሙሉ ዝግጁ መሆኗን እና አዲስ ጥቃት የሚሰነዘርባት ከሆነ በእስራኤል ላይ “አስከፊ ውጤት ይኖረዋል” ስትል ኢራን አስጠንቅቃለች።

  20. “ሐማስ ትጥቅ የማይፈታ ከሆነ ከባድ ቅጣት ይጠብቀዋል” ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የእስራኤሉን ጠቅላይ ሚኒስትር ተቀብለው ያነጋገሩት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሁለተኛው ዙር የጋዛ የሰላም ዕቅድ በፍጥነት እንደሚጀመር በመጠቆም ለሐማስ ከባድ ማስጠንቀቂያ አስተላልፈዋል።

    እስራኤል እና ሐማስ ወደ ቀጣዩ ዙር የሰላም ሂደት በምን ያህል ፍጥነት እንደሚሸጋገሩ በጋዜጠኞች የተጠየቁት ትራምፕ ሂደቱ በአስቸኳይ እንደሚሆን ጠቅሰው ሐማስ ትጥቁን በቶሎ የማይፈታ ከሆነ “ከባድ ቅጣት ይጠብቀዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ባለፉት ወራት ተግባራዊ የሆነው የመጀመሪያው ዙር የጋዛ ስምምነት የተጠናቀቀ ሲሆን በሁለተኛው ዙር ሐማስ ትጥቅ እንዲፈታ ይጠበቃል።

    ትራምፕ ዕቅዳቸው በሆነው የሰላም ስምምነት ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ እንዲሸጋገር መፈለጋቸውን “በዕቅዳችን መሠረት በፍጥነት ወደ ሁለተኛ ምዕራፍ መሸጋገር አለብን። ነገር ግን ትጥቅ ማስፈታት መኖር አለበት” ብለዋል።

    ለዚህም ሐማስ “በተስማማው መሠረት ትጥቅ መፍታት አለበት። ነገር ግን የማይፈታ ከሆነ ከባድ ቅጣት ይጠብቀዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ከዚህ ቀደም ግን የሐማስ ከፍተኛ መሪዎች ትጥቅ የመፍታት ጉዳይ ገና መሆኑን በመጥቀስ ተጨማሪ ንግግር ከአሜሪካ ጋር መደረግ እንዳለበት ሲናገሩ ነበረ።