በዲሞክራቲክ ኮንጎ ቤቶች ላይ የተከሰከሰው አውሮፕላን 27 ሰዎች ቀጠፈ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ትናንት ሁለት የአውሮፕላኑ ሰራተኞችን ጨምሮ 17 ሰዎች አሳፍሮ ከዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎዋ ጎማ ወደ ቤኒን ለማቅናት በተነሳ በአንድ በደቂቃ ውስጥ መኖሪያ ቤቶች ላይ በተከሰከሰው አውሮፕላን ምክንያት 27 ሰዎች መሞታቸውን ባለስልጣናት አስታወቁ።
ከ27ቱ ሟቾች ዘጠኙ የአንድ ቤተሰብ አባላት መሆናቸውም ሊታወቅ ችሏል።
ቢዚ ቢ የተባለ የግል አየር መንገድ ንብረት የሆነው ይህ አውሮፕላን ጎማ ውስጥ ማፔንዶ በተሰኘ መንደር ነው የተከሰከሰው።
የአውሮፕላኑ የመከስከስ መንስኤ ምን እንደሆነ እስካሁን በማጣራት ላይ እንደሆኑ ባለስልጣናቱ ገልፀዋል።
አውሮፕላኑ ሶስት ጊዜ አየር ላይ እንደ እንዝርት ሾሮ ከዚያም እሳት ሲተፋ ማየቱን ዲጅሞ ሚዳር የተባለ የአይን እማኝ ለሮይተርስ ተናግሯል።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
"አውሮፕላኑ ሲከሰከስ ወደ ወደቀበት ቦታ ሮጥን፣ ፓይለቱ ዲዲየር የሚባል ነው እናውቀዋለን። 'እርዱኝ እርዱኝ' እያለ ቢጮኸም እሳቱ በጣም ሃይለኛ ስለነበር ልናወጣው አልቻልንም" ብሏል።
የአቪዬሽን ደህንነት ቁጥጥር የላላ ነው በሚባልባት በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የአውሮፕላን አደጋ ይደጋገማል። አውሮፕላን ጥገና ችግርም ለተደጋጋሚ አደጋዎች በምክንያትነት ይቀመጣል።
የአገሪቱ ሁሉም የግል አየር መንገዶች በአውሮፓ እንዳይንቀሳቀሱ በአውሮፓ ህብረት ዕግድ ተጥሎባቸዋል።













