በአሜሪካ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር 1 ሚሊዮን ደረሰ

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ከዓለማችን ላይ የሚጠፋ አለመሆኑ በተደጋጋሚ ይነገራል። እስካሁን ባለው መረጃ ከ3 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ሲያዙ በሺዎች የሚቆጠሩም ህይወታቸውን አጥተዋል። አንዳንድ አገራት ጥለውት የነበረውን የእንቅስቃሴ ገደብ እያነሱ ቢሆንም አሁንም ግን ዜጎቻቸው ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልጋቸው እየተናገሩ ነው። በእኛም አገር አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ እጅን በሳሙናና በውሃ መታጠብ ሊዘነጉ የሚገባቸው አይደሉም። እናንተም ጤና ወዳጆቻችሁም ደህና እንዲሆኑ ምኞታችን ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ስኮትላንድ ውስጥ የሟቾች ቁጥር 2ሺህ ዘለለ

    ስኮትላንድ ውስጥ ተጨማሪ 656 ሰዎች በኮቪድ-19 ሳቢያ ሕይወታቸውን አጥተዋል። ይህ የጠቅላላ ሟቾችን ቁጥር 2272 አድርሶታል።

    ስኮትላንድ ውስጥ ባለፉት ሶስት ሳምንታት የሟቾች ቁጥር መጨመር እንጂ መቀነስ አላሳየም።

    ከሃገሪቱ ብሔራዊ መረጃ ቋት የተገኘው መረጃ እንደሚጠቁመው ሁሉም ሟቾች ማስረጃቸው ላይ የሞት ምክንያት ኮሮናቫይረስ የሚል ተመዝግቧል።

    ምንም እንኳ ኦፊሴላዊ የሟቾች ቁጥር ይህ ይሁን እንጂ ያልተመዘገቡ ሞቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ ይገመታል።

    የዩናይት ኪንግደም አባል የሆነችው ስኮትላንድ ከ6 ሺህ በላይ ዜጎቿ በቫይረሱ መያዛቸውን አረጋግጣለች።

  2. ስዊዘርላንድ ታዳጊዎች አያቶቻቸውን እንዲያቅፉ ፈቀደች

    አያት ከልጅ ልጃቸው ሲጨባበጡ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት ከተወሰዱ እርምጃዎች አንዱ አረጋውያን ከታዳጊዎች ጋር እንዳይገናኙ ማገድ ነበር። ውሳኔው የብዙዎችን ስሜት የነካ ነበር።

    የእንቅስቃሴ ገደብ እያላላች የምትገኘው ስዊዘርላንድ ከአስር ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊዎች ከአያቶቻቸው ጋር መተቃቀፍ ይችላሉ ብላለች።

    የአገሪቱ ጤና ሚንስትር፣ የተላላፊ በሽታዎች ክፍል ኃላፊ ዳንኤል ኮች እንዳሉት፤ ታዳጊዎች ቫይረሱን እንደማያስተላልፉ ሳይንቲስቶች ደርሰውበታል።

    ስዊዘርላንድ ውስጥ በኮሮናቫይረስ ሳቢያ ሕይወታቸውን ያጡ 1,699 ሰዎች ናቸው።

  3. በኢትዮጵያ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር 130 ደረሰ

    ዶ/ር ሊያ ታደሰ (የጤና ሚኒስትር)

    የፎቶው ባለመብት, ጤና ሚኒስቴር

    ዛሬ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ባለፉት 24 ሰዓታት ከተደረጉ 766 ምርመራዎች መካከል አራት ሰዎች ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ገልጿል።

    ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል ሶስቱ ከፑንትላንድ የመጡና በጅግጅጋ ዩኒቨርስቲ አስገዳጅ ለይቶ ማቆያ ውስጥ የነበሩ ሲሆን አንዱ ግን ምንም አይነት የጉዞ ታሪክ የሌለውና የ23 ዓመት የኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሐረርጌ ዞን ጉባ ኮሪቻ ወረዳ ነዋሪ መሆኑ ተጠቅሷል።

    ሁሉም ከ15 እስከ 25 ባለው የእድሜ ክልል የሚገኙ ናቸው።

    በቫይረሱ ተይዘው ከነበሩ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች መካከል ስምንቱ አገግመው የወጡ ሲሆን በአጠቃላይ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 58 ደርሷል።

    ኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ለ16ሺህ 434 ሰዎች የኮቪድ-19 ምርመራ አድርጋለች።

  4. የኬንያን የኮቪድ-19 ምርመራ የሚያስተባብረው ተቋም የመመርመሪያ መሳሪያ እጥረት ገጠመው

    የኬንያ ሕክምና ጥናትና ምርምር ማዕከል የኮሮና ክትባት ላይ ምርምር ያደርጋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኬንያ የሕክምና ጥናትና ምርምር ማዕከል (ኬምሪ) የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ መሳሪያዎች እጥረት እንደገጠመው ገለፀ።

    በኬንያ የሚታተመው ዘ ሰን፣ ለሴኔቶች ኮሚቴ የቀረበውን ሪፖርት ጠቅሶ እንደዘገበው የምርምር ማዕከሉ የኮቪድ-19 መመርመሪያ ቁሳቁስ አጥሮታል።

    የምርምር ተቋሙ የኮሮናቫይረስን ለመመርመር የሚያገለግሉ መሳሪያዎች ገዝቶ ለማስቀመጥ ቢያንስ 7.3 ሚሊየን ዶላር እንደሚያስፈልገው የተቋሙ ዳይሬክተር የሪ ኮምቤ ተናግረዋል።

    ኬምሪ በኬንያ የኮሮናቫይረስ ምርመራዎችን የሚያስተባብር ሲሆን በወረርሽኙ ላይ ፈዋሽ መድሃኒት ወይንም ክትባት ለማግኘት ምርምር ይሰራል።

    በምስራቅ አፍሪካ አገራት እስካሁን ድረስ 373 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ሲረጋገጥ 14 ሰዎች ሞተዋል።

  5. የቻይናና የአፍሪካ ግንኙነት በኮሮና ዘመን ምን ድረስ ይዘልቃል?

  6. በሞሮኮ በመቶዎች የሚቆጠሩ ታራሚዎች በኮሮናቫይረስ ተያዙ

    የሞሮኮ እስር ቤት

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    በሞሮኮ ማረሚያ ቤቶች በተደረገ ምርመራ 313 ታራሚዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    ባለስልጣናቱ እንዳሳወቁት ኡራዛዛቴ በተባለው ማረሚያ ቤት 303 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን፣ በኡዳያ፣ ዛርና ከቢር በሚባሉ ማረሚያ ቤቶች አስር ታራሚዎች ተይዘዋል።

    አብዛኞቹ በቫይረሱ የተያዙት ታራሚዎች ቢሆኑም ጥቂት ቁጥር ያላቸው የማረሚያ ቤት ጠባቂዎችም መያዛቸውም ተገልጿል።

    ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ታራሚዎች የተመረመሩበት ምክንያት ኡራዛዛቴ በተባለው ማረሚያ ቤት በርካታ ታራሚዎች ባለፈው ሳምንት በቫይረሱ መያዛቸውን ተከትሎ ነው።

    ባለስልጣናቱ በቫይረሱ የተያዙትን ሰዎች ለይቶ ማቆያ ውስጥ እንዳስገቧቸውም ተናግረዋል።

    በሞሮኮ ባሉ ማረሚያ ቤቶች 80 ሺህ ያህል ታራሚዎች አሉ። በሚያዝያ ወርም የቫይረሱን መዛመት ለመቀነስ 5ሺህ 654 ታራሚዎች በሞሮኮ ንጉስ ምህረት ተደርጎላቸዋል።

    በሞሮኮ 4ሺህ 252 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን፣ 165 ሰዎችም ህይወታቸውን አጥተዋል።

  7. በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የተላለፉ ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ

    የፌደራል አቃቤ ሕግ አርማ

    የፎቶው ባለመብት, የፌደራል አቃቤ ሕግ ፌስቡክ ገፅ

    በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ 78 ሰዎች ኮቪድ-19ን ለመቆጣጠር የወጣውን አዋጅ በመተላለፍ በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሆነ ተገለፀ።

    ከእነዚህ ግለሰቦች በተጨማሪ ሚያዚያ 9/ 2012 ዓ.ም በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 በአንድ ጠባብ ቤት ውስጥ ጫት ሲቅሙ የተገኙ ዘጠኝ ሰዎች ሶስት ሺህ ብር መቀጮ እንደተጣለባቸው የፌደራል አቃቤ ሕግ በፌስቡክ ገፁ ላይ አስታውቋል።

    እነዚህ ግለሰቦች ቅጣቱ የተጣለባቸው አስቸኳይ ጊዜ አዋጅንና አዋጁን ለማስፈፀም የወጣውን ደንብ በመተላለፍ ጫት በማስቃምና ከአራት ሰው በላይ በመሆን በመሰብሰባቸው የተነሳ መሆኑ ተገልጿል።

  8. "ኦሎምፒክ በሚቀጥለው ዓመትም ላይካሄድ ይችላል" የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር

    ኦሎምፒክ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ ወረርሽኙ በቁጥጥር ሥር ካልዋለ በስተቀር በሚቀጥለው ዓመትም ኦሎምፒክን ማካሄድ አስቸጋሪ መሆኑን ተናገሩ፡፡

    በተለመደው የጊዜ ሰሌዳ የኦሎምፒክ ውድድር መካሄድ የነበረበት በዚህ ዓመት ቢሆንም በኮሮና ምክንያት ለፈረንጆቹ ጁላይ 2021 ተሸጋግሮ ነበር፡፡

    እንዲህም ሆኖ ግን ውድድሩ ወደፊት መካሄዱን በተመለከተም ጥርጣሬ አለ፡፡

    "የኦሎምፒክና ፓራኦሎምፒክስ ጨዋታዎች ሁሉም አትሌቶች እና ተመልካቾች ደህንነታቸው ተጠብቆ በተሳተፉበት በተሳካ መልኩ መካሄድ እንዳለባቸው ስንናገር ነበር" ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ወረርሽኙ ካልጠፋ በስተቀር በተሟላ መልኩ ጨዋታዎቹን ማካሄድ የማይቻል ነው ብለዋል፡፡

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም ኦሎምፒክ ዓለም የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር የሚያደርገውን ትግል ማሸነፉን በሚያሳይ መንገድ መካሄድ አለበት ሲሉም ተደምጠዋል፡፡

    ማክሰኞ እለት የጨዋታዎች አስተባባሪ ኮሚቴ ኃላፊ ዮሽሮ ሞሪ ኦሎምፒክ በመጭው ዓመት ካልተካሄደ ሊሰረዝ ይችላል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

    በጃፓን እስካሁን 13 ሺህ 895 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን ከ413 በላይ ሰዎች ሕወታቸው አልፏል፡፡

  9. የኮሮናቫይረስ ስጋት በሆነበት ወቅት ቤቶችን ማፍረስ "ኢሰብአዊነት" ነው በማለት አምነስቲ ኮነነ

  10. የኒው ዮርኩ ከንቲባ የአይሁዳዊያኑን የቀብር ሥነ ሥርዓት ተቹ

    የኒው ዮርኩ ከንቲባ ቢል ደ ብላሲዎ

    የፎቶው ባለመብት, Mayor Bill de Blasio twitter

    የኒው ዮርኩ ከንቲባ ቢል ደ ብላሲዎ በኮሮናቫይረስ የሞተን የሃሲዲክ-ይሁዳዊ እምነት መምህር የቀብር ሥነ ሥርዓት ለመፈጸም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በመሰባሰባቸው ትችት ሰነዘሩ፡፡

    ከንቲባው ዲ ብላሲዎ በትችት ብቻ አላቆሙም፡፡ የተሰበሰበውን ሰው ለመበተን ወደ ስፍራው አቅንተው ነበር፡፡

    በትዊተር ገጻቸውም "ስብሰባው ተቀባይነት የሌለው እና ወደ ሌላ ሞት የሚያመራ ስህተት ነው" ሲሉ የማስጠንቀቂያ መልዕክት አስፍረዋል፡፡

    ከንቲባው አክለውም የሚሰባሰቡ ሰዎችን እንዲቆጣጠሩ ወይም በቁጥጥር ስር እንዲያውሉ ለፖሊስ ትዕዛዝ ሰጥተው እንደነበርም ተናግረዋል፡፡

    ይሁን እንጅ ይህ አስተያየታቸ ከንቲባውን ከትችት አላስጣላቸውም ፡፡ ቀደም ብሎ የአየር ኃይል ትዕይንትን ለመመልከት ብዙ ሰዎች ተሰብስበው ማስተዋላቸውን በመግለጽ የተወሰኑ ቡድኖችን ብቻ ነጥለው ነው የተናገሩት በሚል በኦንላይን በስፋት ትችት ገጥሟቸዋል፡፡

    ኒው ዮርክ በቫይረሱ ክፉኛ የተጠቃች ሲሆን ከ17 ሺህ የሚበልጡ ሰዎች በቫይረሱ ሕይወታቸው አልፏል፡፡

    የ X ይዘትን ይለፉት
    ይዘቱን X ይፈቅዳሉ?

    ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።

    ማሳሰቢያ: በሌሎች ገጾች ላይ ላሉ ይዘቶች ቢቢሲ ኃላፊነት አይወስድም።

    የ X ይዘት መጨረሻ

  11. የ'ስላምዶግ ሚሊየነር' ተዋናዩ ኢርፋን ካን ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ

    ኢርፋን ካን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቦሊውድ ኮከብ ተዋናይ ኢርፋን ካን በ53 አመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

    ኢርፋን ካን ሕይወቱ ያለፈው በህንድ ምዕራባዊቷ ከተማ ሙምባይ ሆስፒታል እንደሆነ ተነግሯል፡፡

    ተዋናዩ ከሁለት ዓመት በፊት በትዊተር ገጹ ላይ ሆርሞኖችን ወደ ደም ውስጥ የሚለቁ ህዋሳትን የሚጎዳ እምብዛም ባልተለመደ የእጢ ህመም ህክምና እያደረገ እንደሆነ አስታውቆ ነበር፡፡

    በኋላም በለንደን ሆስፒታል ሕክምና ሲከታተል ነበር፡፡

    ተዋናይ ኢርፋን በሂንዲ፣ በሆሊዩድ እና በእንግሊዝ ሲኒማዎች በጉልህ ይታወቃል፡፡

    በተለይ በጎርጎሮሳዊያኑ አቆጣጠር 2008 የተሰራውና የሙምባይ ጭቁን መንደሮችን በሚያሳየው 'ስላምዶግ ሚሊየነር' እና የአሜሪካ ሳይንሳዊ ልብ ወለድ 'ጁራሲክ ፓርክ' በተሰኙ ፊልሞቹ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዝናን አትርፏል፡፡

  12. በርካታ የአፍሪካ አገራት የኮሮናቫይረስ ምርመራቸውን እያሳደጉ ነው

    የኮሮናቫይረስ ምርመራ ሲደረግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በርካታ የአፍሪካ አገራት የሚያደርጉትን የኮሮናቫይረስ ምርመራ እያሳደጉ ነው።

    በተለይ ይህ ደግሞ ቫይረሱ ወደ ማህበረሰቡ እየተስፋፋ ባለበት ወቅት ወሳኝ ነው። በትናንትናው ዕለት የኡጋንዳ ጤና ሚኒስቴር የኮሮናቫይረስ ወደ ማህበረሰቡ ምን ያህል እንደተስፋፋ ለማወቅ አፋጣኝ ምርመራ እንዲደረግ አዝዘዋል።

    ናይጄሪያ በበኩሏ በቀጣዮቹ ሶስት ወራት 2 ሚሊየን ሰዎችን እንደምትመረምር ተናግራለች። የናይጄሪያ በሽታ መቆጣጠር ማዕከል በሌጎስና በኦጉን ግዛቶች የመመርመሪያ ማዕከሎች ያቋቋመ ሲሆን ይህም በመላው አገሪቱ የተቋቋሙትን የመመርመሪያ ጣብያዎች ቁጥር 17 ያደርሰዋል።

    ዛምቢያ በየዕለቱ 1000 ሰዎች ለመመርመር አቅዳ እየተንቀሳቀሰች ትገኛለች። ሩዋንዳም በበኩሏ በየወቅቱ የሚደረግ ምርመራ እንደሚኖራት አስታውቃለች።

    ደቡብ አፍሪካ ከኩባ የመጡ 217 ዶክተሮች የኮቪድ-19 ሕክምናና የምርመራ አቅሟን እንደሚያሳድገው ተናግራለች። በደቡብ አፍሪካ 135 ያህል የሕክምና ባለሙያዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው የታወቀ ሲሆን በመላ አገሪቱም በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ቁጥር 4 ሺህ 996 ደርሷል።

    የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር ዶ/ር ዝዌሊ ማክሄዚ መንግሥት ለጤና ባለሙያዎች የመከላከያ ቁስ በበቂ ለማቅረብ እየሰራ ነው ብለዋል።

    እንደ አፍሪካ በሽታ መቆጣጠርና መከላከል መረጃ ከሆነ በአህጉሪቱ 33 ሺህ 566 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሲያዙ 1ሺህ 469 ደግሞ ሞተዋል። በአፍሪካ ከኮቪድ-19 ያገገሙ ሰዎች ቁጥርም 10ሺህ 152 ደርሷል።

  13. የኡጋንዳ ሕዝብ እንደራሴዎች ስለኮሮና ግንዛቤ ለማስጨበጥ በሚል ለራሳቸው የመደቡት ገንዘብ አስተቻቸው

    እያንዳንዱ የምክር ቤት አባል ከተመደበው በጀት ላይ 2600 ዶላር ይደርሰዋል

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ የሕዝብ እንደራሴዎች ስለኮሮናቫይረስ ግንዛቤ ለመጨበጥ በሚል ለራሳቸው የመደቡትን 2.6 ሚሊየን ዶላር በጀትን ተቹ።

    ፕሬዝዳንቱ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላቱን ድርጊት " ሞራላዊ ተቀባይነት የሌለው" ሲሉ የኮነኑ ሲሆን ገንዘቡ ኮሮናቫይረስን ለመከላከል በየአካባቢው ለተቋቋሙ ኮሚቴዎች መሰጠት ነበረበት ብለዋል።

    እያንዳንዱ የምክር ቤት አባል ከተመደበው በጀት ላይ 2ሺህ 600 ዶላር ይደርሰዋል

    "አፈ ጉባዔውን ሳገኛቸው፣ ከእንዲህ አይነት ወጥመድ መውጣት እንዳለባቸውና ይህንንም ለማድረግ ገንዘቡን ለተባለው ዓላማ አለመጠቀም መሆኑን ነግሬያቸዋለሁ። ከአፈ ጉባዔዋ ጋር የተስማማነው ለዚሁ ዓላማ ለተቋቋመው ግብረ ኃይል ገንዘቡ እንዲለግሱ ነው" ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ሙሴቪኒ ለኦዲተር ጄነራል መሥሪያ ቤቱ ከበጀቱ ላይ ለተመረጡበት አካባቢ የተለያዩ ነገሮችን የገዙ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትን ኦዲት እንዲደረጉ ደብዳቤ እንደሚጽፉ አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንቱ በግለሰብ ደረጃ የተለያየ የድጋፍ ስራዎችን የሚሰሩትን አግደው እንዲህ አይነት እገዛ ማድረግ የሚፈልጉ ግለሰቦች የሚፈጥሩትን ግርግር ለማስቀረት በየአካባቢው ለተቋቋመው ኮሚቴ እንዲሰጡ ተናግረዋል።

    ባለፈው ሳምንት የተቃዋሚ ፓርቲና የምክር ቤቱ አባል የሆኑት ፍራንሲስ ዛኬ ለተመረጡበት አካባቢ ነዋሪዎች ምግብ ሲያከፋፍሉ በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን ፕሬዝዳንት ሙሴቬኒ ግን ህጉ ለሁሉም የህዝብ እንደራሴዎች እንደሚሰራ ገልፀዋል።

    እስካሁን ድረስ ኡጋንዳ 79 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች መኖራቸውን ስታረጋግጥ እስከሚቀጥለው ሳምንት ድረስ የሚዘልቅ የእንቅስቃሴ ገደብ አስቀምጣለች።

  14. ማራዶና አምላክ አለምን ከወረርሽኙ እንደሚታደጋት ተስፋውን ገለፀ

    ማራዶና

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አርጀንቲናዊው እግርኳስ ተጫዋች ማራዶና ከኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ጋር የሚደረገውን ትግል ከአምላክ እርዳታ ጋር ማሸነፍ እንደሚቻል ተስፋውን ገልጿል።

    በቅርቡም የአምላክ ስራ የተገለፀበትን እና እምነቱም እንዴት እንደረዳው ያያበትንም ክስተት የሚያሰለጥነው ክለብ ወደታችኛው ሊግ ሳይወርድ መቅረቱን በምሳሌነት ጠቅሷል።

    ጊምናሲያ የተባለው የማዶና ክለብ ወደታችኛው ሊግ ሊወርድ ቀርቦ የነበረ ቢሆንም በወረርሽኙ ምክንያት ቡድኑ እንደገና በመዋቀሩ ወደታች ከመውረድ ድኗል።

    በአለም ላይ በምርጥ የእግር ኳስ ተጫዋችነት ዝናን ማትረፍ የቻለው የ59 አመቱ ማራዶና እንደ ጎርጎሳውያኑ አቆጣጠር በ1986 አገሩ ከእንግሊዝ ጋር በምታደርገው ጨዋታ ላይ እጁን በመጠቀም ግብ ማስቆጠሩን ተከትሎም ክስተቱን የአምላክ እጅ ነው ብሎታል።

    "በክለባችን ላይ እንዲህ አይነት ተአምር መፈጠሩን ያዩ የዱሮውን እያወሱ የአምላክ እጅ ነው እያሉት ነው" ብሏል።

    "አሁንም ቢሆን የምፀልየው በዚያን ጊዜም ይሁን አሁን የረዳን የአምላክ እጅ ከወረርሽኙ እንዲታደገንና ህዝቡም ህይወቱን በደስታና በጤና ወደሚኖርበት ሁኔታ እንዲመለስ ነው" በማለት አስረድቷል።

    የአምላክ እጅ ተብላ የምትጠራው ጎል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  15. ኮሮናቫይረስ፡ በእንክብካቤ ማዕከላት እየሰሩ ያሉት የ98 ዓመቱ ዶክተር

    ዶ/ር ክሪስቲያን ቸናይ

    ዶክተር ክሪስቲያን ቸናይ ይባላሉ፡፡ የ98 ዓመት አዛውንት ሲሆኑ በሙያቸው ደግሞ ዶክተር ናቸው፡፡ ኗሪነታቸውም ፈረንሳይ ፓሪስ ነው፡፡

    ምንም እንኳን በእርሳቸው እድሜ ላይ ላለ ሰው የኮቪድ-19 በሽታ አስጊ ቢሆንም፤ እርሳቸው ግን ሙያቸው የሚፈቅድላቸውን ሥራቸውን ማከናወን ቀጥለዋል፡፡

    አዛውንቱ ዶክተር ክርስቲያን፤ የእንቅስቃሴ ገደብ ውስጥ ባለችው ፈረንሳይ በየሳምንቱ ጡረተኞች ወዳሉባቸው የእንክብካቤ ማዕከላት እየሄዱ ሙያዊ ድጋፍ ይሰጣሉ፡፡

    እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሱትም በፈረንሳይ ያለውን የቤተሰብ ሐኪሞች እጥረት ለማቃለል እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

    "ሁሉም ሰው ሰግቷል፤ እኔም በጣም እጠነቀቃለሁ። ባለቤቴ ቫይረሱን ወደ ቤት ይዤ እንዳልሄድ ትሰጋለች ፡፡ በእርግጥ ትክክል ናት" ይላሉ፡፡

    ዶክተር ክሪስቲያን አሁን ላይ በፓሪስ የሚሰጡትን የህክምና አገልግሎት ለጊዜው ቢያቆሙም ታማሚዎችን በኢንተርኔት አማካኝነት ያማክራሉ፡፡

    በየሳምንቱም ወደ የእንክብካቤ ማዕከላት ይሄዳሉ፡፡

    "በዚህ ወረርሽኝ ወቅት ልተዋቸው አልችልም፡፡ብቻቸውን መቋቋም አይችሉም" በማለት አረጋውያኑ የእርሳቸውን ድጋፍ እንደሚሹ ይናገራሉ፡፡

    ምንም እንኳን የአረጋውያን ማዕከላት ለቫይረሱ ተጋላጭ ቢሆኑም ክርስቲያን ግን ስራቸውን ሊያቆሙ አይፈልጉም፡፡

    "እድለኞች ነን፡፡ በእንክብካቤ ማዕከሉ እስካሁን በኮቪድ-19 የተያዘ ሰው የለም፡፡ አንድ ሰው ከተያዘ ግን የከፋ ነው የሚሆነው፤ ማንም እንዲሞት አንፈልግም" ይላሉ፡፡

    አሁን ወደ 99 ዓመት እየተጠጉ እንደሆነ የሚናገሩት ዶ/ር ክርስቲያን "በተለያዩ ምክንያቶች እንቅስቃሴዎችን መቀነስ አለብኝ፡፡ ከዚህ በፊት ከምሰራው በጣም ቀስ ብየ ነው የምሰራው፤ ጥንቃቄ ማድረግ ስላለብኝ" ብለዋል፡፡

  16. በእንግሊዝ ሚሊዮኖች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ማድረግ ይችላሉ ተባለ

    በእንግሊዝ የኮሮና ምርመራ ሲደረግ

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

    የእንግሊዝ መንግሥት የኮሮናቫይረስ ምርመራ ቁልፍ ለተባሉ የስራ ዘርፎች ነው የሚለውን መመሪያ በማላላት ሚሊዮኖችን መመርመር የሚያስችለውን ውሳኔ አስተላልፏል።

    ባለፈው ሳምንት በአገሪቷ ቁልፍ በተባሉ የስራ ዘርፎች ውስጥ ለሚሰሩ ሰራተኞችና ለቤተሰቦቻቸው ምርመራ ተጀምሯል።

    እንደገና በተሻሻለው መመሪያ መሰረት በእንክብካቤ ማዕከል ያሉ ነዋሪዎችና ሰራተኞች፣ ዕድሜያቸው ከ65 በላይ የሆኑና በቤታቸው የማይሰሩ ሰዎች በሙሉ መመርመር ይችላሉ።

    የሃገሪቱ ብሔራዊ ስታስቲክስ መረጃ እንደሚያሳየው በእንግሊዝና በዌልስ በኮሮናቫይረስ ከሚሞቱት መካከል 1/3ኛውን የሚይዙት በእንክብካቤ ማዕከላትና በቤታቸው የሚሞቱ ናቸው።

    የጤና ሚኒስትሩ ማት ሃንኮክ ኮሮናቫይረስን አስመልክቶ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ "በግንባታ ስራ የተሰማሩ፣ በምርምር ላይ ያሉ ሳይንቲስቶች፣ በፋብሪካዎች ተቀጥረው የሚሰሩ እንዲሁም ሌሎች በስራቸው ምክንያት በቫይረሱ በቀላሉ የሚያዙ ሰዎችን በምርመራው እንዲካተቱ ማድረግ ደህንነታቸውን መጠበቅ ነው" ብለዋል።

    ማንኛውም ከላይ የተጠቀሱትን መስፈርቶች የሚያሟሉ በመንግሥት ባወጣው ድረገፁ ላይ በመግባት የምርመራ ቀነ ቀጠሮ መያዝ ይቻላል።

  17. ማላዊ በኮቪድ-19 ጫና ለደረሰባቸው ዜጎቿ የገንዘብ ድጋፍ ልታደርግ ነው

    ማላዊ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የማላዊ ፕሬዝዳንት ፒተር ሙታሪካ በኮቪድ-19 ክፉኛ ለተጎዱ ዝቅተኛ ኑሮ ለሚኖሩ ዜጎቻቸው የገንዘብ ድጋፍ ሊያደርጉ ነው።

    ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮ ለሚመሩ ቤተሰቦች ከፈረንጆቹ ግንቦት ወር መጀመሪያ ጀምሮ 47 ዶላር በሞባይል በኩል ይተላለፍላቸዋል ተብሏል።

    ይህ ውሳኔ የተሰማው የአገሪቱ ከፍተኛው ፍርድ ቤት መንግሥት በመላው አገሪቱ ለሶስት ሳምንት የሚዘልቅ የእንቅስቃሴ ገደብ እንዳይጥል ካገደ በኋላ ነው።

    የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች በሚጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ ምክንያት ለሚጎዱ የኀብረተሰብ ክፍሎች የተዘጋጀ ድጋፍ የለም ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተው ነበር።

    በዚህ መንግሥት ባዘጋጀው ድጋፍ በኮሮናቫይረስ ምክንያት የተጎዱ አንድ ሚሊየን ሰዎችና አነስተኛ ንግዶች እንደሚጠቀሙ ፕሬዘዝዳንት ሙታሪካ ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ይህ ድጋፍ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ ያሉት ነገር የለም።

    በማላዊ 36 ሰዎች ኮቪድ-19 የተገኘባቸው ሲሆን ሶስት ሰዎች ደግሞ መሞታቸው ተመዝግቧል።

  18. በኮሮናቫይረስ ህይወታቸውን ያጡትን በክብር የሚቀብረው ግለሰብ

    አብዱል ማልባሪ

    ለሶስት አስር አመታት አብዱል ማልባሪ ዘመድ የሌላቸውን፣ ቀባሪ ያጡ ሟቾችን ቀብሯል።

    ነገር ግን ቤተሰብ ያላቸውን ሟቾች እቀብራለሁ ብሎ ባያስበውም፤ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ቤተሰቦቻቸውን መሰናበት እንዲሁም መቅበር ያልቻሉትን በክብር መቅበር የየዕለት ስራው ሆኗል።

    "ስራዬ እንዲህ ነው የሚባል የተወሰነ ሰአት የለውም። የሞተ ሰው አለ ተብሎ ከተደወለልን መሮጥ ነው" ብሏል የአምሳ አንድ አመቱ ግለሰብ።

    ሟቾችን መቅበር ከስራ በላይ ለሆነው አብዱል የማያውቃቸው ሰዎች ቢሆኑም ለሟቾቹ ከፍተኛ ኃዘን አለው፤ ልቡም ተሰብሮ እንደ ቤተሰብ፣ ዘመድ በክብር ነው የሚሸኛቸው።

    ለአብዱል ሰው መሆን በራሱ በቂ ነው። ከሶስት አስርት አመታት በፊት ወደዚህ ስራም እንዲገባ ያደረገው ይኸው ለሰብአዊነት የሚሰጠው ቦታ ነው።

    በህንዷ ጉጅራት ግዛት በምትገኘው ሱራት ከተማ ግለሰቦች በኮሮናቫይረስ ህይወታቸውን ሲያጡ ባለስልጣናቱ የሚደውሉት ለአብዱል ማልባሪ ነው። በግዛቷ 19 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፤ 244 ሰዎችም በቫይረሱ ተይዘዋል።

    በአጠቃላይ በጉጅራት ግዛትም 3ሺህ 548 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

  19. ቬትናም በኮሮናቫይረስ አንድም ሞት ያላስመዘገበችበት ሚስጥር ምንድን ነው?

  20. በብራዚል በኮሮናቫይረስ የሞቱት ሰዎች ቁጥር ከቻይና በለጠ

    በብራዚል የፊት ጭምብል ያደረገ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በብራዚል በኮሮናቫይረስ የሞቱት ሰዎች ቁጥር ከቻይና በልጦ አምስት ሺህ ደርሷል።

    የብራዚሉ ጤና ሚኒስቴር እንዳሳወቁት ባለፉት 24 ሰዓታት በኮሮናቫይረስ 474 ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎ ቁጥሩን 5ሺህ 017 አድርሶታል።

    በላቲን አሜሪካ ካሉ አገራት ክፉኛ በኮሮናቫይረስ በተጠቃችው ብራዚል 72ሺህ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    የቫይረሱ መነሻ በሆነችው ቻይና 4ሺህ 633 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።

    ባለፈው ወር የብራዚሉ ፕሬዚዳንት ጄይር ቦልሶናሮ የእንቅስቃሴ ገደቡን ተቃውመው የወጡ ሰልፈኞችን ደግፈው መውጣታቸው ከፍተኛ ውግዘትን አድርሶባቸዋል።

    ከዚህ በተጨማሪም ፕሬዚዳንቱ ኮሮናቫይረስ ቀላል ጉንፋን ነው የሚል አስተያየት በመስጠታቸው ትችቶችን ማስተናገዳቸው የሚታወስ ነው።