ሐማስ ጥቃት ፈጽሞ እስራኤል ጋዛ ላይ የአየር ድብደባ ከጀመረች አንድ ሳምንት ሆነ

ልክ የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ መስከረም 26/2016 ዓ.ም. ማለዳ ሐማስ በእስራኤል ላይ በፈጸመው የተቀናጀ ጥቃት የተጀመረው ግጭት ተባብሶ ቀጥሏል። ባለፉት ሰባት ቀናት እስራኤል በጋዛ ላይ ቀን አና ሌሊት ያለተቋረጠ የአየር ድብደባ አየፈጸመቸ ሲሆን፣ ሐማስም ወደ እስራኤል ሮኬቶቸን ሲተኩሰ ቆይቷል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ የአስቸኳይ ጊዜ መንግሥት እና የጦርነት ካቢኔ አቋቋሙ

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ እና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪው ቤኒ ጋንትዝ የአስቸኳይ ጊዜ መንግሥት ለማቋቋም ተስማሙ።

    ሁለቱ ፖለቲከኞች እዚህ ስምምነት ላይ የደረሱት ሐማስ ድንገተኛ ጥቃት ከፈጸመ በኋላ እስራኤል መጠነ ሰፊ የአጸፋ እርምጃ በጋዛ ላይ እያካሄደች ባለበት አምስተኛ ቀን ላይ ነው።

    ይህንን ስምምነት ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ፣ ጋንትዝ እና የአገሪቱ የመከላከያ ሚኒስትር ያሉበት “የጦርነት ካቢኔ” ያቋቁማሉ ተብሏል።

    በስምምነቱ መሠረት ጦርነቱ በሚካሄድበት ጊዜ “የጦርነቱን ሂደት ከሚመለከቱ ጉዳዮች በስተቀር ማንኛውም አይነት ሕግም ሆነ የመንግሥት ሃሳብ ለውሳኔ አይቀርብም።”

    በተጨማሪም ከዚህ ቀደም ከፍተኛ የመንግሥት ሥልጣንን እንዲይዙ የተሾሙ ሰዎች የኃላፊነት ጊዜ በጦርነቱ ወቅት ሁሉ የሚቀጥል ይሆናል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ እና የናሽናል ዩኒቲ ፓርቲ ሊቀ መንበር ጋንትዝ የአስቸኳይ ጊዜ መንግሥት ለማቋቋም የተስማሙት ላለፉት ቀናት ንግግር ካደረጉ በኋላ ነው።

    ከስምምነቱ በኋላ ከሁለቱም ወገን በጋራ በወጣ መግለጫ ላይ “የአስቸኳይ ጊዜ መንግሥት ለመመሥረት እና ጦርነቱን የሚመራ ካቢኔ ለማቋቋም ተስማምተዋል።

    “ጦርነቱን የሚመራው ካቢኔም ጠቅላይ ሚኒስትሩን፣ የመከላከያ ሚኒስትሩን እና የተቃዋሚ ፓርቲውን መሪ በአባልነት ይዞ ይመሠረታል” ተብሏል።

    ከሦስቱ ባለሥልጣናት በተጨማሪ የጦርነቱ መሪ ካቢኔን በታዛቢነት የሚያገለግሉ ሁለት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ይካተቱበታል።

  2. ረቡዕ የተከሰቱ ዋና ዋና ጉዳዮች

    እስራኤል በሐማስ ለተፈጸመባት ጥቃት አጸፋ ጋዛ ላይ ከበባ በመጣል ለአምስተኛ ቀን ተከታታይ የአየር ጥቃት እየፈጸመች ሲሆን፣ ሐማስም የሮኬት ጥቃቱን ቀጥሏል።

    በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የጋዛ ነዋሪዎች ተፈናቅለዋል።መሠረታዊ አቅርቦቶች በከተማዋ ውስጥ እየተሟጠጡ መሆናቸው እየተዘገበ ነው።

    ዛሬ ረቡዕ እስካሁን የተከሰቱ ዋና ዋና ጉዳዮች ምንድን ናቸው?

    • እስራኤል በጋዛ ላይ በጣለችው ጥብቅ ገደብ የነዳጅ ዕጥረት በመከሰቱ የከተማዋ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ማዕከል ሥራ ማቆሙን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።
    • ሰኞ ዕለት እስራኤል ወደ ጋዛ የሚገቡ የኤሌክትሪክ እና የውሃ መስመሮች እንዲሁም የነዳጅ አቅርቦትን እንደምታቋርጥ አስታውቃ ነበር።
    • የእስራኤል የአየር ጥቃት በጋዛ ላይ ተጠናክሮ በቀጠለበት በአሁኑ ጊዜ በርካታ የከተማዋ ነዋሪዎች ከጥቃት ለመሸሽ ወደ ሆስፒታሎች እና ትምህርት ቤቶች እየገቡ ነው።
    • በእስራኤል ሰሜን እና ደቡብ ግዛቶች ውስጥ የሮኬት ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደወሎች የተሰሙ ሲሆን፣ ከጋዛ በተተኮሱ ሮኬቶች የቆሰሉ ሰዎች እንዳሉ ተዘግቧል።
    • የእስራኤል ጦር 300 ሺህ ተጠባባቂዎችን ጨምሮ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ወታደሮችን በጋዛ ድንበር ላይ አሰባስቧል።
    • እስራኤል በድንበር በምትጎራበታት ሊባኖስ ውስጥ የሚገኙ የሄዝቦላህ ታጣቂዎች የፈጸሙባትን ጥቃት ተከትሎም ሊባኖስ ግዛት ውስጥ የአጸፋ ጥቃት ፈጽማለች።
  3. በእስራኤል-ፍልስጥኤም ግጭት የአፍሪካ አገራት ምን አቋም ያዙ?

    ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ የተቀሰቀሰውን ግጭት በተመለከተ የዓለም አገራት የተለያየ አቋማቸውን እያንጸባረቁ ነው።

    በዚህም በግልጽ ከእስራኤል ወይም ከፍልስጥኤም ጎን መሠለፋቸውን ያሳወቁ አገራት የመኖራቸውን ያህል፣ ከየትኛውም ወገን ሳይቆሙ ገለልተኛ አቋም ያንጸባረቁም አሉ።

    ከ54ቱ የአፍሪካ አገራት መካከልም ከፍልስጥኤም ጎን የተሰለፉ፣ እስራኤልን የደገፉ፣ ገለልተኛ አቋም የያዙ እና ለጊዜው ዝምታን የመረጡ አገራት አሉ።

    በዚህ ዝርዝር አስካሁን በይፋ አቋማቸውን ያንጸባረቁ የአፍሪካ አገራት ተካተዋል።

  4. ጋዛ ውስጥ በእስራኤል ጥቃት የተገደሉት ፍልስጥኤማውያን ቁጥር 1,055 ደረሰ

    እስራኤል ጋዛ ላይ እያካሄደችው ባለው የአየር ጥቃት ምክንያት የተገደሉ እና ጉዳት የደረሰባቸው ፍልስጥኤማውያን ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ነው።

    የፍልስጥኤም የጤና ሚኒስቴር ረቡዕ እኩለ ቀን ላይ ባወጣው መረጃ የተገደሉ ሰዎች አሃዝ 1,055 ሲደርስ፣ ከ5,100 በላይ ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ጨምሮ እንዳለው፣ በጥቃቱ ከተጎዱት ሰዎች መካከል 60 በመቶዎቹ ሴቶች እና ሕጻናት ናቸው።

    ሐማስ ቅዳሜ ዕለት በፈጸመው ጥቃት የተገደሉ እስራኤላውያን 1,200 ሲሆኑ ከ2,700 በላይ የሚሆኑ ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

  5. እስራኤል በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቿን ወደ ጋዛ እያስጠጋች ነው

    የእስራኤል አየር ኃይል ጋዛ ውስጥ የሐማስ ናቸው ያላቸውን ኢላማዎች ለአራተኛ ቀን እየደበደበ ባለበት በዛሬው ዕለት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የእስራኤል ወታደሮች ከጋዛ አቅራቢያ ሰፍረዋል።

    የሐማስ ጠንካራ ይዞታ በሆነችው ጋዛ ላይ እየተፈጸመ ባለው የአየር ጥቃት ምክንያት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የጋዛ ነዋሪዎች መፈናቀላቸው የተዘገበ ሲሆን፣ በነዳጅ ችግር ምክንያት በከተማዋ በሰዓታት ውስጥ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ይቋረጣል።

    የሐማስ ተዋጊዎችን ለማደን እና የታገቱ ዜጎቿን ለማስለቀቅ እስራኤል እግረኛ ሠራዊቷን ወደ ጋዛ ታሰማራ እንደሆነ አስካሁን የታወቀ ነገር ባይኖርም፣ አስፈላጊውን ሁሉ እርምጃ እንደምትወስድ አስታውቃለች።

    የእስራኤል ጦር ሠራዊት ዛሬ ረቡዕ እንዳሳወቀው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቹ “የተሰጣቸውን ተልዕኮ ለመፈጸም ዝግጁ ሆነው” ከጋዛ አቅራቢያ ይገኛሉ ብሏል።

  6. የፍልስጥኤማውያን የተቃውሞ ሰልፍ በዌስት ባንክ

    ዛሬ ረቡዕ ማለዳ ጎህ ሲቀድ ከጋዛ ባሻገር በወረራ በተያዘችው ዌስት ባንክ ውስጥ ያሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ፍልስጥኤማውያን እስራኤል በጋዛ ላይ እየፈጸመችው ያለውን የአውሮፕላን ድብደባ በመቃወም ሰልፍ አድርገዋል።

    የፍልስጥኤም ዜና አገልግሎት እንደዘገበው ተቃዋሚ ሰልፈኞቹ የፍልስጥኤምን ሰንደቅ ዓላማ እና በጥቃቱ የተገደሉ ሰዎችን ፎቶፍራፎች ይዘው ነው አደባባይ የወጡት።

  7. ኢራን በእስራኤል ላይ ለተፈጸመው ጥቃት ድጋፏን ሰጥታ ይሆን?

  8. የቀጠለው የእስራኤል ጥቃት እና የአውሮፓ ኅብረት ትችት

    • ሌሊቱን የእስራኤል አየር ኃይል የጦር ጄቶች የሐማስ የሮኬት ጥቃቶች የሚወነጨፉበት ነው ባለው የጋዛው አል-ፉርቃን አካባቢ ያሉ ከ200 በላይ ኢላማዎች ላይ ድብደባ መፈጸሙን ገልጿል። ይህም ጥቃት ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ የተፈጸመ ሦስተኛው ድብደባ ነው።
    • እስራኤል ሌሊቱን ጋዛ ላይ በፈጸመችው የአየር ድብደባ ቢያንስ 30 ሰዎች መገደላቸውን የሐማስ ቃል አቀባይ አስታወቁ።
    • የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሆኑት ጆሴፍ ቦሬል እስራኤል በጋዛ ላይ እየወሰደች ያለችው እርምጃ ዓለም አቀፍ ሕግን የጣሰ ነው ሲሉ ተቹ። “እስራኤል እራሷን የመከላከል መብት ቢኖራትም ይህንን ማድረግ ያለባት በዓለም አቀፍ ሕጎች መሠረት መሆን አለበት” ብለዋል።
    • የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን የሐማስን ጥቃት አጥብቀው ያወገዙ ሲሆን አሜሪካ ለእስራኤል የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ በማጠናከር የመጀመሪያው የጦር መሳሪያ ድጋፍ ማክሰኞ ደቡባዊ እስራኤል ደርሷል።
    • የጋዛ ነዋሪዎች “ደኅንነቱ የተጠበቀ መተላለፊያ” እንዲያገኙ ከእስራኤል እና ከግብፅ ጋር እየተነጋገረች መሆኗን የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ጃክ ሰሊቫን ገለጹ።
    • አስካሁን ከፍልስጥኤም እና ከእስራኤል ወገን የሞቱት ሰዎች አሃዝ በአጠቃላይ ወደ 2,100 ሲደርስ፣ ከእስራኤል በኩል 1,200፣ ከፍልስጥኤም ወገን ደግሞ 900 ሰዎች ተገድለዋል።
    • በጥቃቶቹ የደረሰው ጉዳት ታይቶ የማይታወቅ መሆኑን እስራኤላውያን እና ፍልስጥኤማውያን እየተናገሩ ነው። እስራኤላውያን “በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተፈጸመ ጭፍጨፋ ነው” ሲሉ፣ ፍልስጥኤማውያን ደግሞ “ሕይወታችንን የምናድንበት ቦታ አጣን” እያሉ ነው።
  9. እስራኤል ከሶሪያ በኩል ለተሰነዘረ ጥቃት አጸፋውን መመለሷን ገለጸች

    የእስራኤል ጦር ሠራዊት ከሶሪያ በኩል ወደ ጉላን ተራሮች ለተሰነዘረ የከባድ መሳሪያ ጥቃት በመድፍ ተኩስ ምላሽ መስጠቱን ገለጸ።

    የጎላን ተራሮች የ1967ቱን የአረብ እስራኤል ጦርነትን ተከትሎ እስራኤል አስካሁን ድረስ በወረራ የያዘቻቸው መሆኑ ይታወቃል።

    የእስራኤል ጦር ባወጣው መግለጫ ከሶሪያ በኩል የተሰነዘረውን የከባድ መሳሪያ ጥቃት ተከትሎ “ወታደሮቻችን መድፍ እና ሞርታር ጥቃቱ ወደ ተነሳበት ስፍራ በአጸፋው ተኩሰዋል” ብሏል።

    ጨምሮም ቀደም ሲልም በርካታ ጥቃቶች ከሶሪያ በኩል ወደ እስራኤል ግዛቶች መፈጸማቸውን ገልጿል።

    የእስራኤል ጦር ሠራዊት ቃል አቀባይ ለፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ ጥቃቶቹ በሞርታር እንደተፈጸሙ ገልጸዋል።

    ሐማስ ባለፈው ቅዳሜ የፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ ግጭቱ ከተባባሰ በኋላ በእስራኤል እና በሶሪያ መካከል የከባድ መሳሪያ ተኩስ ልውውጥ ሲካሄድ ይህ የመጀመሪያው ነው።

  10. በአራት ቀናት ውስጥ ከ260 ሺህ በላይ ፍልስጥኤማውያን ከጋዛ ተፈናቅለዋል፡ የተባበሩት መንግሥታት

    የእስራኤል ጦር ሠራዊት የፍልስጥኤሟን ግዛት ጋዛን በጦር አውሮፕላኖች መደብደቡን በቀጠለበት በአሁኑ ጊዜ ከ260 ሺህ በላይ ሰዎች ከጋዛ መፈናቀላቸውን የተባበሩት መንግሥታት አስታወቀ።

    ድርጅቱ እንዳለው ይህ በአራት ቀናት ያጋጠመው የነዋሪዎች መፈናቀል ከሰባት ዓመት በፊት ጋዛ ውስጥ ሁለት ወራት ለሚጠጋ ጊዜ ቆይቶ በነበረው ግጭት ከተፈናቀሉት የበለጠ ነው። የተፈናቃዮች ቁጥር ከዚህም በላይ ሊጨምር እንደሚችል ይጠበቃል።

    ጋዛ ሰርጥ ውስጥ 2.3 ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎች የሚኖሩ ሲሆን፣ በጠባብ ስፍራ ላይ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ተጠጋግተው ከሚኖሩባቸው ቦታዎች መካከል የሚጠቀስ ነው።

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጨምሮ እንዳለው ለቀናት በቀጠለው የአየር ጥቃት ጋዛ ውስጥ ከአንድ ሺህ በላይ የመኖሪያ ቤቶች ወድመዋል።

    የእስራኤል የአየር ጥቃት በቀጠለበት ሁኔታ በጋዛ ውስጥ ለሚገኙ ነዋሪዎች መሠረታዊ አቅርቦቶችን ማሟላት “በጣም ፈታኝ” እየሆነ መምጣቱ ተገልጿል።

    ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በቀጠለው ግጭት እስካሁን በእስራኤል በኩል 1,200 እንዲሁም ከፍልስጥኤም ወገን ደግሞ ከ900 በላይ ሰዎች ተገድለዋል።

  11. የዛሬ ዋና ዋና ክስተቶች በአጭሩ

    ባለፈው ቅዳሜ የተቀሰቀሰው የእስራኤል እና የሐማስ ውጊያ ለአራተኛ ቀን ቀጥሎ እስራኤል ጋዛን በጦር ጀቶቿ ስትደበድብ፣ ሐማስ ደግሞ ሮኬቶችን ወደ እስራኤል መተኮሱን ቀጥሏል።

    በዛሬው ዕለት የተከሰቱ ቁልፍ ነገሮችን አጭሩ እነሆ፡...

    • ·የሐማስ ታጣቂዎች እስራኤላውያን ነዋሪዎች አሽኬሎን ከተባለችው ከተማ ለቀው እንዲወጡ አሰጠንቅቀው አመሻሽ 12 ሰዓት ላይ የሮኬት ተኩስ በከተማዋ ውስጥ ተሰምቷል።
    • ·የሐማስን ጥቃት ተከትሎ የደረሱበት ያልታወቁ የአሜሪካ ዜጎች ዘመዶች በእስራኤሏ መዲና ቴል አቪቭ ውስጥ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እየጠበቋቸው ስላሉት የቤተሰቦቻቸው አሳዛኝ ታሪኮችን ተናግረዋል።
    • ·ከቅዳሜ ጀምሮ በእስራኤል የአየር ድብደባዎች የተገደሉ ፍልስጥኤማውያን ቁጥር ወደ 830 ሲደርስ፣ በእስራኤላውያን በኩል የተመዘገበው ሞት ደግሞ ቢያነስ 1,008 መድረሱ ተዘግቧል።
    • ·ሐማስ “ውጊያው አስኪቆም ድረስ” በእገታው ስር ስላሉ እስራኤላውያን ጉዳይ እንደማይነጋገር አሳውቋል። አስካሁን ባለ መረጃ ከ100 አስከ 150 የሚደርሱ እስራኤላውያን በሐማስ እገታ ውስጥ እንዳሉ ይታመናል።
    • ·እስራኤል ጋዛ ላይ የምትፈጽመው የአየር ጥቃት ቀን ከሌት ሳይል የቀጠለ ሲሆን፣ ሐማስም ሮኬቶቹን ማስወንጨፉን ቀጥሏል።
  12. የሳዑዲው ልዑል ሞሐመድ ቢን ሳልማን ለፍልስጥኤማውያን ድጋፋቸውን ገለጹ

    የሳዑዲው ልዑል አልጋ ወራሽ ሞሐመድ ቢን ሳልማን አገራቸው የፍልስጥኤማውያን መብት እንዲከበር ድጋፏን እንደምትቀጥል ተናገሩ።

    ሳዑዲ አረቢያ መሪ የሆኑት ቢን ሳልማን ይህንን ያሉት እስራኤል በሐማስ የተፈጸመባትን ጥቃት ተከትሎ ጋዛ ውስጥ ከባድ ጥቃት እያካሄደች ባለበት ጊዜ ከፍልስጥኤም ፕሬዝዳንት ማሐሙድ አባስ ጋር በስልክ በተወያዩበት ጊዜ ነው።

    ቢን ሳልማን “ፍልስጥኤማውያን ተገቢ መብቶቻቸው፣ የተረጋጋ ሕይወት፣ ፍትሃዊ እና ዘላቂ ሰላምን እንዲያገኙ ለማስቻል” አገራቸው ድጋፏን ትቀጥላለች ብለዋል።

    ጨምረውም ከዓለም አቀፍ እና ከአካባቢያው ማኅበረሰብ ጋር በመሆን ግጭቱ እንዳይስፋፋ እየሰሩ መሆናቸውን ለአባስ ገልጸውላቸዋል።

    ፍልስጥኤሙ ፕሬዝዳንት ማሐሙድ አባስ እና ጋዛን የተቆጣጠረው ሐማስ የፖለቲካ ተቀናቃኞች ናቸው። አባስ ሌላኛውን የፍልስጥኤም ግዛት ዌስት ባንክን የተቆጣጠረው የፋታህ ንቅናቄ እና የፍልስጥኤም ነጻነት ድርጅት (ፒኤልኦ) መሪ ናቸው።

    ሳዑዲ አረቢያ ለፍልስጥኤም ያላትን ድጋፍ የገለጸችው በአሜሪካ አማካይነት ከእስራኤል ጋር ያላትን ግንኙነት ለመሻሻል ድርድር እየተደረገ ባለበት ጊዜ ነው።

    ተንታኞች የተቀሰቀሰው ግጭት ግንኙነታቸውን ለማሻሻል በእስራኤል እና በሳዑዲ መካከል በሚደረገው ጥረት ላይ እንቅፋት ደቅኗል ብለዋል።

    ቅዳሜ ዕለት የተፈጸመውን የሐማስን ጥቃት ተከትሎ ሳዑዲ አረቢያ ባወጣችው መግለጫ ለግጭቱ መባባስ እስራኤልን ተጠያቂ አድርጋለች።

  13. ውጊያው ሳይቆም በታጋቾች ጉዳይ ላይ አንደራደርም፡ ሐማስ

    ውጊያው እስኪያቆም ድረስ በቁጥጥሩ ስር ስላሉ ታጋቾች ሐማስ ከእስራኤል ጋር እንደማይደራደር የቡድኑ ፖለቲካ ቢሮ ኃላፊ ኢስማኤል ሃኒያህ ተናገሩ።

    “በቁጥጥራችን ስር ያሉ የጠላት አስረኞች ጉዳይ ጦርነቱ ከማብቃቱ በፊት እንደማይነሳ ጥያቄ ላቀረቡልን ወገኖች ሁሉ አሳውቀናቸዋል” ያሉት ሃኒያህ ቡድናቸው “ጉዳዩን የሚቀበለው የሚፈልገውን ምላሽ ሲያገኝ ብቻ ነው” ብለዋል።

    ሐማስ ባለፈው ቅዳሜ በእስራኤል ላይ ጥቃት መክፈቱን ተከትሎ፣ ከደቡባዊ እስራኤል አካባቢዎች በ100 እና በ150 መካከል የሚገኙ ሰዎች በፍልስጥኤማዊው ቡድን ቁጥጥር ስር እንደሚገኙ ተዘግቧል።

    የኳታር እና የአሜሪካ አሸማጋዮች ሐማስ እና እስራኤል በእጃቸው ያሉ ሴቶች እና ሕጻናት እስረኞችን እንዲለዋወጡ ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን ሮይርስ ዘግቦ ነበር።

    የሐማስ ጥቃትን ተከትሎ ለቀናት የቆየ የአጸፋ ጥቃት እየፈጸሙ ያሉት የእስራኤል መከላከያ ኃይሎች ዛሬ ማክሰኞም የሐማስ ናቸው ያሏቸውን ኢላማዎች ማጥቃታቸውን ቀጥለዋል።

    ሰኞ ሌሊት የእስራኤል አየር ኃይል 200 ኢላማዎችን ጋዛ ውስጥ መደብደቡን ገልጸዋል።

  14. ሰበር, በጋዛ የተገደሉ ፍልስጥኤማውያን ቁጥር 770 ደረሰ

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ እየፈጸመቻቸው ያሉ የአየር ጥቃቶችን ተከትሎ በጋዛ ሰርጥ የተገደሉ ፍልስጥኤማውያን ቁጥር 770 ደረሰ።

    በተጨማሪም 4 ሺህ 100 መቁሰላቸውን የእስራኤል ጤና ሚኒስቴር ገልጿል።

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ሙሉ ከበባ እንዲፈጸም ትዕዛዝ መስጠቷን ተከትሎ የዓለም የጤና ድርጅት ለሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት መተላለፊያ እንዲኖር ጥሪ አቅርቧል።

    እስራኤል በጋዛ የኤሌክትሪክ፣ ምግብ፣ ነዳጅ እና ውሃ አቅርቦት እንዲቋረጥም ማድረጓን ተከትሎ ነው የዓለም የጤና ድርጅት እና ዩኒሴፍ የሰብዓዊ እርዳታ እንዲገባ እየጠየቁ ያሉት።

    የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ኃላፊ ቮልከር ቱርክ የሃማስን ጥቃት አውግዘው የእስራኤል ከበባ በዓለም አቀፍ ህግ መሰረት ህገወጥ ነው ብለዋል።

  15. በእስራኤል እና በሐማስ መካከል የተፈጠረው ግጭት አጀማመር ምን ይመስላል?

  16. በጋዛ 187 ሺህ ፍልስጥኤማውያን ተፈናቅለዋል- ተመድ

    እስራኤል ገና መጀመሩ እንደሆነ በገለጸችው የጋዛ የአየር ጥቃቶችን ተከትሎ 187 ሺህ ፍልስጥኤማውያን መፈናቀላቸውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አስታውቋል።

    ቁጥሩ ከዚህ ሊልቅ እንደሚችልም ነው ተመድ ያሳሰበው።

    በጋዛ ባሉ 83 የተባበሩት መንግሥታት ትምህርት ቤቶች ውስጥ 137 ሺህ 500 ፍልስጥኤማውያን ተጠልለው ይገኛሉ ተብሏል።

    በጋዛ የሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት የፍልስጥኤም ስደተኞች ኤጀንሲ ጽህፈት ቤት በአየር ጥቃቱ ጉዳት ደርሶበታል ተብሏል።

    በጋዛ የሚገኙ የምግብ ማከፋፈያ ማዕከላት በመዘጋታቸው ወደ ግማሽ ሚሊዮን የሚጠጉ ፍልስጥኤማውያን የተባበሩት መንግሥታት የምግብ እርዳታ ማግኘት አልቻሉም ተብሏል።

    እስራኤል ጋዛ ሰርጥን ሙሉ በሙሉ በመዝጋት ከበባ እንዲደረግ አዛለች። በጋዛ 'ኤሌክትሪክ፣ ምግብ፣ ነዳጅ አይኖርም ሲሉም የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ዮአቭ ጋላንት ትዕዛዝ ሰጥተዋል።

    ጋዛ ሰርጥ ወደ 2.3 ሚሊዮን የሚጠጉ ፍልስጥኤማውያን መኖሪያ ስትሆን ለ16 ዓመታት ያህል የቆየ ከበባ ውስጥ ትገኛለች።

  17. ሐማስ በእስራኤል ላይ ለፈጸመው ጥቃት ምክንያቱ ምንድን ነው?

  18. በእስራኤል የሚገኙ ኤርትራውያን ተጎጂዎችን ለመርዳት አልባሳት እያሰባሰቡ ነው

  19. የእስራኤል ጦር በጋዛ ድንበር 35 ክፍለ ጦር ማሰማራቱን አስታወቀ

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል በጋዛ ሰርጥ ድንበር 35 ክፍለ ጦር ማሰማራቱን አስታውቋል።

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ላይ እየፈጸመቻቸው ካሉ የአየር ጥቃቶች በተጨማሪ በምድር ላይ ከፍተኛ ወታደራዊ ጥቃት በቅርቡ ትጀምራለች ተብሎ ይጠበቃል።

    “ለወደፊት ለሚደረገው ዘመቻ መንገድ እያመቻቹ መሆናቸውንም” የሰራዊቱ ቃለ አቀባይ ሪቻርድ ሄክት ተናግረዋል።

    አንድ ክፍለ ጦር በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን ይዟል።

    የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በጋዛ ላይ እየተፈጸሙ ያሉ የአየር ጥቃቶች ገና እየጀመሩ መሆናቸውን አስታውቀዋል።

  20. እስራኤል በጋዛ የስደተኞች ካምፕን በአየር ደበደበች

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ በስተሰሜን በሚገኘው የጃባሊያ የስደተኞች መጠለያ ካምፕ ላይ የአየር ጥቃት ፈጸመች።

    በዚህም የአየር ጥቃት ቢያንስ 15 ሰዎች መሞታቸውን የፍልስጥኤም ባለስልጣናት ተናግረዋል።

    እስራኤል ገና የመጀመሪያው ነው ባለችው ተከታታይ የአየር ጥቃቶች በርካታ ህንጻዎች መውደማቸውን ከአካባቢው የወጡ ምስሎች አሳይተዋል።

    የእስራኤል አየር ኃይል በአንድ ምሽት 200 የታጣቂ ኢላማዎችን መምታተቱን አስታውቋል።

    ከቅዳሜ ጀምሮ በቀጠለው የአየር ጥቃቶች ወደ 700 ሰዎች መገደላቸውን የአካባቢው ባለስልጣናት አስታውቀዋል።