“እንደ ኢትዮጵያ ያለ አገር የተለያዩ የወደብ መዳረሻዎች ያስፈልጉታል”- ጠ/ሚ ዐቢይ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ለአፍሪካ ሕብረት ጉባዔ ተሰብሳቢዎች ባደረጉት ንግግር ላይ ከ130 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ላለው እንደ ኢትዮጵያ ላለ አገር ቀጣይነት ያለው እድገት የተለያዩ የወደብ መዳረሻዎች ያስፍለጉታል አሉ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስቴር ከዶናልድ ትራምፕ ጋር በኢራን ጉዳይ ሊወያዩ ነው

    ቤንያሚን ኔታንያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የአሜሪካውን ፕሬዚዳንት በዚህ ሳምንት በዋሺንግተን ሲያገኟቸው ከኢራን ጋር ስለነበራቸው ድርድር እንደሚወያዩ ገለፁ።

    “በርካታነገሮችን እንወያያለን። ስለ ጋዛ፣ ስለቀጠናው፣ ነገር ግን በቅድሚያ ከኢራን ጋር ስለነበራቸው ድርድር እናወራለን። ለፕሬዚዳንቱ በድርድሩ መርሆች ላይ ያለኝን ዕይታ አጋራቸዋለሁ” ብለዋል።

    ኔታንያሁበዋሺንግተን ከዶናልድ ትራምፕ ጋር ረቡዕ ዕለት ለመገናኘት ወደ ዩናይትድ ስቴትስ ያመራሉ።

    የኔታንያሁእና የዶናልድ ትራምፕ ውይይት የሚካሄደው በኢራን እና በአሜሪካ መካከል በኦማን ድርድር በተደረገ በጥቂት ቀናት ልዩነት ውስጥ ነው።

  2. የግብፅ ፕሬዝዳንት ጉብኝት በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ

    ፕሬዝዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ እና ፕሬዝዳንት ሼክ ሞሐሙድ ቢን ዛይድ አል ናህያን

    የፎቶው ባለመብት, Egyptian Presidency

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ እና ፕሬዝዳንት ሼክ ሞሐሙድ ቢን ዛይድ አል ናህያን

    የግብፅ ፕሬዝዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ በዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ ጉብኝት አድርገው ከአገሪቱ ፕሬዝዳንት ሼክ ሞሐሙድ ቢን ዛይድ አል ናህያን ጋር ተወያዩ።

    ሁለቱ መሪዎች አቡዳቢ ውስጥ በመካከለኛው ምሥራቅ በተከሰተው ውጥረት እንዲሁም በፍልስጤም እና በእስራኤል ጉዳይ ላይ መወያየታቸው ተነግሯል።

    የግብፅ ፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ መሪዎቹ ቀጠናዊ መረጋጋት የመካከለኛው ምሥራቅ አገራትን “የግዛት አንድነት እና ሉዓላዊነት” ማክበር ላይ የሚመሠረት ነው በማለት በአካባቢው ያለው ውጥረት የሚባባስ ከሆነ ሁሉም አገራት ላይ ተጽእኖ ይኖረዋል ሲል አሳስቧል።

    የግብፁ ፕሬዝዳንት ባለፉት ቀናት ከቱርክ እና ከሶማሊያ አቻዎቻቸው ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ተከትሎ ነው ወደ ዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ ያቀኑት።

    ኤምሬትስ በመካከለኛው ምሥራቅ እና በአፍሪካ ቀንድ ከፍተኛ ተጽእኖ ያላት ሲሆን፣ ግብፅ በታላቁ የሕዳሴ ግድብ ከምትወዛገባት ኢትዮጵያ ጋር የጠበቀ ግንኙነት አላት።

    ሲሲ ከኤምሬትስ መሪ ጋር የምጣኔ ሀብታቸውን ትስስር ለማጠናከር ከመወያየታቸው በተጨማሪ የአገሪቱን የሰው ሠራሽ አስተውሎት ዩኒቨርስቲን በጋራ መጎብኘታቸው ተዘግቧል።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ገንዘብ በመመደብ በሜዲትራኒያን የባሕር ዳርቻ ላይ ግዙፍ ግንባታዎችን ለማካሄድ ከግብፅ ጋር ከአንድ ዓመት በፊት ከስምምነት መድረሷ ይታወሳል።

    ሁለቱ መሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, Egyptian Presidency

  3. ንጉሥ ቻርለስ ወንድማቸው በኤፕስቲን ሰነድ ላይ መጠቀሱን ተከትሎ “ጥልቅ ስጋት” እንደተሰማቸው ገለጹ

    የእንግሊዝ ንጉስ ቻርለስ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የእንግሊዝ ንጉሥ ቻርለስ፤ ከወሲብ ወንጀለኛው ጄፍሪ ኤፕስቲን ጋር በተያያዘ ወንድማቸው አንድሪው ማውንትባተን ዊዶሰር ላይ ለሚደረግ ምርመራ ቤተ መንግሥቱ ከፖሊስ ጋር እንደሚተባበር ገለጹ።

    የቤተ መንግሥቱ ቃል አቀባይ፤ “ንጉሡ ከማውንትባተን ዊዶሰር ባሕሪ ጋር በተያያዘ መውጣት በቀጠሉት ውንጀላዎች የተሰማቸውን ጥልቅ ስጋት በቃላቸው እንዲሁም በተግባራቸው ግልጽ አድርገዋል” ብለዋል።

    ሪፐብሊክ የተባለ ጸረ ንጉሣዊ ቡድን የቀድሞው ልዑል አንድሪው ማውንትባተን ዊዶሰር በሕዝብ ስልጣን ላይ በተፈጸመ ያለአግባብ የሆነ ተግባር እንዲሁም የመንግሥት ምሥጢሮችን በማውጣት ጉዳዮች እንደሚጠረጠሩ በመግለጽ ለፖሊስ አቤቱታ አቅርቦ ነበር።

    ፖሊስም በቀረበው አቤቱታ መሠረት ምርመራ ለማካሄድ የሚያስችል ሁኔታ መኖሩን ወይም አለመኖሩ እየገመገመ እንደሆነ አረጋግጧል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘም ንጉሣዊው ቤተ መንግሥት ከፖሊስ ጋር እንደሚተባበር አስታውቋል። የቤተ መንግሥቱ ቃለ አቀባይ፤ “ተለይተው የቀረቡት ጥያቄዎች በማውንትባተን ዊዶሰር የሚመለሱ ቢሆኑም፤ በቴምስ ቫሊ ፖሊስ የምንጠየቅ ከሆነ እናንተም እንደምትጠብቁት ለመተባበር ዝግጁ ነን” ብለዋል።

    በቅርቡ ይፋ የተደረጉ የኤፕስቲን ሰነዶች የቀድሞው ልዑል ወደ ሲንጋፖር፣ ሆንግ ኮንግ እና ቪየትናም ከሚደረጉ ጉዞዎች ጋር የተያያዙ መረጃዎችን ሲያስተላልፉ እንደነበር ጠቁመዋል። ዝርዝር የምሥጢራዊ ኢንቨስትመንት መረጃዎችም ከተላለፉት የመንግሥት መረጃዎች መካከል እንደሆኑ ሰነዶቹ አመልክተዋል።

    በመንግሥት መመሪያ መሠረት የንግድ ልዑኮች ከይፋዊ ጉዞ ጋር የተገናኙ ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው የንግድ ወይም የፖለቲካ መረጃዎችን በምሥጢራዊነት መያዝ አለባቸው።

    የንጉሣውያኑ ቤተ መንግሥት ባወጣው መግለጫ፤ ንጉሡ እና ንግሥቷ በወሲብ ወንጀለኛው ኤፒስቲን ተግባራት “ማንኛውም ዓይነት በደል ለደረሰባቸው ተጎጂዎች” ያላቸውን ሐዘን ገልጸዋል።

    አዲስ የተለቀቁ ሰነዶች ኤፕስቲን ከቀድሞው ልዑል ጋር ወሲባዊ ግንኙነት እንድታደርግ እንዲት ሴትን ወደ ዩናይትድ ኪንግደም መላኩን አሳይተዋል።

    የቀድሞው ልዑል መሬት ላይ ከተኛች አንዲት ሴት ሥር ተንበርክኮ እና እጆቹን መሬት ላይ አድርጎ የሚያሳይ ፎቶግራፍ መለቀቁም ጫናውን አበርትቶታል።

  4. ኢራን ሁሉም ማዕቀቦች የሚነሱላት ከሆነ የበለጸገ ዩራኒየሟን የጥራት ደረጃ ልትቀንስ እንደምትችል አስታወቀች

    የኢራን ባንዲራ እና የሚቃጠል ነዳጅ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን የተጣሉባት ማዕቀቦች በሙሉ የሚነሱላት ከሆነ በከፍተኛ መጠን ያበለጸገችውን ዩራኒየም የጥራት ደረጃ ዝቅ ለማድረግ ልትስማማ እንደምትችል የአገሪቱ የአቶሚክ ኃላፊ መናገራቸውን የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘገበ።

    ኢራን ያቀረበችው ይህ ሐሳብ ከአሜሪካ ጋር እያደረገችው ባለችው ድርድር በግልጽ አቋሟ የተንጸባረቀበት ተደርጎ ተቆጥሯል።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የባሕር ኃይላቸውን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ማሰማራቸውን ተከትሎ በዋሽንግተን እና ቴህራን መካከል ጦርነት ይነሳል የሚል ስጋት በርትቶ ቆይቷል። ይህ ስጋት ማየሉን ተከትሎም የአሜሪካ እና ኢራን ዲፕሎማቶች ካለፈውሳምንት ጀምሮ በኦማን አደራዳሪዎች አማካኝነት ኦማን ውስጥ ንግግር እያደረጉ ነው።

    የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቋም ባለፈው ዓመት ይፋ ያደረገው ግምት እንደሚያሳየው ኢራን ከ400 ኪሎ ግራም በላይ የሆነ ዩራኒየም አከማችታለች። የኢራን ዩራኒየም እስከ 60% የሚደርስ የጥራት ደረጃ እንዳለውም ተገልጿል።

    ዩራኒየም ለጦር መሣሪያነት ደረጃ ደርሷል የሚባለው 90% ጥራት ሲኖረው ሲሆን የኢራን ክምችት እዚህ ላይ ለመድረስ አንድ እርምጃ ብቻ የቀረው እንደሆነም ተቋሙ አስታውቋል።

    ባለፈው ዓመት የኢራን የኒውክሌር ጣቢያዎች ላይ የአየር ድብደባ የፈጸመችው አሜሪካ፤ ይህን የዩራኒየም ክምችት እንድትተው ትፈልጋለች።

    የኢራን የአቶሚክ ኢነርጂ ድርጅት ኃላፊ መሐመድ ኢስላሚ፤ "60 በመቶ የበለጸገውን ዩራኒየም የመበረዝ (diluting) አማራጭ... በምላሹ የተጣሉብን ሁሉም ማዕቀቦች ይነሳሉ ወይስ አይነሱም በሚለው ላይ የተመሰረተ ነው" ብለዋል።

    እስካሁን ድረስ ከአሜሪካ ባለሥልጣናት ጋር በተደረገው ንግግር የኢራንን የበለጸገ ዩራኒየም ወደ ሌላ አገር የመላክ ሐሳብ እንዳልተነሳም ኃላፊው መናገራቸውን የኢራን የዜና ወኪል አይኤስኤንኤ ዘግቧል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ የቅርብ አማካሪ እና የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ጸሐፊ የሆኑ አሊ ላሪጃኒ፤ ከአሜሪካ ጋር ድርድር እየተደረገባት ወዳለችው ኦማን እንደሚጓዙ ተዘግቧል።

    "በዚህ ጉዞ [ላሪጃኒ] ከኦማን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ተገናኝተው ስለ ወቅታዊው ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች እንዲሁም ስለ ሁለትዮሽ ትብብር ይመክራሉ" ሲል ከፊል ይፋዊ የዜና ወኪል የሆነው ታስኒም ዘገባ አመልክቷል።

    ቀጣዩ ዙር የአሜሪካ እና ኢራን ድርድር የሚካሄድበት ጊዜ እና ቦታ እስካሁን አልታወቀም። የኢራኑ ፕሬዝዳንት መስዑድ ፔዜሽኪያን፤ ቀጣዩ ዙር ንግግር "ለዚህ ጉዳይ ፍትሐዊ እና ሚዛናዊ መፍትሄ ለማግኘት የሚያስችል ተገቢ አጋጣሚ ነው" ብለዋል።

    አሜሪካ ከፍተኛ ጫናዎችን ከማሳደር ከተቆጠበች እና ቃሏን የምታከብር ከሆነ ተፈላጊው ውጤት ላይ መድረስ እንደሚቻልም ገልጸዋል።

  5. ሶማሊያ ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የመከላከያ እና ወታደራዊ ስምምነት ተፈራረመች

    የሶማሊያ እና የሶዑዲ የመከላከያ ሚኒስትሮች ስምምነቱን ሲፈራረሙ

    የፎቶው ባለመብት, @MoDSomaliya

    የምስሉ መግለጫ, የሶማሊያ እና የሶዑዲ የመከላከያ ሚኒስትሮች ስምምነቱን ሲፈራረሙ

    ሶማሊያ እና ሳዑዲ አረቢያ በመካከላቸው ያለውን የመከላከያ እና ወታደራዊ ትብብር የበለጠ ለማጠናከር የሚስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ።

    ስምምነቱ ሁለቱ አገራት ያላቸውን የደኅንነት ትብብር ከማስፋት ባሻገር በቀይ ባሕር ቀጣና መረጋጋትን ለማጠናከር የታለመ መሆኑን የሶማሊያ የመከላከያ ሚኒስቴር ገልጿል።

    ሳዑዲ አረቢያ ሪያድ ውስጥ በሶማሊያው የመከላከያ ሚኒስትር አህመድ ሞአሊም ፊቂ እና በሳዑዲ አቻቸው ልዑል ኻሊድ ቢን ሳልማን የተፈረመው ይህ ስምምነት፤ የተለያዩ የጋራ ወታደራዊ እና የመከላከያ ጉዳዮችን የሚመለከት ነው።

    ሶማሊያ ከሌላ አገር ጋር ወታደራዊ እና ምጣኔ ሀብታዊ ስምምነት ስትደርስ ይህ ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የፈረመችው የመጀመሪያዋ አይደለም።

    ከዚህ ቀደም ከቱርክ እና ከግብፅ ጋር ተመሳሳይ ስምምነት መድረሷ የሚታወስ ሲሆን፣ እስራኤል በቅርቡ ለሶማሊላንድ የአገርነት ዕውቅናን ከሰጠች በኋላ በርካታ አገራት ከጎኗ እንዲቆሙ ጥረት እያደረገች ነው።

  6. በሊባኖስ የመኖሪያ ሕንፃዎች ተደርምሰው 14 ሰዎች ሞቱ

    ሕንፃዎቹ የፈረሱበት ቦታ የአደጋ ሰራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሰሜናዊ ሊባኖስ ከተማ ትሪፖሊ በሁለት የመኖሪያ ሕንፃዎች መደርመስ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 14 መድረሱን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የሲቪል ደኅንነት ጥበቃ መሥሪያ ቤት ዳይሬክተር ኢማድ ክሬይስ የስምንት ሰዎችን ሕይወት መታደግ መቻሉን ተናግረዋል።

    ዳይሬክተሩ እንዳሉት አደጋው በደረሰባቸው ሁለት የተያያዙ ሕንፃዎች ውስጥ 22 ሰዎች ይኖሩ ነበር። ሆኖም አሁንም ያልወጡ ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ የከተማዋ አስተዳደር ባለሥልጣናት አስጠንቅቀዋል።

    በከተማዋ ከታኅሳስ ወር ጀምሮ ባሉት ወራት ብቻ ሕንፃ ሲደረመስ ይህ አምስተኛው ነው።

    ይህም በሊባኖሷ ድሃ ከተማ ውስጥ በሚገኙ ያረጁ እና እድሳት ባልተደረገላቸው ሕንፃዎች ላይ ያለው ስጋት እንዲጨምር አድርጓል።

    የትሪፖሊ ከንቲባ አብደል ሃሚድ ካሪሜህ፣ “በትሪፖሊ የሚኖሩ በሺዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ለዓመታት በቸልተኝነት ምክንያት ስጋት ውስጥ ወድቀዋል” ብለዋል።

    ሁኔታው ከትሪፖሊ ማዘጋጃ ቤት አቅም በላይ እንደሆነም ገልጸዋል።

    በኋላ ላይም ለአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ የሥራ መልቀቂያ አስገብተዋል።

    ፕሬዝዳንትጆሴፍ አውን በበኩላቸው "ያሉትን ክስተቶች እየተከታተልኩ ነው" ሲሉ በመላ አገሪቱ የሚገኙ የነፍስ አድን ሰራተኞችን እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ አቅርበዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም የሕንፃዎቹን መፍረስ “ ሰብዓዊ አደጋ “ ሲሉ መንግሥታቸው እርዳታ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።

    በኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ ያለችው ሊባኖስ ሁለተኛ ትልቅ ከተማ የሆነችው ትሪፖሊ በተደጋጋሚ የሕንፃ መፍረስ አደጋዎች አጋጥመዋታል።

    ባለፈው ወር የአገሪቷ የአደጋ መከላከያ እና ምላሽ ሰጪ ተቋም በከተማዋ ከ100 በላይ ሕንፃዎች ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ለቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ገልጿል።

  7. የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐሙድ እና የግብፁ ፕሬዝዳንት አል ሲሲ በካይሮ

    ፕሬዝዳንት ሞሐሙድ እና አል ሲሲ

    የፎቶው ባለመብት, Egyptian Presidency

    የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐሙድ እና የግብፁ ፕሬዝዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ ካይሮ ውስጥ ባደረጉት ውይይት ያላቸውን የደኅንነት ትብብር በማጠናከር ላይ መስማማታቸው ተዘገበ።

    ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ ወደ ካይሮ ያቀኑት የሶማሊያው ፕሬዝዳንት፤ ከፕሬዝዳንት አልሲሲ ጋር በሰጡት የጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ "የሶማሊያን አንድነት የሚጋፋ የትኛውንም ተግባር በጋራ እንቃወማለን” ብለዋል።

    ግብፅ በበኩሏ በአፍሪካ ኅብረት የሶማሊያ የድጋፍ እና የማረጋጋት ተልዕኮ ሥር ወታደሮቿን ለመላክ በያዘችው ዕቅድ መሠረት ተግባራዊ እንደምታደርግ ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

    የግብፁ ፕሬዝዳንት ጨምረውም የሶማሊያ መረጋጋት ለቀጣናው ልማት እና ደኅንነት “ወሳኝ ጉዳይ ነው” በማለት ሶማሊያን ለመደገፍ አገራቸው የሚጠበቅባትን ታደርጋለች ብለዋል።

    ሶማሊያ የግዛቷ አካል እንደሆነች ለምትመለከታት ሶማሊላንድ እስራኤል የአገርነት ዕውቅና መስጠቷን ተከትሎ ግብፅ እና ሶማሊያ የጋራ አቋም ይዘው ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የሶማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐሙድ በአልጀዚራ ቴሌቪዥን ላይ በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ ሶማሊላንድ ከጋዛ የሚፈናቀሉ ፍልስጤማውያንን ለማስፈር እና ለእስራኤል ጦር ሰፈር ለመስጠት ተስማምታለች ማለታቸውን ሶማሊላንድ ወቅሳለች።

    ፕሬዝዳንቱ በቃለ ምልልሱ ላይ እስራኤል በሶማሊላንድ ውስጥ የጦር ሰፈር የምትመሠርት ከሆነ “እራሳችንን ለመከላከል ባለን አቅም ሁሉ እንፋለማለን” ሲሉ ተቃውሟቸውን አሰምተው ነበር።

    ነገር ግን የሶማሊላንድ ፕሬዝዳንት ቃል አቀባይ ሐሰን አደን በሰጡት ምላሽ ፕሬዝዳንቱ ያሉትን “እውነታ የሌለው ግልጽ ውሸት” በማለት ውድቅ አድርገውታል።

    ቃል አቀባዩ ጨምረውም የሶማሊያ መሪ አስተያየት “በውስጡ የገጠመውን ውድቀት በሌሎች ላይ ለማንጸባረቅ የሚፈለግ የተለመደው ዓይነት ያልተሳካለት አመራር አካሄድ ነው” በማለት ሶማሊያ የራሷን ደኅንነት እንኳን መጠበቅ ያልቻለች ናት በማለት ተናግረዋል።

  8. ሱዳን ዳግም ኢጋድን ተቀላቀለች

    የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ) ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)

    የፎቶው ባለመብት, @DrWorkneh

    ሱዳን ከሁለት ዓመት በኋላ ዳግም የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታት ድርጅትን መቀላቀሏን አስታወቀች። ወደ ድርጅቱ ዳግም መቀላቀሏን ይፋ ያደረጉት የድርጅቱ የወቅቱ ፕሬዚዳንት የጂቡቲው ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ኦማር ጊሌ ናቸው።

    የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ) ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ሱዳን ወደ ቀጣናዊ ድርጅቱ ዳግም በመመለሷ የተሰማቸውን ደስታ ገለፀዋል።

    የኢጋድ የወቅቱ ሊቀመንበር የሆኑት የጂቡቲው ፕሬዚዳንት፤ ሱዳን ዳግም ቀጠናዊ ድርጅቱን መቀላቀሏን ያስታወቁት እሁድ ዕለት ነበር።

    ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ሱዳን ወደ ቀጣናዊ ድርጅት መመለሷን “ለቀጣናዊ አንድነት” ያላትን ቁርጠኝነት ያጋገጠ ነው ያሉ ሲሆን፤ እንዲሁም “በቀጣናው ውስጥ ላለው ሰላም፣ መረጋጋት እና ትብብር ያላትን" ፍላጎት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል።

    ሱዳን ከኢጋድ አባልነቷ የወጣችው በኡጋንዳ በተዘጋጀው የድርጅቱ ጉባዔ ላይ የፈጥኖ ደራሽ አዛዡ ሞሐመድ ሀምዳን ዳጋሎ መገኘታቸውን በመቃወም ነው።

    የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል እአአ ከሚያዚያ 2023 ጀምሮ ከሱዳን ጦር ጋር እየተዋጋ ይገኛል።

    ሱዳን የኢጋድ መስራች አባል አገራት መካከል አንዷ መሆኗን ያስታወሱት የደርጅቱ ዋና ጸሐፊ ዳግም ወደ ድርጅቱ መመለሷ “የኢጋድን አንድነት እንደሚያጠናክር እና በቀጠናው ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የጋራ ጉዳዮች የመፍታት አቅሟን እንደሚያሳድግ” ተናግረዋል።

    የወቅቱ የኢጋድ ሊቀመንበር የጂቢቲው ፕሬዚዳንት ሱዳን ወደ ድርጅቱ እንድትመለስ ላደረጉት ጥረትም አመሰግነዋል።

    ኢጋድ በምሥራቅ አፍሪካ የሚገኙ ስምንት አገራትን ያቀፈ ቀጣናዊ ድርጅት ሲሆን እነርሱም ኢትዮጵያ ፣ ጂቡቲ፣ ኤርትራ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን እና ኡጋንዳ ናቸው።

    ኤርትራ በቅርቡ ከአባልነት ራሷን ማግለሏን ማስታወቋ ይታወሳል።

    ተቋሙ ቀጣናዊ ትብብር ላይ የተመሠረተ ፖለቲካዊ መረጋጋትና የምጣኔ ኃብት እድገት እንዲገኝ የሚሠራ ነው።

  9. በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተጀመረው ድርድር መቀጠል እንዳለበት ሩሲያ ገለፀች

    ሰርጌይ ላቭሮቭ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የሩሲያ እና የኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በስልክ ከተወያዩ በኋላ በኢራን እና በዩናይትድ ስቴትስ መካከል የተጀመረው ድርድር መቀጠል አለበት አሉ።

    የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ እና የኦማኑ ባድር አል አሳዲ በሁለቱ ተደራዳሪ አገራት መካከል ወታደራዊ እሰጥ አገባን ለማስቀረት ንግግራቸው መቀጠል አለበት ብለዋል።

    የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ላይ ኦማን ሁለቱን አገራት ለማደራደር እያደረገች ያለውን ጥረት አድንቋል።

    በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ድርድር የተጀመረው አርብ ዕለት ነበር።

    የኢራን ልዑካን ቡድን በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አባስ አራጋቺ የተመራ ሲሆን በስቲቭ ዊትከር ከተመራው የአሜሪካው ተደራዳሪ ቡድን ጋር በኦማን ተገናኝቶ ተነጋግሯል።

    እንደ ኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒሲቴር መግለጫ ተደራዳሪዎቹ በኢራን ኒውክለር ፕሮግራም ላይ ጠንካራ ውይይት ያካሄዱ ሲሆን ንግግሩንም የመቀጠል ፍላጎት እንዳላቸው ገልጿል።

  10. የኢራን የበላይ መሪ አሊ ኻሜኒ ባልተለመደ ሁኔታ በኢራን አብዮት በዓል ላይ ሳይገኙ ቀሩ

    የኢራን የበላይ መሪ አሊ ኻሜኒ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በየዓመቱ የካቲት ወር መጀመሪያ ላይ የሚከበረው የኢራን አብዮት መታሰቢያ ዝግጅት ላይ ባልተለመደ ሁኔታ የኢራን የበላይ መሪ አሊ ኻሜኒ ሳይገኙ ቀሩ።

    በእርሳቸው ምትክ የኢራን ጦር የበላይ አዛዥ የሆኑት ሜጀር ጄነራል አብዶልራሂም ሚሳቪ ክብረ በዓሉ ላይ ተገኝተው ንግግር አድርገዋል።

    የሚሳቪ ጠቅላይ መሪውን ወክለው በመገኘታቸው የተሰማቸውን ክብር ለታዳሚዎቹ ባደረጉት ንግግር ላይ ገልጸዋል።

    በኢራኑ የበላይ መሪ ምትክ በበዓሉ ላይ የታደሙትን የተለያዩ ወታደራዊ አዛዦችን ያገኙት ሚሳቪ በንግግራቸው ላይ ከአሜሪካ ጋር ሊኖር ስለሚችል ግጭት በማንሳት “ቀጠናዊ ጦርነት ለመጀመር ምንም ፍላጎቱ የለንም” ብለዋል።

    ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ተቃዋሚዎች አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ከሥልጣን እንዲወርዱ እና በሕዝባዊ አብዮት የመጣውን የእስላማዊውን ሪፐብሊክ አገዛዝ እንዲያበቃ ሲጠይቁ ነበር።

    በኢራን ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች ለሳምንታት በተካሄዱት የተቃውሞ ሰልፎች ላይ የተሳተፉ በርካቶች ሲታሰሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ደግሞ መገደላቸው ይታወሳል።

  11. ታዋቂው ሆንግ ኮንጓዊ የሚዲያ ባለቤት እና የዲሞክራሲ ተሟጋች የ20 ዓመት እስር ተፈረደበት

    ጂሚ ላይ በፖሊስ ታጅቦ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የሆንግ ኮንግ ፍርድ ቤት የዲሞክራሲ አቀንቃኝ እና የሚዲያ ባለቤት የሆነው ጂሚ ላይ ከብሔራዊ ደኅንነት ጋር ተያይዞ በቀረበበት ክስ ጥፋተኛ ሆኖ በማግኘቱ የ20 ዓመት እስር ፈረደበት።

    ቻይና ከከተማዋ መረጋጋት ጋር በተያያዘ አስፈላጊ ነው በምትለው እና አወዛጋቢ በሆነው የብሔራዊ ደኅንነት ሕግ መሠረት የተሰጠው ይህ የፍርድ ውሳኔ በጣም ከባዱ ነው ተብሏል።

    ላይ የብሪታኒያ ፓስፖርት ያለው ሲሆን የቻይና መንግሥትን ክፉኛ በመተቸት ይታወቃል።

    አፕል ዴይሊ የተሰኘ በየዕለቱ የሚታተም ጋዜጣ ባለቤት የሆነው ላይ በተደጋጋሚ በአገሪቱ ውስጥ ለተካሄዱ የተቃውሞ ሠልፎች መነሻ ሆኗል።

    ሰኞ ዕለት ስድስት የጋዜጣው የቀድሞ ኃላፊዎች ከስድስት እስከ 10 ዓመት እስር ተፈርዶባቸው በቁጥጥር ሥር ውለዋል።

    በዲሞክራሲ አቀንቃኞች ዘንድ እንደ ጀግና የሚቆጠረው ላይ፣ በቤይጂንግ ግን አንደ አገር ከዳተኛ ይወነጀላል።

    በተደጋጋሚ የቻይና መንግሥት የሚያቀርበብትን ክስ የሚያስተባብለው የሚዲያ ባለቤቱ ላይ የሆንግ ኮንግ እሴቶች የሆኑ የሚላቸው የሕግ የበላይነት እና የመናገር ነጻነትን እንዲሚሰብክ ይናገራል።