ለጨረታ የቀረበው የጃክ ዶርሲ የመጀመሪያው ትዊት በ2.5 ሚሊዮን ዶላር ገዢ አገኘ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የትዊተር መስራች ከሆኑት መካከል አንዱ ጃክ ዶርሲ በትዊተር ገጹ ላይ የለጠፋቸውን የመጀመሪያ ትዊቶች በጨረታ ለሽያጭ አቅርቦ የመጀመሪያው ትዊት ከ2.5 ሚሊዮን ዶላር መሻገሩ ተነገረ።
በ2.5 ሚሊዮን ዶላር ለመግዛት ጥያቄ የቀረበበት ትዊት፤ የጨረታው አሸናፊ ትዊቱን ስለመግዛቱ ዲጂታል ሰርተፊኬት ይቀበላል ተብሏል።
ጃክ ዶርሲ እአአ 2006 ላይ "Just setting up my twttr," ነበር ሲል ለመጀመሪያ ጊዜ ትዊተር ላይ የጻፈው።
የጃክ የመጀመሪያ ትዊት ብትሸጥም በትዊተር ላይ ትቆያለች።
ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።
የ X ይዘት መጨረሻ
አሸናፊው ተጫራች የሚቀበለው ዲጂታል ሰርተፊኬት በጃክ ዶርሲ የተረጋገጠ እና የተፈረመ ይሆናል። ዲጂታል ሰርተፊኬቱ የመጀመሪያ ትዊት መቼ ትዊት እንደተደረገች፣ የትዊቱ ይዘት እና መሰል መረጃዎችን የያዘ ይሆናል።
ይሁን እንጂ በዲጂታል ሰርተፊኬቱ ላይ የሰፈቱት መረጃዎች ማንኛውም የትዊተር ተጠቃሚ በትዊተር ላይ ሊመለከተው የሚችል ነው።
ጨረታው የወጣው 'ቫሊዩብል ባይ ሴንት' በሚሰኝ ድረ-ገጽ ላይ ሲሆን፤ የደረ-ገጹ መሥራቾች ሰዎች ገንዘባቸውን ወጪ አድርገው መሰል ዲጂታል ሰርተፊኬቶችን ቢይዙ አዋጭ የሆነ ኢንቨስትመንት ነው ይላሉ።
የቢቢሲ የቴክኖሎጂ ዘጋቢ ሮሪ ኬለን-ጆነስ ትዊቶችን በብሎክቼይን አማካኝነት ዲጂታል ገንዘብ እየሆኑ መጥተዋል ይላል።
ለአብዛኞቻችን አንድን ትዊት 2.5 ሚሊዮን ዶላር ወጪ አድርጎ መግዛት የማይታሰብ ሊሆን ይችላል ይሁን እንጂ ይህን የመጀመሪያ ትዊት ከትዊተር መሥራች ከሆነው ዶርሲ ጋር አንዳች ቁርኝነት እንዳለው በማሰብ ዋጋ ይሰጡታል።
ሮሪ ምናልባት ሌላ ገዢ ወደፊት ከ2.5 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ አድርጎ የመግዛት ፍላጎት ሊኖረው ይችላል ሲል ይናገራል።












