ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ኮሮናቫይረስ፡ ቻይና ውስጥ ጥቁሮች እንዳይገቡ የከለከለው ምግብ ቤት ይቀርታ ጠየቀ
በቻይናዋ የኢንዱስትሪ ከተማ ጓንዡ ውስጥ የሚገኝ አንድ የማክዶናልድስ ቅርንጫፍ ምግብ ቤት አፍሪካዊያን ገብተው እንዳይጠቀሙ በመከልከሉ ድርጅቱ ይቅርታ ጠየቀ።
ጥቁሮች ወደ ምግብ ቤቱ መግባት እንደማይችሉ የሚያመለክት ማስታወቂያን ተለጥፎ የሚያሳይ አንድ ተንቀሳቃሽ ምስል በማኅበራዊ መገናኛ መድረኮች ላይ በስፋት ሲሰራጭ ታይቷል።
በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ምግብ ቤቶችን የሚያስተዳድረው ማክዶናልድስ ቻይና ውስጥ በሚገኘው ቅርንጫፉ በኩል ስለተለጠፈውን የክልከላ ማስታወቂያ እንዳወቀ ምግብ ቤቱን ለጊዜው እንዲዘጋ ማድረጉን አሳውቋል።
ባለፈው ሳምንት በድረ ገጾች በኩል የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በከተማዋ ባሉ አፍሪካዊያን መካከል እየተስፋፋ ነው የሚል ወሬ ከተነዛ በኋላ በመቶዎቹ የሚቆጠሩ ነዋሪነታቸው ጓንዡ የሆኑ በመቶዎቹ የሚቆጠሩ አፍሪካዊያን ከሚኖሩባቸው አፓርታማዎች መባረራቸውን የማኅበረሰቡ መሪዎች ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በዚህም ሳቢያ በአሁኑ ጊዜ በከተማዋ ውስጥ በነዋሪዎችና በአፍሪካዊያን መካከል ያለው ውጥረት በእጅጉ ተካሮ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል።
ሸቀጦችን የሚሸጡና የሚገዙ የአፍሪካዊያን ነጋዴዎች ማዕከል የሆነችው ጓንዡ በቻይና ውስጥ በርካታ የአፍሪካ ማኅበረሰብ ከሚገኝባቸው ከተሞች መካከል አንዷ ናት።
በአፍረካውያን ላይ የሚደረገውን መድልዎ በተመለከተ የጓንግዶንግ ክፍለ አገር መንግሥት ቻይናና አፍሪካ መልካም ወዳጆች፣ አጋሮችና ወንድማማቾች ናቸው የሚል ምላሽ ሰጥቷል።
ጥቁሮች ላይ የተደረገውን ክልከላ በተመለከተ ማክዶናልድስ በበኩሉ በሰጠው ምላሽ ድርጊቱ "ሁሉን አካታች የሆነውን እሴታችንን የሚወክል አይደለም" ሲል አውግዞታል።
ጨምሮም "ጓንዡ በሚገኘው ምግብ ቤታችን ውስጥ ያልፈቀድነው ማስታወቂያ መለጠፉን እንዳወቅን ወዲያውኑ በማስነሳት ምግብ ቤቱ ለጊዜው እንዲዘጋ አድርገናል።"
ማክዶናልድ እንዳለው ከዚህ ቀደም በዚሁ ቅርንጫፉ ውስጥ ለሚሰሩ ሰዎች "ብዘሃነትንና ሁሉን አቀፍነትን" የተመለከተ ስልጠና መስጠቱን ተናግሯል።