በኢትዮጵያ በ704 ሰዎች ላይ ቫይረሱ ተገኝቶ ከፍተኛው የህሙማን ቁጥር ተመዘገበ

የኮሮናቫይረስ የማኅበረሰብ ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ባለባት ኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 10 ሺህ 207 ደርሷል። ከእነዚህም ውስጥ 5 ሺህ 237 አገግመዋል። አገሪቱ እስካሁን 170 ዜጎቿን በኮሮናቫይረስ አጥታለች። በኢትዯጵያ እስካሁን ድረስ 331 ሺህ 266 ምርመራዎች መከናወናቸውን ከጤና ሚኒስቴርና ከሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት መግለጫ የተገኘው መረጃ ያሳያል። በሕብረተሰቡ ዘንድ መዘናጋት እየተስተዋለ በመሆኑ ሕዝቡ በሽታውን የመከላከያ መንገዶች ተግባራዊ በማድረግ እራሱንና ሌሎችን ከወረርሽኙ እንዲጠብቅ ባለሙያዎች እየመከሩ ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. የዕለተ ቅዳሜ ሐምሌ 11/2012 ዓ.ም የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ

    እንደምን አደራችሁ?

    ቅዳሜ ሐምሌ 11/2012 ዓ.ም

    በሽታውን ለመከላከል ከሚወሰዱ እርምጃዎች ውጪ ክትባትም ሆነ መድኃኒት ያልተገኘለት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የዓለም ሕዝብ ስጋት ከሆነ ሰነባብቷል።

    ከቢቢሲ አማርኛ በየዕለቱ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ዙሪያ ከኢትዮጵያና ከመላው ዓለም በየደቂቃው የሚወጡ ዜናና መረጃዎችን በተለይ በዚህ ገጽ ላይ በቀጥታ እናቀርባለን።

    ስለወረርሽኙ ጠቃሚ ትኩስ መረጃዎችን ለማግኘት በአመቻችሁ አጋጣሚ ሁሉ ይህንን የቀጥታ ዘገባ ገጽ እንድትከታተሉ እንጋብዛለን።

    በባለሙያዎች የሚመከሩ የበሽታውን የመከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ በማድረግ እራሳችሁንና ሌሎችን ከወረርሽኙ እንድትጠብቁ እያስታወስን መልካም ቅዳሜ እንዲሆንላችሁ እንመኛለን።

  2. የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በብራዚል በፍጥነት እንዴት ተስፋፋ?

  3. ጃፓን የአሜሪካ ወታደሮች ኮቪድ-19 እንዲመረመሩ ጠየቀች

    የጃፓን መከላከያ ሚኒስትር፣ ታሮ ኮኖ ወደ ጃፓን የሚመጡ የአሜሪካ ወታደሮች የኮሮናቫይረስ ምርመራ እንዲያደርጉ ጠየቁ።

    አሜሪካ፣ በአሁኑ ሰዓት የበሽታውን ምልክት ያሳዩ ግለሰቦችን ብቻ የምትመረምር ቢሆንም የሚኒስትሩን ሃሳብ በመቀበል እንደሚያስቡበት እንደነገሯቸው ግን ገልጸዋል።

    እስከ ሐሙስ ድረስ ብቻ 138 ወታደሮች በተለያዩ የጃፓን ግዛቶች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተገልጿል።

    በጃፓን ኦኪናዋ ግዛት፣ የአሜሪካ መከላከያ ኃይል የጦር ሰፈር አለው።

    ባለፈው ሳምንት የኦኪናዋ አስተዳዳሪ ዴኒ ታማኪ በግዛታቸው ጦር ሰፈር ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ወታደሮች የኮሮና መከላከያዎችን ቸል በማለታቸው ምክንያት ለቫይረሱ መጋለጣቸውን ገልፀው ነበር።

    እንደ አገረ ገዢው ከሆነ ወታደሮቹ የአሜሪካ የነጻነት በዓልን ለማክበር በባህር ዳርቻው ፓርቲ ማዘጋጀታቸውን፣ በከተማዋ ምሽት ክበቦችም ማሳለፋቸውን ጠቅሰዋል።

    በኦኪናዋ የሚኖሩ ጃፓናውያንና አሜሪካውያን ያላቸው ግንኙነት በውጥረት የተሞላ ነው።

    ለአመታት የአሜሪካ ጦር ሰፈር ከቦታው እንዲነሳ የአካባቢው ነዋሪዎች ሲጠይቁ ቆይዋል።

  4. የቤት ስራ ያልሰራችው ጥቁር አሜሪካዊቷ ተማሪ መታሰሯ ተቃውሞ ቀሰቀሰ

  5. በኮሮና የተነሳ ከሶስት ወር በላይ አገራቸው መግባት ያልቻሉ ሞዛምቢካውያን ትናንት መግባታቸው ተሰማ

    ከሚያዚያ ወር ጀምሮ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በተጣለ የእንቅስቃሴ ገደብ የተነሳ በፖርቹጋል ተቀምጠው የነበሩ 160 ሞዛምቢካውያን ትናንት መመለሳቸው ተገለፀ።

    በሞዛምቢክ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ስርጭትን ለመግታት ሁሉም ዓለም አቀፍ በረራዎች ታግደው ቆይተው ነበር።

    እገዳው አሁንም ያለ ቢሆንም በልዩ በረራ የፖርቹጋል አየር መንገድ ግለሰቦቹን ሐሙስ ማታ እንዲያመጣቸው ተደርጓል።

    አንዳንድ መንገደኞች ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኀን እንደተናገሩት ወደ አገራቸው በመመለሳቸው ደስተኛ ቢሆኑም የአውሮፕላን ትኬት ዋጋው ግን ውድ ነበር ብለዋል።

    የአንድ መስመር ጉዞ ዋጋ 1868 ዶላር እንደነበር ተናግረዋል።

    በዚህ ውድ የቲኬት ዋጋ የተነሳ ፖርቹጋል ውስጥ የቀሩ ሞዛምቢካውያን መኖራቸው ተሰምቷል።

    አብዛኞቹ ተመላሾች ፖርቹጋል የሄዱት ለሕክምና እና ለትምህርት እንደነበር ተናግረዋል።

  6. ፓኪስታን ዜጎቿን የኢድ በዓልን ቀለል አድርገው እንዲያከብሩ ጠየቀች

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር መጪውን ኢድ አል አድሃ ዜጎቻቸው ኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል እንዲቻል"ቀለል" አድርገው እንዲያሳልፉት ተማፀኑ።

    በፓኪስታን የኢድ በዓል የሐምሌ ወር መጨረሻ ላይ የሚውል ሲሆን አከባበሩም ለሳምንታት ይቆያል ። በዚህ ወቅት በርካታ ሰዎች ወደ ገጠር በመሄድ ከዘመድ ወዳጆቻቸው ጋር በመሆን በዓሉን ያከብራሉ።

    በረመዳን ወቅት በርካታ ፓኪስታናውያን የአካላዊ ርቀታቸውን ሳይጠብቁ በመቅረታቸው በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ከፍ ብሎ ነበር።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በትዊተር ገጻቸው ላይ በረመዳን ወቅት የተከሰተው እንዳይደገም በማለት ዜጎቻቸውን የተማፀኑ ሲሆን "ሆስፒታሎቻችን ተጨናንቀው ነበር" በማለት ሁናቴውን አስታውሰዋል።

    በፓኪስታን እስከ አሁንድረስ ከ5 ሺህ 470 በላይ ሰዎች በኮቪድ19 ምክንያት ሲሞቱ ከ260 ሺህ ሰዎች በላይ በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

  7. በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 9 ሺህ 147 ደረሰ

    ኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት ለ7 ሺህ 407 የኮቪድ-19 ምርመራ በማድረግ 344 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን ማረጋገጧን ገለፀች።

    ይህም በአጠቃላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 9 ሺህ147 አድርሶታል።

    ጤና ሚኒስትርና የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ ባወጡት እለታዊ መግለጫ ላይ እንዳሰፈሩት በአዲስ አበባ 206 ሰዎች ሲያዙ፣ በኦሮሚያ 31፣ በትግራይ 29፣ በአፋር 22፣ በሶማሊ 15፣ በድሬዳዋ 14፣ በጋምቤላ ዘጠኝ፣ በሲዳማ ሰባት፣ በሐረሪ ሰባት፣ በደቡብ ክልል ሁለት፣ በአማራ ሁለት ሰዎች መያዛቸው ተመልክቷል።

    በአሁኑ ሰዓት የኮሮናቫይረስ በመያዛቸው ሕክምና እያገኙ ያሉ ግለሰቦች 4 ሺህ 082 ሲሆን 36 ሰዎች ደግሞ በጽኑ ህክምና ክፍል ውስጥ መሆናቸውን ተገልጿል።

    86 ሰዎች ከኮሮናቫይረስ ሲያገግሙ እስካሁን ድረስ ሙሉ በሙሉ ከቫይረሱ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 4 ሺህ 900 ደርሷል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ 13 ሰዎች ሲሞቱ ከእነዚህም መካከል ዘጠኙ ከአስከሬን ላይ በተደረገ ምርመራ መታወቁን፣ አራቱ ደግሞ የሕክምና ክትትል እያደረጉ የነበሩ ናቸው ተብሏል።

    የኮሮናቫይረስ በአገሪቱ ውስጥ መከሰቱ ከታወቀበት ጊዜ አንስቶ በኮቪድ-19 ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 163 ደርሷል።

    እስካሁን ድረስ ለ 317 ሺህ 046 ናሙናዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ተደርጓል።

  8. ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኮሮናቫይረስ ወረርሸኝ ምክንያት ተቀባይነታቸው እየወረደ ይሆን?

    በዋሺንግተን ፖስት እና በኤቢሲ ኒውስ የተደረገ የሕዝብ አስተያየት መመዘኛ አብዛኛው አሜሪካውያን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በሰጡት ምላሽ ደስተኛ አለመሆናቸውን አሳየ።

    አስተያየታቸውን ከሰጡ አሜሪካውያን መካከል 60 በመቶ ያህሉ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኮቪድ-19 ላይ የወሰዱትን እርምጃ ሲያጣጥሉ 38 በመቶ ያህሉ ደግሞ ይበል የሚያሰኝ ስራ ሰርተዋል ብለዋል።

    የፕሬዝዳንት ትራምፕ የኮሮናቫይረስ መከላከል ስራን ካጣጣሉት አሜሪካውያን መካከል 53 በመቶዎቹ በጣም የሚቃወሙ መሆናቸውም ተነግሯል።

    በአሜሪካ ከአስር ሰዎች መካከል ስድስቱ ፕሬዝዳንቱ ኮቪድ-19 በሚመለከት የሚሉትን ነገር እንደማያምኑ ተናግረዋል

    ከሁሉ የሚደንቀው ደግሞ ፕሬዝዳንቱ አባል የሆኑበት ሪፐብሊካን ፓርቲ ደጋፊዎችም መካከል ከ10 ሰዎች መካከል ሶስቱ ፕሬዝዳንቱ ኮሮናን በሚመለከት የሚናገሩትን ቃል ማመን ይቸገራሉ።

    በአሜሪካ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ቢሆንም ፕሬዝዳንት ትራምፕ ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱ በማለታቸው ከፍተኛ ትችትና ወቀሳ ቀርቦባቸዋል።

    ሌላው ፕሬዝዳንቱ ስማቸው የተብጠለጠለበት ምክንያት ለህብረተሰብ ጤና ባለሙያዎች ያላቸው አመለካከት ዝቅ ያለ ነው በሚል ነው።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የተሰራ ሌላ የሕዝብ አስተያየት መመዘኛ ፕሬዝዳንቱ የኮሮናቫይረስ መከላከልን እየጎዱት ነው የሚሉ ሰዎች ቁጥር 62 በመቶ መሆኑን ያሳየ ነበር።

  9. የሞዛምቢክ ፕሬዝዳንት በኮሮናቫይረስ መከላከል መመሪያዎች ላይ ጥብቅ መሆናቸውን አስታወቁ

    ፕሬዝዳንት ፊሊፔ ኒዩሲ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ተጥሎ የነበረው የእንቅስቃሴ ገደብ እንደማይነሳ አስታወቁ።

    ፕሬዝዳንቱ ሐሙስ ማታ ለዜጎቻቸው ባሰሙት ንግግር ከአሁን ጀምሮ ህዝብ በሚሰበሰብበት ስፍራ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ ግዴታ መሆኑን አስታውቀዋል።

    አክለውም ከ20 ሰው በላይ የሚገኝበት ስብሰባ እንደማይፈቀድ ተናግረዋል። ይህ ደግሞ ስፖርታዊ፣ ማህበራዊና ኃይማኖታዊ እንቅስቃሴዎች ላይም ተግባራዊ እንደሚሆን ተገልጿል።

    በሞዛምቢክ የሚገኙ የኃይማኖት አባቶች መንግሥት የጣለውን የእንቅስቃሴ ገደብ እንዲያነሳ ከፍተኛ ግፊት ሲያደርጉ ቆይተዋል።

    አንዳንድ የኃይማኖት አባቶች በአገሪቱ የእምነት ነጻነት ለማስፈን የሚያስችለው ረቂቅ ህግ ላይ እየተደረገ ያለውን ውይይት ቤተ እምነቶች እስካልተከፈቱ ድረስ አቋርጠው ለመውጣት እስከ ማስፈራራት ደርሰው ነበር።

    ነገር ግን ፕሬዝዳንቱ ለእነዚህ አካላት ማስፈራሪያ እጅ የሚሰጡ አልሆኑም። እንደውም ቤተ እምነቶች ንጽህናውና ደህንነቱ የተጠበቀ አገልግሎት ለምዕመናን እስካልሰጡ ድረስ ዝግ ሆነው እንደሚቆዩ ተናግረዋል።

    ይህ ክልከላ ትምህርት ቤቶችም ላይ ተግባራዊ እንደሚሆንም ተገልጿል።

    ፕሬዝዳንቱ በንግግራቸው ወቅት ትምህርት ቤቶች ከመከፈታቸው በፊት፣ አካላዊ ርቀትን ማስጠበቃቸው፣ በቂ ውሃና ንጽህና መጠበቂያ መሳሪያ ማቅረባቸውን ማረጋገጥ ያስፈልጋል ብለዋል።

    ነገ በዚህ ወር መጨረሻ ላይ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የሚያጠናቅቁ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ የተፈቀደ ቢሆንም የትምህርት ባለሙያዎች ግን ይህ እንደሚሆን ተስፋ የለንም ሲሉ ጥርጣሬያቸውን ገልፀዋል።

  10. በመጪው ጥቅምት ስታዲየሞች ለተመልካቾች ክፍት ሊደረጉ ይችላል ተባለ

  11. በኮሮናቫይረስ ምክንያት ታይቶ የማይታወቅ የምግብ እጥረት ሊያጋጥም ይችላል

  12. በርካታ የአሜሪካ ግዛቶች ማስክን የተመለከተ ደንብ አወጡ

    በአሜሪካ ወረርሽኙ መስፋፋቱን ተከትሎ በአገሪቷ ካሉ 50 ግዛቶች ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት የአፍና አፍንጫ መሸፈኛን የተመለከተ ደንብ አውጥተዋል።

    ሉዚያና ግዛት በቤት ውስጥም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግን ግዴታ ካደረጉ ግዛቶች አንዷ ናት።

    ከዚህም በተጨማሪ ዴሞክራቲኩ የግዛቷ አስተዳዳሪ ጆን ቤል ኤድዋርድስ በደቡብ ምስራቅ ባሉ ግዛቶች መጠጥ ቤቶች እንደሚዘጉ ተናግረዋል።

    ከዚህ ቀደም የኮሎራዶ ገዥ ጃረድ ፖሊስ በምዕራብ የግዛቷ አካባቢ የሚኖሩና እድሜያቸው ከ10 ዓመት በላይ የሆነ ማንኛውም ሰው ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው ቦታዎች የፊት ጭምብል ማድረጋቸውን እንዲያረጋግጡ አዘዋል።

    ነገር ግን ጉዳዩ አሁንም የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ የማድረግ ጉዳይ መነጋገሪያ መሆኑን ቀጥሏል።

    ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕም ወረርሽኙ ከጀመረ አንስቶ ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ አድርገው የታዩት ባለፈው ሳምንት ነበር። ፕሬዚደንቱ ከዚህ ቀደም ማስክ እንደማያደርጉ መናገራቸው ይታወሳል።

  13. በአንድ የቻይና ግዛት አንዲት ሴት በቫይረሱ መያዟን ተከትሎ በርካታ በረራዎች ተሰረዙ

    በቻይና ዥንጂያንግ ግዛት ዋና ከተማ ኡርምቂ በከሮናቫይረስ የተያዘ ሰው መገኘቱን ተከትሎ ከ600 በላይ በረራዎች መሰራዛቸው ተገለፀ።

    በቫይረሱ የተያዘችው የ24 ዓመት ሴት ስትሆን፤ የበሽታው ምልክት ከታየባት በኋላ ሐሙስ ዕለት በቫይረሱ መያዟ በምርመራ ተረጋግጧል።

    ከእርሷ ጋር የቅርብ ንክኪ የነበራቸው ሌሎች ሦስት ሰዎችም ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል። ይሁን እንጅ ግለሰቦቹ የበሽታው ምልክት አልታየባቸውም።

    በዚህ ሳቢያ በኡሩምቂ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የተሰረዘው በረራ በቀን ውስጥ ከሚደረገው በረራ ከ80 በመቶ በላይ እንደሆነም ተነግሯል።

    ከአርብ ዕለት ጀምሮም ጁኔያዎን እና ሸንዠን ዶንጋይን ጨምሮ በርካታ አየር መንገዶች ወደ ከተማዋ የሚገቡም ሆነ የሚወጡ መንገደኞች በሰባት ቀናት ውስጥ ያደረጉትን ‘ከኑክሊክ አሲድ’ ነፃ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ መረጃ እንዲያሳዩ መጠየቅ ጀምረዋል።

    ከዚህም ባሻገር መንገደኞች ቫይረሱ ሊኖርባቸው የሚችሉ ሰዎችን ለመለየት በተዘጋጀው መተግበሪያ ላይ ለመጓዝ ደህና መሆናቸውን የሚያመለክት የጤና ኮድ ማሳየት እንደሚጠበቅባቸው የቻይና ግሎባል ታይምስ ዘግቧል።

    የቻይና ምስራቃዊ አየር መንገዶች እነዚህን ደንቦች ተግባራዊ ያደርጋሉ። ኡሩምቂ ከተማም የከተማዋን የባቡር አገልግሎት ሐሙስ ዕለት አግዳለች።

    የአገሪቷ የጤና ባለሥልጣን እንዳስታወቀው በቻይና አርብ ዕለት 10 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች የተመዘገቡ ሲሆን፤ ከእነዚህ መካከል ዘጠኙ ከውጪ የገቡ ሰዎች ናቸው።

  14. ብሪቲሽ ኤርዌይስ ቦይንግ 747 አውሮፕላኖቹን ከአገልግሎት አስወጣ

    ብሪቲሽ ኤርዌይስ የመንገደኞች ቁጥር መቀነሱን ተከትሎ ሁሉንም ቦይንግ 747 አውሮፕላኖቼን ከአገልግሎት ለማስወጣት ተገድጃለሁ አለ።

    በኮሮናቫይረስ ስርጭት ምክንያት በዓለም ዙሪያ የተጣሉ የጉዞ ገደቦች አየር መንገደኞችን ክፉኛ ጎድቷል።

    “ሁሉም ቦይንግ 747 አውሮፕላኖቻችን በአስቸኳይ ከአግልግሎት ውጪ እንዲደረጉ እንደተወሰነ ሳረጋግጥ በከፍተኛ ሃዘን ነው” ሲሉ የብሪቲሽ ኤርዌይስ ቃል አቀባይ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ግዙፉ የዩናይትድ ኪንግደም አየር መንገድ የሆነው ብሪቲሽ ኤርዌይስ 31 ቦይንግ 747 አውሮፕላኖች አሉት።

    ቃል አቀባዩ “የሰማይ ላይ ንግስቶች” ያሏቸው አውሮፕላኖችን ዳግም ወደ ሥራ የመመለስ እድል እንደሌላቸው ጨምረው ተናግረዋል።

  15. በጋና በሺዎች የሚቆጠሩ የጤና ባለሙያዎች በኮሮናቫይረስ ተያዙ

    በጋና ሁለት ሺህ ስልሳ አምስት የጤና ባለሙያዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን የአገሪቷ የጤና አገልግሎት አስታወቀ።

    የተቋሙ ዳይሬክተር ፓትሪክ ኩማ አቦግየ እንዳሉት በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋገጠው የጤና ባለሙያዎች መካከል ስድስቱ ሕይወታቸው ሲያልፍ 1 ሺህ 870 የሚሆኑት አገግመዋል።

    ቀሪዎቹ ደግሞ በለይቶ ማከሚያ ማዕከላት የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።

    የአገሪቷን ዋና መዲና አክራን በሚያካትተው የታላቋ አክራ ግዛት በቫይረሱ የተያዙ በርካታ የጤና ባለሙያዎች የተመዘገቡ ሲሆን፤ ባለሙያዎቹን ከወረርሽኙ ለመጠበቅ የበሽታ መከላከያ የህክምና ግብዓቶችን እያዳረሱ እንደሆነ ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    በጋና እስካሁን 26 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን 139 ሰዎች ደግሞ በበሽታው ሕይወታቸውን አጥተዋል።

    አገሪቷ እስካሁን 339 ሺህ 491 የኮሮናቫይረስ ምርመራ አድርጋለች።

  16. የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በብራዚል በፍጥነት እንዴት ተስፋፋ?

    በቫይረሱ ክፉኛ ከተጠቁ አገራት መካከል አንዷ ብራዚል ናት። ወረርሽኙ ከተከሰተበት መጋቢት ወር አንስቶ ከ2 ሚሊየን ሰዎች በላይ በቫይረሱ ተይዘዋል።

    እንደ ጤና ሚኒስቴር መረጃ ከሆነ አጠቃላይ ቁጥሩ 2 ሚሊየን 12 ሺህ 151 ነው። በዚህም ከአሜሪካ በመቀጠል በቫይረሱ ክፉኛ የተጠቃች ሁለተኛዋ የዓለማችን አገር ሆናለች።

    በቫይረሱ ሳቢያም ከ74 ሺህ በላይ ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል። በቂ ምርመራ ስላልተደረገ እንጂ ቁጥሩ ከዚህም ሊልቅ እንደሚችል ይታመናል።

    ለመሆኑ ቫይረሱ በደቡብ አሜሪካ አገራት እንዴት በፍጥነት ሊዛመት ቻለ?

  17. በሕንድ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከአንድ ሚሊዮን ተሻገረ

    በሕንድ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከአንድ ሚሊዮን ማለፉን እየወጡ ያሉ ሪፖርቶች ይጠቁማሉ።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ብቻ ከ30ሺህ በላይ ሰዎች ቫይረሱ እንደተገኘባቸው የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

    ለወራት በሕንድ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በተከታታይ እየጨመረ መጥቷል።

    ሕንድ ከአሜሪካ እና ብራዚል በመቀጠል በርካታ የቫይረሱ ተጠቂዎች ያሉባት አገር ሆናለች።

  18. አሜሪካ በአንድ ቀን በኮሮናቫይረስ የተያዙ ከፍተኛውን ቁጥር መዘገበች

    አሜሪካ በ24 ሰዓታት ውስጥ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ከፍተኛ ቁጥርን መመዝገቧ ተነገረ።

    ባለፉት 24 ሰዓታት ከ74,500 ሰዎች በምርመራ በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል። ይህም ወረርሽኙ ከጀመረ ወዲህ በአሜሪካ በአንድ ቀን በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ከፍተኛው ቁጥር ነው።

    በአገሪቱ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርም ከ3,570,000 በላይ እንዳደረሰው ከጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ የተገኘው አሃዝ ያሳያል።

    ኮቪድ-19 በአሁኑ ወቅት ከ30 በላይ የአሜሪካ ግዛቶች በፍጥነት እየተዛመተ ይገኛል።

    ባለፉት 24 ሰዓታትም ከ1ሺህ በላይ አሜሪካውያን በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸውን አጥተዋል። እስካሁን በጠቅላላው ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች ብዛት ከ138ሺህ በላይ ሆኗል።

  19. የዕለተ አርብ ሐምሌ 10/2012 ዓ.ም የቢቢሲ አማርኛ ቀጥታ ዘገባ

    እንደምን አደራችሁ የተከበራችሁ ተከታታዮቻችን?

    ቢቢሲ አማርኛ ከዚህ ሰዓት ጀምሮ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ ኮሮናቫይረስን የተመለከቱ ዘገባዎችን በቀጥታ ዘገባ ገጹ ወደ እናንተ ማድረሱን ጀምሯል።

    በአህጉር አፍሪካ እስካሁን 663 ሺህ 912 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን ከእነዚህ መካከል 343 ሺህ 409 ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል። 14 ሺህ 359 ሰዎች ደግሞ በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸውን አጥተዋል።

    በኢትዮጵያም በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 8803 መድረሱን የጤና ሚኒስቴር ትናንት ባወጣው ሪፖርቱ ገልጿል። የወረርሽኙ ደረጃም በአስጊ ሁኔታ ላይ መሆኑን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መርማሪ ቦርድ አስታውቋል።

    ከጤና ባለሙያዎች የሚሰጡ የጥንቃቄ መልዕክቶችን ተግባራዊ በማድረግ ራሳችንንና ማሕበረሰባችንን ከኮሮናቫይረስ እንጠብቅ መልዕክታችን ነው።

    መልካም ቀን!

  20. ወረርሽኙ በኢትዮጵያ ውስጥ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል ተባለ

    የኮሮናቫይረስ ስርጭት በኢትዮጵያ አሳሰቢ ደረጃ ላይ መድረሱን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መርማሪ ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ጴጥሮስ ወልደሰንበት ለፋና ገለጹ።

    በተለይ በወጣቶች እንዲሁም በሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ላይ የቫይረሱን ስርጭት ለመከላከል የሚያስፈልጉ ጥንቃቄዎችን በመተግበር በኩል ከፍተኛ መዘናጋት እንደታየ ሰብሳቢው ተናግረዋል።

    ይሄንን ተከትሎም የከፋ አደጋ እንዳይከሰት ቦርዱ መንግሥት የማስተካከያ እርምጃዎችን እንዲወስድ ሀሳብ ማቅረቡን ጠቅሰው፤ የሚሰጠውን ትምህርት ከማጠናከር በተጨማሪ ሕጋዊ እርምጃዎችን መውሰድ አስፈላጊ የሆነበት ጊዜ መድረሱንም ገልጸዋል።

    አቶ ጴጥሮስ ወልደሰንበት እንዳሉት ኮሮናቫይረስን ለመከላከል የሁሉንም ሰው አስተዋጽኦ የሚጠይቅ መሆኑን ጠቅሰው በተለይም ወጣቶች አስፈላጊውን ወረርሽኙን የመከላከያ መንገዶች ሳይዘናጉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ መክረዋል።