ኮሎምቢያዊያን በቤታቸው ደጅ ለምን ቀይ ጨርቅ ይሰቅላሉ?
በደቡብ አሜሪካዊቷ አገር ኮሎምቢያ እስካሁን ከ165 ሺህ ሰዎች በላይ በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን፤ 5 ሺህ 800 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል።
በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥርም እየጨመረ በመሆኑ የተጣሉ ገደቦች ለተጨማሪ ሁለት ሳምንታት እንዲራዘሙ ተደርጓል።
ይህ ደግሞ ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ ለሆነው የኅብረተሰብ ክፍል ያለ ምንም ገቢ የሚቆዩበት ተጨማሪ ጊዜ ሆኗል።
ታዲያ እነዚህ የማኅበረሰብ ክፍሎች በሚኖሩባቸው መንደሮች ሰዎች ቀይ ጨርቅ በእንጨት አስረው ደጃቸው ላይ ይሰቅላሉ።
ይህን ማድረጋቸው መንግሥት እርዳታ እንዲያደርግላቸው ለመጠየቅ ነው።
የኮሎምቢያ ዋና መዲና ቦጎታ ጎረቤት በሆነችው ላ ፔርሰቨራንሲያ የምትኖረው ክላውዲያ፤ ቆሻሻዎችን በመሰብሰብና እንደገና ጥቅም ላይ በማዋል ሥራ ነው የምትተዳደረው።
"ወረርሽኙ በተከሰተበት ወቅት ማናችንም ሥራ አንሰራም ነበር። ማንም ዞር ብሎ ያየንም አልነበረም" በማለት እርዳታ ለመጠየቅም ቀይ ጨርቅ በደጃቸው ማንጠልጠላቸውን ለቢቢሲ ተናግራለች።
አሁንም ግን ከመንግሥት የተደረገላቸው እርዳታ እንደሌለ ገልፃለች።
ሌላኛዋ በሶአቻ የምትኖረው የአምስት ልጆች እናትም ከመንግሥት ያገኘችው ድጋፍ እንደሌለ ትናገራለች።
"ለቁርስ የምንመገበው ብናገኝ፤ ምሳ አናገኝም፤ ልጆቹም እየከሱ ነው" ስትል ችግር ውስጥ መሆናቸውን አስረድታለች።