አውስትራሊያ ውስጥ በኮሮናቫይረስ ስጋት ሁለት ሆስፒታሎች ተዘጉ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በአውስትራሊያዋ ታስማኒያ ግዛት ውስጥ ከሚገኙት ሁለት ሆስፒታሎች ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ተይዘው በመገኘታቸው ሆስፒታሎቹ ተዘጉ።
ይህንንም ተከትሎ በሁለቱ ሆስፒታሎች ውስጥ የሚሰሩ 1,200 ሠራተኞችና ቤተሰቦቻቸው ለሁለት ሳምንት ወደ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ ሊደረግ ነው።
በዚህም ሳቢያ የሆስፒታሉን ሠራተኞች ጨምሮ ከእነሱ ጋር የቅርብ ንክኪ አላቸው የተባሉ 5 ሺህ ቤተሰቦቻቸው ወደ ለይቶ ማቆያ ይገባሉ ተብሏል።
በተዘጉት ሁለቱ ሆስፒታሎች ውስጥ ህክምና ሲከታተሉ የነበሩት አብዛኞቹ ህሙማን በአቅራቢያ ወደሚገኝ ሌላ ሆስፒታል የሚዘዋወሩ ሲሆን ሆስፒታሎቹም ከፍ ያለ ከተዋህሲያን የማጽዳት ተግባር ይከናወንባቸዋል ተብሏል።
በታስማኒያ ግዛት ውስጥ እስካሁን በኮሮናቫይረስ ከተያዙት 144 ሰዎች መካከል 60 ያህሉ ከእነዚህ ሆስፒታሎች ጋር የተገናኙ እንደሆኑ ዘገባዎች አመልክተዋል።
የግዛቲቱ አስተዳዳሪ ፒተር ገትዊን ስለርምጃው ሲናገሩ “የበሽታውን መስፋፋትን ለማስቆም ይህ ልናደርገው የምንችለው ተመራጭ ነገር ነው” በማለት ትብብር ጠይቀዋል።






