በኢትዮጵያ በ704 ሰዎች ላይ ቫይረሱ ተገኝቶ ከፍተኛው የህሙማን ቁጥር ተመዘገበ

የኮሮናቫይረስ የማኅበረሰብ ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ባለባት ኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 10 ሺህ 207 ደርሷል። ከእነዚህም ውስጥ 5 ሺህ 237 አገግመዋል። አገሪቱ እስካሁን 170 ዜጎቿን በኮሮናቫይረስ አጥታለች። በኢትዯጵያ እስካሁን ድረስ 331 ሺህ 266 ምርመራዎች መከናወናቸውን ከጤና ሚኒስቴርና ከሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት መግለጫ የተገኘው መረጃ ያሳያል። በሕብረተሰቡ ዘንድ መዘናጋት እየተስተዋለ በመሆኑ ሕዝቡ በሽታውን የመከላከያ መንገዶች ተግባራዊ በማድረግ እራሱንና ሌሎችን ከወረርሽኙ እንዲጠብቅ ባለሙያዎች እየመከሩ ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ 302 ሺህ 728 የኮሮናቫይረስ ምርመራዎች ተደርገዋል

    ባለፉት 24 ሰዓታት 5 ሺህ186 ናሙናዎች የኮቪድ-19 ምርመራ እንደተደረገላቸው ተገለፀ። ከእነዚህም መካከል 294 ሰዎች ላይ ኮሮናቫይረስ መገኘቱን የጤና ሚኒስቴርና የህብረሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ ባወጡት መግለጫ ላይ አመልክተዋል።

    በአዲስ አበባ 209፣ ኦሮሚያ 13፣ ትግራይ 31፣ ጋምቤላ 20፣ አማራ 9፣ አፋር 6፣ ድሬዳዋ፣ 4፣ ሶማሊ 2፣ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎችን አስመዝግበዋል።

    በአሁኑ ሰዓት በጽኑ ሕሙማን የሚገኙ ሰዎች ቁጥር 36 ሲሆን ከሕመሙ ሙሉ በሙሉ ያገገሙ ደግሞ 51 መሆናቸው በመግለጫው ላይ ተመልክቷል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ሁለት ሰዎች ሲሞቱ አንዱ ግለሰብ በአፋር ህክምና ክትትል እየተደረገለት የነበረ መሆኑ ሲነገር ቀሪው ግለሰብ ደግሞ በአዲስ አበባ ከአስክሬን ላይ በተወሰደ ናሙና መገኘቱ ተገልጿል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ 4768 ሰዎች ከኮቪድ-19 ሲያገግሙ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ደግሞ 148 ደርሷል።

    በመላው ኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ከ300 ሺህ በላይ የኮሮናቫይረስ ምርመራዎች የተደረጉ ሲሆን ከእነዚህም መካከል 8 ሺህ 475 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ታውቋል።

  2. የአሜሪካ ሆስፒታሎች ለሲዲሲ ሳይሆን ለትራምፕ አስተዳደር ሪፖርት እንዲያደርጉ ታዘዙ

    የአሜሪካ ሆስፒታሎች ከዛሬ ጀምሮ የኮቪድ-19 ሕሙማንን መረጃ ለበሽታ መቆጣጠር ማእከል (ሲዲሲ) ሳይሆን ለፌደራል ጤና ኤጀንሲ እንዲያቀርቡ መታዘዛቸው ተገለፀ።

    ሲዲሲ የአሜሪካ ሕብረተሰብ ጤናን የሚመራ ተቋም ሲሆን ከዚህ ቀደም በአሜሪካ የሚከሰቱ ወረርሽኞችን የሚመለከቱ መረጃዎችን ይይዝ ነበር።

    የጤና ባለሙያዎች አዲሱን ውሳኔ ተከትሎ መረጃዎች ፖለቲካዊ አንድምታ ይሰጣቸዋል፣ ግልፅ የመሆን እድላቸው ያነሰ ይሆናል እንዲሁም የተመራማሪዎችን ሥራ ያደናቅፋል ሲሉ ስጋታቸውን ገልፀዋል።

    እንደ ኒውዮርክ ታይምስ ዘገባ ከሆነ የአሜሪካ የጤናና ሰዎች አገልግሎት ክፍል (ኤችኤችኤስ) መረጃዎቹን የሚይዝ ሲሆን ለሕዝቡም ክፍት አይደረግም ተብሏል።

    የኤችኤችኤስ ቃል አቀባይ ማይክል ካፑቶ እንዳሉት የሲዲሲ ስርዓት መረጃዎችን ለመያዝ በቂ አለመሆን ብቻ ሳይሆን የአንድ ሳምንት መዘግየት አለበት ብለዋል።

    “ዜጎች ኮሮናቫይረስን ለማሸነፍ የሚፈልጉት አዲሱን፣ ፈጣንና የተሟላ መረጃ ነው ከአሁን በኋላ ሲዲሲ፣ በኤችኤች ኤስ ስር የሚንቀሳቀሰው ተቋም፣ ውጤታማ በሆኑ የመንግሥት ምላሾች ላይ የሚሳተፍ ሲሆን መረጃዎችን ግን እንዲይዝ አይደረግም” ብለዋል።

    ይህ ለውጥ በህብረተሰብ ጤና ባለሙያዎችና በዋይት ሃውስ መካከል ያለውን ውጥረት አክርሮታል።

    ማክሰኞ እለት የቀድሞው የሲዲሲ ዳይሬክተር ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኮቪድ-19 የሚሰጡትን ምላሽ “አሳዛኝ ክስተት” በማለት የተቹ ሲሆን” የአሜሪካ ሕዝብ አመራር፣ ክህሎትና ግልጽነት በሚፈልግበት ወቅት ግራ መጋባት ተዘርቷል” ብለው ነበር።

  3. ደቡብ አፍሪካ የማዕድን ማውጫዎቿን ወደ ሥራ እየመለሰች ነው

    የማዕድን ማውጣት ላይ የተሰማሩ 300 ሞዛምቢካውያ ንሠራተኞች ሥራቸውን ለመጀመር ወደ ደቡብ አፍሪካ ማቅናታቸው ተገለፀ።

    በርካቶቹ ሥራቸውን አቋርጠው ወደ አገራቸው የተመለሱት በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በተጣለው እገዳ ምክንያት ነበር።

    በአስር ቀን ውስጥ ወደ ደቡብ አፍሪካ ተመልሰው ሥራቸውን እንዲጀምሩ ከተነገራቸው የማዕድን አውጪዎች መካከል ይህ ሁለተኛው ቡድን ነው ተብሏል።

    መጀመሪያ የተጠራው ከ200 በላይ ሠራተኞችን የያዘው ቡድን ወደ ደቡብ አፍሪካ የተመለሰው ሰኞ እለት ነበር።

    ሠራተኞቹ ወደ ሥራ ከመግባታቸው በፊት ከኮቪድ-19 ነጻ መሆናቸውን ለማረጋገጥ የ14 ቀን ለይቶ ማቆያ እንደሚከርሙ ተገልጿል።

    ጁካ ባታ የሞዛምቢክ ብሔራዊ የስደተኞች አገልግሎት ቃል አቀባይ ሲሆኑ ሠራተኞቹ በሙሉ ተመርምረው ከኮሮናቫይረስ 19 ነጻ መሆናቸው ተረጋግጧል ብለዋል። ደቡብ አፍሪካ ከደረሱ በኋላም ዳግም እንደሚመረመሩ ታውቋል።

    በደቡብ አፍሪካ 12 ሺህ ያህል ሞዛምቢካውያን የማእድን ማውጣት ስራ ላይ ተሰማርተዋል።

    ደቡብ አፍሪካ የማእድን ማውጫዎቿን ሙሉ በሙሉ የዘጋችው ባለፈው መጋቢት ወር ሲሆን ከዚያ ወዲህ የተጣለው ገደብ ቀስ በቀስ እየላላ መጥቷል።

    • የኒውዮርክ ከተማ ቡጢኞች

      የኒውዮርክ ከተማ ክብርና ዝና ያተረፈበትን የቦክስ ስፖርትን በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በርካታ ስፖርት ማዘውተሪያዎች በመዘጋታቸው ለአንዴና ለመጨረሻ ሊዘጋ እንደሚችል ቡጢኞቹ ተናገሩ።

      ከተማዋ የኮሮናቫይረስ ስርጭት ለመግታት ስፖርት ማዘውተሪያዎችን ብትዘጋም ኮቪድ-19 በመከላከል መመሪያው ላይ እንዴትና መቼ እንደሚከፈቱ የተቀመጠ ነገር አለመኖሩ ቡጢኞቹን ፈተና ውስጥ ጥሏል።

      የኒውዮርክ ከተማ ስመጥር ቡጢኞች እንዳሉት በኮሮናቫይረስ ምክንያት ግጥሚያዎች ባለመካሄዳቸውና የልምምድ ስፍራዎች በመዘጋታቸው ራሳቸውን በገቢ ለመደጎም ፈተና ገጥሟቸዋል።

      በስፖርቱ ውስጥ ሶስት አስርታትን ያሳለፈችው ብሩስ ሲልቨርግሌድ የቦክስ ስፖርት ፖለቲከኞች ጭምር ወደ ጎን እንደተገፋ እና ሌላ አማራጭ ወደማየት መሄዳቸውን ተናግራለች።

    • የኮቪድ-19 ክትባትን ለማግኘት ምን ያህል ጊዜ ይፈጃል?

      የኮሮናቫይረስ ክትባት ሙከራ ውጤቶች በባዮቴክኖሎጂ ኩባንያው ሞደርና ይፋ የተደረጉ ሲሆን ነገር ገን ጊዜያዊ መሆናቸው ተገልጿል።

      ሞደርና 45 ሰዎች ላይ ያደረገውን የክትባት ሙከራ ይፋ አድርጎ ነበር። የዚህ የምርምር ሙከራ ውጤት ወስዶ የትኛውም ድርጅት መደምደሚያ መስጠት ስህተት መሆኑ ተጠቅሶ ነገር ግን ተመራማሪዎቹ በሚያደርጉት የኮቪድ-19 ክትባት ሙከራ በትክክለኛው ጎዳና ላይ መሆናቸውን ያሳያል ተብሏል።

      ሞደርና የሚያደርጋቸውን የኮቪድ-19 ክትባት ሙከራዎች ውጤት በበርካታ ሰዎች ላይ ተሞክሮ መስራት አለመስራቱ መረጋገጥ እንደሚኖርበት ተነግሯል።

      ሞደርና የሚያካሂደው ጥናት ሜሴንጀር አርኤንኤ የሚባል ዘዴን የሚጠቀም ሲሆን የመከላከል ብቃትን በማነቃቃት በቤተሙከራ ውስጥ የተወሰዱትን የቫይረሱን ናሙናዎች ላይ ተሞክሮ ውጤታማ መሆኑ ተነግሯል።

      ነገር ግን ሰዎች ላይ ተሞክሮ ተመሳሳይ ውጤት ማምጣት አለማምጣቱ፣ እንዲሁም ሰዎች እንዳይታመሙ መከላከል አለመከላከሉ መረጋገጥ አለበት ተብሏል።

      ኩባንያው ሙከራውን ያደረገው 45 ሰዎች ላይ ሲሆን የተወሰኑት ግለሰቦች በወሰዱት መድሃኒት የተነሳ ከፍተኛ የጎንዮሽ ጉዳት ማስተናገዳቸው ተገልጿል።

      የጎንዮች ጉዳቱ የመጣው ከፍተኛ መጠን ያለው መድሃኒት የወሰዱት ላይ ሲሆን፣ ለዚህም መፍትሄ መገኘት እንዳለበት ተጠቅሷል።

      እስካሁን ድረስ በመላው ዓለም ለኮሮናቫይረስ መድሃኒት ለማግኘት የሚደረጉ ምርምሮች 200 የደረሱ ሲሆን፣ የሳይንቲስቶች ቡድን ከምን ጊዜውም የበለጠ ትኩረቱን አድርጎ እየሰራ ነው ተብሏል። ነገር ግን ያሉ ተግዳሮቶች ታልፈው ውጤት እስኪገኝ ድረስ ወራት ሊቆጠሩ ይችላሉ የሁሉም የጤና ባለሙያዎችና የተመራማሪዎች ቃል ነው።

    • በኮሮናቫይረስ ዳግም ከመያዝ እንድን ይሆን?

    • የቤልጄም ጤና ሚንስትር ማስክ ብዙዎችን እያነጋገረ ነው

      የቤልጄም ጤና ሚንስተር የፊት እና አፍ መሸፈኛ ጭምብል ብዙዎችን ያነጋገረ እና ፈገግ ያሰኘ ሆኗል።

      ሚንስትሯ ማጊ ዲ ብሎክ ከአፍንጫቸው እስከ አገጫቸው ያለው የሰውነት ክፍላቸው የታተመበትን ፊት እና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል አድርገው ከፓርላማ ተገኝተዋል።

      በርካቶች የጤና ሚንስትሯ ጭምብል ፈገግ እንዳሰኛቸው ገልጸዋል።

      ካሳለፍነው ቅዳሜ ጀምሮ የቤልጄም መንግሥት ሰዎች ከቤታቸው ሲወጡ ማስክ ማድረግ ግዴታ ነው ሲል አውጇል።

    • የኮቪድ -19 ሐሰተኛ የምስክር ወረቀቶችን የሰጡ የሆስፒታል ባለቤት በቁጥጥር ሥር ዋሉ

      የባንግላዴሽ ፖሊስ ከኮቪድ -19 ነፃ መሆንን የሚያሳዩ ሐሰተኛ የህክምና የምስክር ወረቀቶችን ሰጥተዋል ያላቸውን የአንድ ሆስፒታል ባለቤት ማሰሩን አስታወቀ።

      ሞሃመድ ሻሄድ የተባሉት ግለሰብ ማንነታቸውን በመደበቅ ወደ ሕንድ ለመሻገር ሲሞክሩ መያዛቸውን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

      ግለሰቡ በቁጥጥር ሥር የዋሉት ከባንግላዴሽ ወደ ሌሎች አገራት የሚጓዙ ሰዎች ከቫይረሱ ነፃ መሆናቸውን የሚያሳይ የምስክር ወረቀት በእጃቸው ቢይዙም፤ በደረሱበት ወቅት ሲመረመሩ ግን ቫይረሱ እንዳለባቸው በመረጋገጡ እና ጣልያንን ጨምሮ በርካታ አገራት ከባንግላዴሽ የሚደረጉ በረራዎች ላይ ገደብ መጣላቸውን ተከትሎ ነው።

      በዚህም ምክንያት የአገሪቷ ባለሥልጣናት በበርካታ ሆስፒታሎች ላይ ጥብቅ የሆነ ምርመራ በማካሄዳቸው ነበር ሐሰተኛ የምስክር ወረቀት የሚሰጥ ሆስፒታል መኖሩን የደረሱበት።

      የሆስፒታሉ ባለቤት በዋና መዲናዋ ዳካ የሚገኘው ሬጀንት የግል ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅም ናቸው።

      ከዚህ ቀደም ሌላ ዶክተር በተመሳሳይ ወንጀል በቁጥጥር ሥር ሆኖ ምርመራ እየተደረገበት ይገኛል።

    • ማርከስ ራሽፎርድ የክብር ዶክትሬት ሊበረከትለት ነው

      የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን እና የማንችስተር ዩናይትድ የፊት መስመር ተጫዋች ማርከስ ራሽፎርድ ከማንችስተር ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ሊበረከትለት ነው።

      ይህም ራሽፎርድን ከማንችስተር ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ያገኘ በእድሜ ትንሹ ያደርገዋል።

      የ22 ዓመቱ እግር ኳስ ተጫዋች ይህ ክብር እንዲሰጠው ያደረገው መንግሥት አቅም ለሌላቸው ልጆች በትምህርት ቤት የምገባ ፕሮግራም እንዲቀጥል ጫና ማሳደሩን ተከትሎ ነው።

      በእንግሊዝ የእቅስቃሴ ገደብ ተጥሎ በነበረበት ወቅት መንግሥት ለተመረጡ የቤተሰብ አባላት የነጻ ምግብ ኩፖኖችን ሲያድል የቆየ ሲሆን፤ የአገሪቱ መንግሥት በተደጋጋሚ ይህ ድጋፍ የሚዘልቀው የእንቅስቃሴ ገደቡ እስኪነሳ ድረስ ብቻ እንደሆነ አስታውቆ ነበር።

      ይሁን እንጂ ራሽፎርድ ሌሎችን በማስተባበር መንግሥት ላይ ጫና በመፍጠር ለተማሪዎች ነጻ የምግብ አቅርቦቱ እንዲቀጥል አድርጓል።

      “ማርከስ ከእግር ኳስ ሜዳ በዘለለ ልዩ ክህሎት ያለው ወጣት ነው” በማለት የማንችስተር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ፕሮፌሰር ዴም ኔንሲ ሮዝዌል ተናግረዋል።

      ራሽፎርድ በበኩሉ፤ “ይህ ለእኔ እና ለቤተሰቤ የኩራት ቀን ነው” ብሏል።

      ከዚህ ቀደም የማንችስተር ዩናይትድ የምንጊዜም ምርጦች ሰር አሌክስ ፈርጉሰን እና ሰር ቦቢ ቻርልተን ከዚህ ቀደም ይህን የክብር ዶክትሬት ከዩኒቨርሲቲው ተቀብለው ነበር።

    • በዩናይትድ ኪንግደም ሪኮርድ በሆነ መጠን ሚሊዮኖች ማጨስ አቆሙ

      የዩናትድ ኪንደም አጫሾች ሪከርድ በመሆነ አሃዝ ሚሊዮኖች ሲጋራ ማጨስ ማቆማቸው ተነገረ።

      አክሽን ኦን ስሞኪንግ & ሀልዝ የተሰኘውድ በጎ አድራጊ ድርጅት አካሄድኩት ባለው የዳሰሳ ጥናት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ከተቀሰቀሰ በኋላ በዩናይትድ ኪንግደም ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ሲጋራ ማጨስ አቁመዋል ብሏል።

      ባለፉት 4 ወራት ውስጥ ማጨስ ካቆሙ ሰዎች መካከል 41 በመቶ የሚሆኑት ማጨስ ያቆምነው በኮሮናቫይረስ ምክንያት ነው ብለዋል።

      'ሲጋራ ማጨስ ከኮሮናቫይረስ ጋር ተደማምሮ የጤና ችግር ሊያስከትል ይችላል'፣ 'በወረርሽኙ ወቅት የእንቅስቃሴ ገደብ ስለተጣለ ሲጋራ ማግኘት ስላልቻልኩ ማጨስ አቆምኩ' እንዲሁም 'ከሌሎች ነገር የማጨስ እድል ስላልነበረኝ ማጨስ አቆምኩ' የሚሉ ምክንያቶች መሰጠታቸውን የዳሰሳ ጥናቱ አመላክቷል።

      የጤና ባለሙያዎች አጫሾች ከፍተኛ የሆነ የኮቪድ-19 ምልክቶች ሊታይባቸው ይችላል ሲሉ ያስጠነቅቃሉ።

    • የዩናይትድ ኪንግደም ጤና ሚኒስትር በቢሮዎች ውስጥ ማስክ እንዲደረግ አዘዙ

      የዩናይትድ ኪንግደም ጤና ሚኒስትር ማት ሃንኮክ በቢሮዎችና በሥራ ቦታዎች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ አስገዳጅ እንደሆነ ተናገሩ።

      ሚኒስትሩ "ሰዎች ቢሮ ውስጥ እና በትምህርት ቤቶች አንዳቸው ካንዳቸው ጋር ለረጅም ሰዓታት ይቀራረባሉ። በመሆኑም የፊት እና አፍ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ከሰዎች ጋር ለሚኖረን መሰል ግንኙነት ከበሽታው ለመጠበቅ ውጤታማ ነው" ብለዋል።

      ሚኒስትሩ ቢሮዎችና የሥራ ቦታዎች አካላዊ ርቀት መጠበቅን ጨምሮ ሌሎች የጥንቃቄ መመሪያዎች እንዳሏቸውም ገልፀዋል።

      በሕዝብ መጓጓዣ እና በሱቆች አካባቢ ሰዎች እስከመቼ ማስክ ማድረግ እንዳለባቸው የተጠየቁት ሚኒስተሩ ፤ ይህንን ጥያቄ መመለስ እንደማይቻል በመግለፅ፤ ነገር ግን “በቅርቡ ሊሆን ይችላል” ሲሉ መልሰዋል።

    • የቬንዙዌላ ዋና መዲና የእንቅስቃሴ ገደብ ልትጥል ነው

      ደቡብ አሜሪካዊቷ አገር ቬንዙዌላ በዋና መዲናዋ የእንቅስቃሴ ገደብ ልትጥል እንደሆነ አስታውቃለች።

      በዋና መዲናዋ ካራካስ እና ጎረቤቷ ሚራንዳ ግዛት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር የእንቅስቃሴ ገደብ እንደሚጣል የአገሪቱ ፕሬዚደንት ኒኮላ ማዱሮ በትዊተር ገፃቸው አስታውቀዋል።

      ገደቡም ከረቡዕ ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገልጿል።

      ፕሬዚደንቱ በትዊተር ገፃቸው ላይ እንዳስታወቁት በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ለመጨመሩ "በሕገ ወጥ መንገድ ወደ አገሪቷ በሚገቡ ሰዎች" ምክንያት ናቸው ብለዋል።

      እንደ ጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ መረጃ ከሆነ በአገሪቷ እስካሁን ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን፤ 96 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል። ይህ ከሌሎች የላቲን አሜሪካ አገራት፣ ፔሩና ብራዚል ጋር ሲነፃፀር ቁጥሩ እጅግ በጣም ዝቅተኛ ነው።

      ነገር ግን ቬንዙዌላ የወረርሽኙን ሥርጭት በተመለከተ የምታወጣው ሪፖርት፤ እየሆነ ካለው ያነሰ ነው የሚል ትችት ይቀርብባታል።

      ቬንዙዌላ ለዓመታት ካጋጠማት የምጣኔ ሐብት ቀውስና ማዕቀብ በኋላ የጤና ሥርዓቷ የተዳከመ ሲሆን የሚገጥሟትን የጤና ቀውሶች ለመቆጣጠር የሚያስችል አቅምም የላትም።

    • የደቡብ አፍሪካው ሚኒስተር በኮሮናቫይረስ ተያዙ

      የደቡብ አፍሪካ የማዕድን ሐብትና ኢነርጂ ሚኒስተር ግዌዴ ማንታሸ እና ባለቤታቸው በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተገለፀ።

      ጥንዶቹ እራሳቸውን ለይተው እያቆዩ ያሉ ሲሆን ሚኒስትሩ ከቤታቸው ሆነው ሥራቸውን እንደሚቀጥሉ ካቢኔው ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

      ሚኒስተሩ ወረርሽኙ ከተከሰተ አንስቶ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ሲያደርጉ ይህ ሦስተኛ ጊዜያቸው ነው።

      ሚኒስትሩ በመስሪያ ቤታቸው ያሉ ሰራተኞች እንዲመረመሩ አሳስበዋል ተብሏል።

      እንደ የዓለም ጤና ድርጅት ከሆነ በደቡብ አፍሪካ እስካሁን 287 ሺህ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን ይህም በአህጉሪቷ ካሉ አገራት ከፍተኛው ቁጥር ነው።

    • የአሜሪካ ኩባንያ ያመረተው የኮቪድ- 19 ክትባት የመጨረሻ የሙከራ ደረጃ ላይ ደረሰ

      የአሜሪካ የባዮቴክኖሎጂ ኩባንያ ሞደርና፤ የኮቪድ -19 ክትባት በሰዎች ላይ ለመሞከር ወደ ሚያስችለው የመጨረሻ ደረጃ የሙከራ ሂደት በሐምሌ ወር መጨረሻ ላይ እንደሚገባ አስታወቀ።

      ኩባንያው በሙከራው 30 ሺህ ሰዎችን ለማሳተፍ እንዳለመም ገልጿል።

      ክትባት ለማግኘት ዓመታትን የሚፈጅ በመሆኑ ምርምሩ እስከ ጥቅምት 2022 ድረስ እንደሚቀጥል ታውቋል።

      ኩባንያው አሁን የደረሰበትን የሙከራ ደረጃ ያስታወቀው ኒው ኢንግላንድ የህክምና ጆርናል የክትባቱን የመጀመሪያ ደረጃ ሙከራ ውጤት ይፋ ካደረገ በኋላ ሲሆን፤ በዚህ ሙከራ 45 የምርምሩ ተሳታፊዎች ሁሉም ቫይረሱን የመከላከል አቅም ( አንቲቦዲ) እንዳመረቱ አመላክቷል።

      የባዮቴክኖሎጂ ኩባንያ ሞደርና ቴራፒዩቲክስ በዓለማችን ካሉ ክትባት አምራች ድርጅቶች አንዱ ነው።

    • የትኞቹ አገራት በርካታ የኮቪድ-19 ተጠቂዎችን መዘገቡ?

      በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ በኮሮናቫይረስ ስርጭት ምክንያት ጉዳት ያልደረሰበት የዓለማችን ክፍል የለም።

      ኮቪድ-19 ዝቅተኛ ጉዳት ያስከተለባቸው አገራት እንዳሉ ሁሉ ከፍተኛ የምጣኔ ሃብት እና ማህበራዊ ቀውስ ያስከተለባቸው አገራት በርካታ ናቸው።

      ከጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ በተገኘው አሃዝ መሰረት በተጠቂዎች ብዛት እስከ 5ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት አገራት የሚከተሉት ናቸው።

      1ኛ. ዩናይትድ ስቴትስ - 3.42 ሚሊዮን

      2ኛ. ብራዚል - 1.92 ሚሊዮን

      3ኛ. ሕንድ - 906,752

      4ኛ. ሩሲያ - 738,787

      5ኛ. ፔሩ - 333,867

    • በሕንድ የወረርሽኙ ሥርጭት አሁንም እየጨመረ ነው

      በሕንድ የወረርሽኙ ሥርጭት እየጨመረ ሲሆን ባለፉት ሦስት ቀናትም በአንድ ቀን ከ28 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን የጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ መረጃ ያሳያል።

      በአገሪቷ እስካሁን ከ900 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ሲረጋገጥ በዚህም ከአሜሪካና ብራዚል ቀጥላ ከአለም አገራት በሦስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።

      ይሁን እንጂ ሕንድ ከእነዚህ አገራት ጋር ስትነፃፀር የሟቾች ቁጥር አነስተኛ ነው።

      በአጠቃላይ 23 ሺህ 727 ሰዎች በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን በሟቾች ቁጥር በ8ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።

      የወረርሽኙ ሥርጭትም በተለያየ ጊዜ በተለያዩ ግዛቶች ጭማሬ የሚያሳይ ሲሆን ከዚህ ቀደም በዴልሂእና ማሃራሽትራ ግዛት በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ ነበር።

      አሁን ደግሞ ትኩረቱ በደቡባዊ የአገሪቷ ግዛቶች ሆኗል።

    • በጀርመን በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው ተባለ

      ባለፉት ጥቂት ቀናት በጀርመን በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ ተነገረ።

      ከሮበርት ኮች ኢንስቲትዩት የተገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው ባለፉት 24 ሰዓታት 351 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

      በጀርመን እስካሁን 199,726 በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 9,071 ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

      ጀርመን በርካታ ምርመራዎችን በማከናወን እንዲሁም በበሽታው መያዛቸው ከተረጋገጡ ሰዎች ጋር ንክኪ አላቸው የተባሉ ሰዎችን በመለየት የቫይረሱን ስርጭት ለመቆጠጠር አስደናቂ ሥራ አከናውናለች በመባል ስትደነቅ ቆይታለች።

    • ኮሮናቫይረስ በሜክሲኮ በፍጥነት እየተዛመተ ነው

      የሜክሲኮ ጤና ሚንስቴር ባለፉት 24 ሰዓታት በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 7051 መሆኑን ይፋ አድርጓል። ጤና ሚንስቴሩ ጨምሮም 836 ሰዎች ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ ህይወታቸውን ማጣታቸውን አሳውቋል።

      ይህም በአገሪቱ በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርን 311,486 ያደረሰ ሲሆን እስካሁን 36,327 በቫይረሱ ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት ተዳርገዋል።

      የአገሪቱ መንግሥት በጤና ሚንስቴር በኩል በቫይረሱ የሚያዙ እና የሚሞቱ ሰዎች አሃዝ ሪፖርት ከሚደረገው በላይ ሊሆን እንደሚችል ያስጠነቅቃል።

    • የአልኮል ሽያጭ በታገደ ማግስት ሌቦች አልኮል መሸጫ መደብርን ዘረፉ

      የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝደንት የአልኮል ሽያጭን ባገዱ ማግስት ሌቦች አንድ የመጠጥ መደብር ሰብረው በመግባት ውስኪ ዘረፍው መሰወራቸው ተነገረ።

      “ከመደርደሪያው ላይ ውስኪ ብቻ መርጠው ነው የዘረፉት” ሲል በኬፕ ታወን የሚገኘው የአልኮል መጠጥ መሸጫ መደብር ባለቤት ማርክ ካሌንድ ለኒውስ24 ተናግሯል።

      ዘራፊዎቹ ወይን እና ሌሎች የመጠጥ አይነቶች አለመነካታቸውን የመደብሩ ባለቤት ተናግሯል።

      ፕሬዝደንት ሲሪያል ራማፎሳ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመቆጣጠር የአልኮል ሽያጭ እግድ የጣሉ ሲሆን የሰዓት እላፊም አውጀዋል።

      ለሁለተኛ ጊዜ በአልኮል ሽያጭ ላይ ተግባራዊ የተደረገው እገዳ በጤና ስርዓቱ ላይ የሚደርሰውን ጫና ያቃልላል ሲሉ ፕሬዝደንት ራማፎሳ ተናግረዋል።

      ደቡብ አፍሪካ ከአፍሪካ አገራት በኮሮናቫይረስ ክፉኛ የተጠቃች አገር ስትሆን እስካሁን ከ275 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን ከ4ሺህ በላይ የሚሆኑ ሰዎች ደግሞ ህይወታቸው አጥተዋል።

      እንደ አገሪቱ መንግሥት ቅድመ ግምት ከሆነ የያዝነው የፈረንጆቹ ዓመት መጠናቀቂያ ላይ በቫይረሱ ሳቢያ ህይወታቸውን ሊያጡ የሚችሉ ሰዎች ቁጥር 50ሺህ ሊደርስ ይችላል።

    • የረቡዕ ሐምሌ 08/2012 ዓ. ም. የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ

      እንደምን አደራችሁ የተከበራችሁ የቢቢሲ አማርኛ ተከታታዮች?

      ቢቢሲ አማርኛ በየዕለቱ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ጋር የተያያዙ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ መረጃዎችን በዚህ የቀጥታ ዘገባ ገፅ ያቀርባል።

      የዓለም ጤና ድርጅት አሁንም የጥንቃቄ እርምጃዎች ካልተተገበሩ ወረርሽኙ እየባሰ እንደሚሄድ በየጊዜው ያስጠነቅቃል።

      እኛም ከጤና ባለሙያዎች የሚሰጡ ምክሮችን ተግባራዊ በማድረግ ራሳችንና ማህበረሰባችንን ከወረርሽኙ እንጠብቅ መልዕክታችን ነው።

      አስተያየትና ጥቆማ ካላችሁም በፌስ ቡክ ገፃችን ብታደርሱን በአክብሮት እንቀበላለን።

      መልካም ቀን እንዲሆንላችሁ ተመኘን!