በኮሮናቫይረስ የተያዙ 8 ሰዎች መገኘታቸውን ተከትሎ በኢትዮጵያ የህሙማኑ ቁጥር 82 ደረሰ

የጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ አሃዝ እንደሚጠቁመው በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 1.9 ሚሊዮን ደርሷል። ከእነዚህ መካከል ሲሶ ያክሉ የሚገኙት ደግሞ በአሜሪካ ነው። ፕሬዝደንት ትራምፕ ግን አሁንም ቫይረሱን እንቆጣጠራለን እያሉ ነው። ወደ የቀጥታ ዘገባችን ገጽ ቢያመሩ ከቫይረሱ ስርጭት ጋር የተያያዙ ወቅታዊ መረጃዎችን ታገኛላችሁ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. 7ቱ የሞዲ ምክሮች

    የሕንዱ ጠቅላይ ሚንስትር ናሬንድራ ሞዲ የኮሮናቫይረስን ስርጭት ለመግታት እና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ ሕንዳውያን መከተል ያለባቸው ያሏቸውን 7 ምክሮች ለግሰዋል።

    ጠቅላይ ሚንስትሩ ዜጎች በጥብቅ ሊከተሏቸው የሚገቡ 7 ሕጎች ያሏቸው የሚከተሉት ናቸው።

    • አዛውንቶችን መንከባከብ
    • ማህበራዊ ርቀት የመጠበቅ ትዕዛዝን አለመተላለፍ። በቤት የሚሰሩ የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ጨርቆችን መጠቀም
    • የሰውነት የበሽታ የመከላከል አቅምን ከፍ የሚያደርጉት ምግቦችን በቤት አዘጋጅቶ መጠቀም
    • መንግሥት ያበለጸገውን አሮገያሴቱ የተሰኘውን መተግበሪያ በስልክ ላይ መጫን። ይህ መተግበሪያ ስለ ከቪድ-19 መረጃ ይሰጣል
    • አቅመ ደካሞችን መንከባከብ
    • ቀጣሪዎች በዚህ ወረርሽኘ ወቅት ሠራተኞቻቸውን ከማባረር ይቆጠቡ
    • የኮሮናቫይረስን ከፊት ሆነው ለሚዋጉት ጤና ባለሙያዎች፣ ሕግ አስከባሪዎች እና የጽዳት ሠራተኞች ክብር እንስጥ።
  2. ደቡብ አፍሪካ ቫይረሱን የመቆጣጠር ስራዬ ስኬታማ ነው አለች

    ደቡብ አፍሪካ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር እየወሰደችው ያለው እርምጃ ውጤታማ መሆኑን ገልጻለች።

    በመላው አገሪቱ የታወጀው የእንቅስቃሴ ገደብ ለጊዜውም ቢሆን ስርጭቱን ለመግታት እንዳስቻለ ተገልጿል።

    የመንግስት አማካሪ ኮሚቴው ዋና ሰብሳቢ በቴሌቪዥን ባስተላለፉት መልዕክት የተሰራው ስራ አመርቂ ውጤት አስገኝቷል ብለዋል።

    ፕሮፌሰር አብዱል ካሪም እንደተናገሩት አገሪቱ ቀደም ብላ የወሰደችው ለሁለት ሳምንታት ሙሉ በሙሉ እንቅስቃሴን የመገደብ እርምጃ ቫይረሱን ለመቆጣጠር አስችሏታል።

    አገሪቱ ዓለማ አቀፍ መዳረሻ መሆኗን ከግምት ውስጥ በማስገባት በአሁኑ ሰአት በቀን 65 አዳዲስ ቫይረሱ ያለባቸው ሰዎች ብቻ መገኘታቸው ጥሩ ዜና ነው ብለዋል።

    አክለውም የቫይረሱን ስርጭት የሚከታተሉና የሚመረምሩ ከ20 ሺ በላይ የጤና ባለሙያዎችን ማሰልጠናቸውን ገልጸዋል።

  3. ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ላይ ምክረ ሀሳቡን አቀረበ

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አስፈላጊነት እንደሚገነዘብ ጠቅሶ ሁሉም የሕግ አስከባሪ ተቋማት በአስቸኳይ ጊዜ ሁኔታ ውስጥ ሊከተሉ ስለሚገባቸው መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች መርሆች እና ግዴታዎች በሚመለከት ምክረ ሃሳቡን አቅርቧል።

    ኮሚሽኑ የሕግ አስከባሪ ተቋማት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁንና ደንቡን በሥራ ላይ ሲያውሉ እና ሲያስፈጽሙ በሰብዓዊ መብቶች እና ሕገ መንግሥታዊ መርሆች እንዲመሩ፣ በማናቸውም ሁኔታ ሊገደቡ የማይችሉ መሠረታዊ መብቶችን እንዲያከብሩና እንዲያስከብሩ፣ እንዲሁም በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜትና የሙያ ሥነ ምግባር እንዲመሩ አሳስቦ፤ የአዋጁን አፈጻጸምም የሚከታተል መሆኑን ገልጿል።

    ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ጨምሮም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወቅት የተወሰኑ የፖለቲካና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ላይ ጊዜያዊ ዕገዳ ሊደረግ እንደሚችል በመጥቀስ እንደ በሕይወት የመኖር መብት ያሉ በአስቸኳይ ጊዜ ሁኔታም ሊገደቡ የማይችሉ መሠረታዊ መብቶች ሙሉ በሙሉ የማክበር እና የማስከበር ግዴታ መቀጠል አለበት ብሏል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የአዋጁ አፈጻጸም ላይ የሕግ አስከባሪ ተቋማት ልዩ ሚና እና ኃላፊነት እንዳለባቸውም ጠቅሷል።

    በተለይ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት መሠረታዊ መብቶች እንዳይጣሱ መከላከል፣ ሊገደቡ የማይችሉ መሠረታዊ መብቶችን የማክበርና የማስከበር፣ እንዲሁም የአስቸኳይ ጊዜ ደንቡ በሕግ በተቀመጠለት ገደብ ሥራ ላይ መዋሉን ማረጋገጥ የሕግ አስከባሪ ተቋማት ሚና መሆኑን ኮሚሽኑ አስታውሷል።

    ከዚህ በተጨማሪም የሕግ አስከባሪ ተቋማት የአስቸኳይ ጊዜ ደንቡንና ዓላማውን ሲያስፈፅሙ በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት መስራት እንደሚኖርባቸው አስታውሶ፤ ሕብረተሰቡም ከመንግሥት አካላት የሚሰጡ መመሪያዎችን በማክበር የበሽታውን ስርጭት ለመከላከል የበኩሉን እንዲወጣ ኮሚሽኑ ጥሪውን አስተላልፏል።

  4. በጉዋንግዡ የሚገኙ ከ100 በላይ አፍሪካውያን ቫይረሱ ተገኘባቸው

    የጉዋንግዡ ከተማ 111 አፍሪካውያን በኮሮናቫይረስ እንደተያዙ ማስታወቁን ሺኑዋ ዘግቧል።

    ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ የከተማዋ አስተዳደር 4500 ለሚሆኑ አፍሪካውያን ምርመራ አድርጓል።

    ቫይረሱ ከተገኘባቸው 111 ሰዎች መካከል 19ኙ ቫይረሱን ይዘው የገቡ መሆናቸውን ባለስልጣናት ገልጸዋል።

    ባለፉት ቀናት ደግሞ አፍሪካውያን ከመኖሪያቸው በግድ እንዲወጡ እየተደረገ እንደሆነ በሰፊው ሲነገር ነበር።

    አፍሪካውያን በሆቴሎችና በሕዝብ መሰብሰቢያዎችም ጭምር እንዳይገቡ ተከልክለዋል መባሉን ተከትሎ መንግስታት ቅሬታቸውን ገልጸዋል።

    የጉዋንግዡ ከተማ አስተዳደር ግን ቫይረሱን ለመከላከል ብዙ እርምጃዎችን እየወሰድኩ ነው፤ አፍሪካውያንን ለይቼ ያደረኩት ነገር የለም ብሏል።

  5. ሕንድ የእንቅስቃሴ ገደቡን አራዘመች

    የሕንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ለህዝባቸው ባስተላለፉት መልእክት በኮሮናቫይረስ ምክንያት ተከልክሎ የነበረው ማንኛውም እንቅስቃሴ እስከ ሚያዝያ 25 መራዘሙን ገልጸዋል።

    ውሳኔውም የተላለፈው ከሁሉም የአገሪቱ ግዛቶች ጋር ከተደረገ ውይይት በኋላ ነው ብለዋል።

    ጠቅላዩ አክለውም በመንግስት የተላለፉ የመከላከያ እርምጃዎችን ህዝቡ እንዲከተል አሳስበዋል።

  6. በቻይና አዲስ 89 ሰዎች ኮሮና ተገኘባቸው

    ቻይና ሰኞ ዕለት 89 አዲስ የኮሮና ቫይረስ ታማሚዎችን ማግኘቷን አስታወቀች።

    ከትናንት በስቲያ ደግሞ 108 ቫይረሱ ያለባቸው ሰዎች በቻይና መገኘታቸውን ተከትሎ ከስድስት ሳምንታት በኋላ ከፍተኛው ሆኖ ተመዝግቦ ነበር።

    አዳዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር በቻይና እየጨመረ የመጣው በሰሜናዊ ሄይሎንግጂያንግ በኩል አድርገው ከሩሲያ የሚመለሱ ቻይናዋያን ምክንያት ነው ተብሏል።

    እንደ አገሪቱ የጤና ኮሚሽን ከሆነ ከሰማንያ ዘጠኙ ሰዎች መካከል ሰማንያ ስድቱ ከሌላ ቦታ ወደ ቻይና የመጡ ሲሆን ሶስቱ ግን በጉዋንዶንግ ግዛት የተገኙ ናቸው።

    ሲሲቲቪ የተሰኘው የዜና አውታር በበኩሉ 79ኙ የቻይና ዜግነት ያላቸው ሲሆን በሩሲያ በኩል ወደ አገር ቤት የገቡ ናቸው ብሏል።

  7. "1 ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን የምግብ እርዳታ ያሻቸዋል" ተመድ

    የተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት (ፋኦ) በኢትዮጵያ 1 ሚሊዮን ሰዎች የምግብር እርዳታ ያሻቸዋል አለ።

    ይህም የሆነው እጅግ ሰፋፊ የእርሻ ቦታዎች በአንበጣ ወረርሽኝ መጎዳታቸውን ተከትሎ ነው።

    ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በመስራት የተመድ የምግብና እርሻ ድርጅት ደረስኩበት እንዳለው ከሆነ በትንሹ 200ሺህ ሄክታር ሰብል አንበጣ በልቶታል።

    ከዚህ ውስጥ አብዛኛው የማሽላና በቆሎ እርሻ ነው። ኬንያና ሶማሊያም ከኢትዮጵያ ቀጥሎ ክፉኛ በአንበጣ ወረርሽኝ የተጠቁ አገራት ናቸው ብሏል ድርጅቱ።

    በነዚህ አገራት ወረርሽኙን ለማቆም በአውሮፕላን የጸረ አንበጣ መድኃኒት ርጭት እንደተደረገ ተጠቁሟል። በዩጋንዳ የመከላከያ ሰራዊቱ ጭምር የአንበጣ ወረርሽኝን ለመከላከል ተሳትፎ አድርጓል።

    ሆኖም አሁን እነዚህ ጥረቶች በኮሮና ቫይረስ ምክንያት እክል እንደገጠማቸውን አውስቷል።

  8. በዩክሬን የኦርቶዶክስ ገዳም ተዘጋ

    ሁለት መነኮሳት በኮቪድ-19 መሞታቸውን ተከትሎ በዩክሬን ዋና ከተማ ኪየቭ አንድ የኦርቶዶክስ ክርስቲያን ገዳም በፖሊስ እንዲዘጋ ሆኗል።

    ፔቼርስክ ላቭራ ገዳም 90 የሚሆኑ የኮሮናቫይረስ ታማሚዎች ተገኝተውበታል።

    ባለፈው ወር የዚሁ ገዳም ኃላፊ ይህ ቫይረስ በእኛ ሀጥያት የመጣ ነው፤ ሊጠፋም የሚችለው በመተቃቀፍ፣ በጾም በጸሎት ነው በሚል ተናግረው ነበር።

    በርካታ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን ተከትሎ ግን የገዳሙ ኃላፊ ቫይረሱን አቃለው መመልከታቸን አምነዋል።

    ይህቺ ፔቼርስክ ላቭራ የተባለቸው የ11ኛው ክፍለ ዘመን ጥንታዊት ገዳም ዜጎች ቤት አርፈው ይቀመጡ ሚለውን የመንግሥት መመሪያ ስትንቀው ነበር ተብሏል።

    በኋላ ግን ሕዝቡ የመንግሥት መመሪያዎችን እንዲከተል አዛለች። ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት እንዲዘጉም ወስናለች። ገዳሙ የራሺያ የኦርቶዶክስ ክርስትና ቤት ክርስቲያን አንድ ቅርንጫፍ ናት።

  9. ዶናልድ ትራምፕ የጤና አማካሪያቸውን ከሥራ ሊያባሯቸው ይሆን?

    እጅግ የካበተ የሥራ ልምድ አላቸው የሚባሉትና 6 የአሜሪካ ፕሬዝዳንቶችን እንዳማከሩ የሚነገርላቸው የ79 ዓመቱ አንቶኒ ፋውቺ በዶናልድ ትራምፕ ከሥራ ሊፈናቀሉ ይችላሉ የሚለው ዜና ከትናንት ጀምሮ ሲናፈስ ነበር።

    ያለ ምክንያት አይደለም ታዲያ። ዶ/ር ፋውቺ ዶናልድ ትራምፕ እጅግ በሚያወግዙትና የሐሰት ፋብሪካ በሚሉት ሲኤንኤን ቲቪ ቀርበው በሰጡት ቃለ ምልልስ ‹‹ቀድመን እርምጃ ወስደን ቢሆን ኖሮ የደረሰውን ጥፋት መቀነስ እንችል ነበር›› የሚል ይዘት ያለው አስተያየት በመስጠታቸው ነው።

    ይህም በቀጥታ ትራምፕንና አመራራቸው በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ዙርያ የወሰዱትን የዘገየ እርምጃ እንደመተቸት ተደርጎ ተወስዶባቸዋል።

    ትራምፕ በማንኛውም መንገድ የሚተቿቸውን ኃላፊዎች በቀጥታ ሳይጠበቅ የማባረር አባዜ ተጸናውቷቸዋል። ይህን ተከትሎ ትራምፕ አንድ የትዊተር ገጽ ላይ የተጻፈን አስተያየት ያጋራሉ።

    ጽሑፉ በአንድ የሪፐብሊካን የኮንግረስ እጩ የተጻፈና "ፋውቺን ከሥራ አባረው" (#fireFauci) የሚል ሃሽታግ ያለበት ነው። ይህን ተከትሎ ትራመፕ ዶ/ር ፋውቺን ያባሯቸዋል የሚለው ዜና በአንዳንድ መገናኛ ብዙኃን ወጥቶ ነበር።

    ምሽት ላይ አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ‹‹ ዶ/ር ፋውቺን እወደዋለሁ፤ አላባርረውም›› ብለዋል።

  10. አገራትን ጭምብል እስከመሰራረቅ ያደረሳቸው የኮሮናቫይረስ ዲፕሎማሲ

    የአንዳንደ አገራትን እውነተኛ ባህሪ አውጥቶታል ኮቪድ-19።

    ጭምብል እስከመሰራረቅ የደረሰ።

    ወረርሽኙን ተከትሎ በአገራት መካከል ቬንትሌተር ለማግኘት የሚደረገው ሽሚያ ለጉድ ነው። ሁሉም ቅድሚያ ለዜጋዬ ስለሚል ማለት ነው።

    ክትባቱን ቀድሞ ለማግኘትም ፉክክሩ ጦፏል። ሁሉም አገር በሳይንስ የበላይነቱን ለማስጠበቅ።

    የአውሮፓ ኅብረት ከኮቪድ-19 በኋላ ዕድሜ ይኖረዋል? ሲሉ መጠየቅ የጀመሩም አልጠፉም። ምክንያታቸው ደግሞ በሰሜንና በደቡብ የአውሮፓ አገራት መካከል የታየው መቃቃር ነው።

    ጣሊያንና ስፔን እንዴት በችግራችን አትደርሱልንም ሲሉ በእነ ጀርመን ላይ ጥርስ ነክሰዋል።

    ተንታኞች 'የኮቪድ ዲፕሎማሲ' ሲሉ ስም አውጥተውለታል ይህን ምስቅልቅል።

  11. የፈረንጆቹ በጋ የቫይረሱን ሥርጭት ይገታው ይሆን?

    ኮቪድ-19 የጀመረ ሰሞን ይሄ ቫይረስ ሙቀት አይስማማውም ሲባል ነበር።

    ከጤና አማካሪዎቻቸውም በላይ በኅብረተሰብ ጤና ጉዳይ እንደ ሳይንቲስት የሚያደርጋቸው ዶናልድ ትራምፕ እንዲያውም "በጋ ይግባ እንጂ ሙቀት ቫይረሱን አፈር ድሜ ያበላዋል" ሲሉ ነበር።

    እውን የቫይረሱ ሥርጭት በሙቀት ወራት ይገታ ይሆን?

    ሳይንቲስቶች ይህን ጥያቄ አፍ ሞልቶ ለመመለስ ጊዜው ገና ነው ይላሉ።

    ይህ ቫይረስ ወቅት ይመርጣል አይመርጥም ጥናት ይሻል። ጥናቱን ለማድረግ ገና ወቅቶቹ ራሳቸው አልገቡም፤ በተለይ በአንድ አካባቢ በተለያየ ወቅት ኮቪድ-19 ምን የተለየ ባህሪ አለው የሚለውን ለማጥናት።

    ምልክቶችን ለማየትም በተለያዩ አካባቢዎች በሽታው ያሳየው ባሕሪ በስፋት መጠናት ይኖርበታል።

    ይህ ማለት ግን እስካሁን በዚህ ረገድ የተገኙ ምንም መረጃዎች የሉም ማለት አይደለም።

  12. እንደምን አደራችሁ የቢቢሲ አማርኛ ቤተሰቦች!

    ከአሁኑ ሰዓት ጀምሮ የቀጥታ ዘገባችንን እንጀምራለን።

    በቀጥታ ዘገባችን ከኮሮናቫይረስ ስርጭት ጋር የተያያዙ ከመላው ዓለም አሁናዊ መረጃዎችን እናደርሳችኋላን።

    መልካም ቀን።

    የሰኞ ዘገባችንን ከታች መመልከት ትችላላችሁ።

  13. የዛሬን በዚህ ቋጨን ነገ ጠዋት እንመለሳለን

    ውድ የቢቢሲ አማርኛ ቤተሰቦች የዛሬን በዚህ ቋጭተናል። ነገ ጠዋት በቀጥታ ዘገባችን እንመለሳለን።

    የሰኞ ዘገባችንን ከታች ይመልከቱ።

  14. ወረርሺኙን የሚገታው ክትባት ብቻ ነው ተባለ

    የዓለም ጤና ድርጅት የኮሮናቫይረስ ስርጭት ሙሉ በሙሉ ሊገታ የሚችለው ውጤታማ ክትባት ጥቅም ላይ ሲውል ብቻ ነው አለ።

    የድርጅቱ ኃላፊ ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም እንዳሉት፤ “ስርጭቱን ሊያቆም የሚችለው ውጤታማና ጉዳት የማያስከትል ክትባት ነው።”

    በርካታ ባለሙያዎች፤ ሰዎችን ከኮሮናቫይረስ ለመከላከል የሚያስችል ክትባት እስኪሠራ ቢያንስ አንድ ዓመት እንደሚወስድ ተናግረዋል።

    አንዳንድ አገሮች እንቅስቃሴ ላይ የጣሉትን ገደብ ለማንሳት እያቀዱ ነው። ዶ/ር ቴድሮስ ግን ዜጎችን ከወረርሽኙ የሚከላከል እርምጃ ሳይተገበር፤ እገዳ ማንሳት በጥንቃቄ ሊፈተሽ የሚገባ ውሳኔ ነው ይላሉ።

  15. በአራቱ የአማራ ክልል ከተሞች ተጥሎ የነበረው ገደብ ተነሳ

    በአማራ ክልል በሚገኙ አራት ከተሞች ተጥሎ የነበረው ያለመንቀሳቀስ ገደብ ከነገ ጀምሮ እንደሚነሳ ተገለጸ።

    በአማራ ክልል ሶስት በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች መገኘታቸውን ተከትሎ በባህር ዳር፣ አዲስ ቅዳም፣ ቲሊሊ እና እንጅባራ ከተሞች ማንኛውም አይነት የህዝብ እና የተሽከርካሪ እንቅስቃሴ እንዳይኖር መወሰኑ የሚታወስ ነው።

    የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ ተመስገን ጥሩነህ ለአማራ ቴሌቪዥን ሲናገሩ፤ በአራቱ ከተሞች ላይ የተጣለው ገደብ ቢነሳም፤ በአገር አቀፍ ደረጃ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የተላለፉት መመሪያዎች በከተሞቹ ላይ ይተገበራሉ ብለዋል።

    አራቱ ከተሞች እንቅስቃሴ አልባ ሆነው ላለፉት 13 ቀናት ሰንብተዋል።

  16. የኤርትራ የኦርቶዶክስ ሐይማኖት ተከታዮች ትንሳዔን በቤት ሆነው እንዲያከብሩ ጥሪ ቀረበ

    የኤርትራ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሲኖዶስ አማኞች የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመቆጣጠር መጪውን የትንሳዔ በዓል በቤት ሆነው እንዲያክበሩ ዝርዝር መመሪያ ማውጣቱ ተነገረ።

    ሲኖዶሱ በሰሞነ ህማማት፣ ስቅለትና የትንሳኤ በዓልን አማኞች ከቤት ሳይወጡ በዓላቱን እንዲያከብሩ መመሪያውን አስተላልፏል።

    የኤርትራ መንግሥት የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመቆጣጠር ከመጋቢት 24 ጀምሮ ለ21 ቀናት የሚዘልቅ ከቤት ያለመውጣት ውሳኔን አስተላልፎ እንደነበረ ይታወሳል።

    ኤርትራ እስካሁን 34 በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ ሰዎች ይገኙባታል።

  17. “ኮቪድ-19 ከስዋይን ፍሉ አስር እጥፍ አደገኛ ነው” ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም

    ኮሮናቫይረስ፤ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ አቆጣጠር 2009 ላይ ከተቀሰቀሰውና ‘ስዋይን ፍሉ’ በመባል ከሚታወቀው ወረርሽኝ አስር እጥፍ አደገኛ እንደሆነ የዓለም ጤና ድርጅት ኃላፊ ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም ተናገሩ።

    ከመላው ዓለም የተሰበሰበ መረጃ፤ ኮሮናቫይረስ ምን አይነት ባህሪ እንዳለው፣ እንዴት ማከም እንሚቻልና በምን መንገድ ማቆም እንደሚቻል በግልጽ እንደሚጠቁም ተናግረዋል።

    “ኮቪድ-19 በፍጥነት እንደሚሰራጭ እና እጅግ አደገኛ እንደሆነ እናውቃለን፤ ከ2009ኙ ወረርሽኝ አንጻር በ10 እጥፍ ይበልጣል” ሲሉም አክለዋል።

    የ2009ኙ ወረርሽኝ በመላው ዓለም ወደ 200,000 ሰዎችን ገድሏል።

  18. በኮሮናቫይረስ ሳቢያ በርካታ ዜጎቻቸውን ያጡ ቀዳሚ 10 አገራት

    እንደ ጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ አሃዝ መሠረት ዛሬ ላይ በመላው ዓለም በኮቪድ-19 ሳቢያ ሕይወታቸውን የተነጠቁ ሰዎች ቁጥር 116ሺ 098 ነው።

    ከእነዚህም መካከል አሜሪካ፣ ጣሊያን እና ፈረንሳይ 22ሺ154፣ 19ሺ899 እና 17ሺ489 እንደየቅድመ ተከተላቸው የሟቾች ቁጥርን በመያዝ ከአንድ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል።

    4ኛ ፈረንሳይ 14ሺ 393

    5ኛ ዩናይትድ ኪንግደም 11ሺ 329

    6ኛ ኢራን 4ሺ585

    7ኛ ቤልጂየም 3ሺ903

    8ኛ ቻይና 3ሺ345

    9ኛ ጀርመን 3ሺ022

    10ኛ ኔዘርላንድስ 2ሺ823

  19. ሰበር, በኒው ዮርክ በቫይረሱ ምክንያት የሞቱ ሰዎች ቁጥር 10ሺን ተሻገረ

    በኒው ዮርክ በቫይረሱ ሳቢያ ከ10ሺ በላይ ሰዎች መሞታቸውን የኒው ዮርክ ገዢ አንድሩ ኩዎሞ አስታወቁ።

    አንድሩ በፈረንጆቹ ዕለተ ፋሲካ በኒው ዮርክ በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር 671 መሆኑን ተናግረዋል።

    ይህም በኒው ዮርክ ግዛት በቫይረሱ የሞቱ ሰዎች ቁጥርን ወደ 10,056 ወስዶታል።

    የግዛቷ ገዢ በየቀኑ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር የመቀነስ ምልክት እያሳየ ቢሆንም አሁንም ግን በየቀኑ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ ነው ብለዋል።

  20. አሜሪካ የወረርሽኙ ጫፍ ላይ ተቃርባለች ተባለ

    አሜሪካ የኮቪድ-19 ጫፍ መቃረቧን የ ‘ሴንተር ፎር ዲዚዝ ኮንትሮል’ ዳይሬክተር ዶ/ር ሮበርት ሬድፊልድ ተናገሩ።

    ይህም ለምጣኔ ኃብት ዘርፉ መከፈት መንገድ እንደሚጠርግ ገልጸዋል።

    በአሜሪካ 557,663 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል። 116,052 ሰዎች ደግሞ ሞተዋል። እነዚህ ቁጥሮች አሜሪካን ከሌሎች አገራት ቀዳሚ ያደርጓታል።

    በወረርሽኙ በከፍተኛ ሁኔታ በተጠቁ ግዛቶች የሟቾች ቁጥር ዝግ እያለ ይመስላል።

    ዶ/ር ሮበርት፤ የምጣኔ ኃብት ዘርፉ የሚከፈተው ደረጃ በደረጃ እንደሆነና ጥንቃቄ እንደሚያስፈልግም አስረድተዋል።