ሁለት ሚሊዮን ሰዎች ከዩክሬን መሰደዳቸውን የመንግሥታቱ ድርጅት አስታወቀ
ሁለት ሳምንት ሊሞላው በተቃረበው የዩክሬን- ሩሲያ ጦርነት ሳቢያ ከዩክሬን የተሰደዱ ሰዎች ቁጥር ከሁለት ሚሊዮን መብለጡን የመንግሥታቱ ድርጅት ለቢቢሲ ገለጸ።
ነገ ረቡዕ ሁለተኛ ሳምንቱን የሚደፍነው ሩሲያ በዩክሬን ላይ የከፈተችው ወረራ ከባድ ሰብአዊ ቀውስን አስከትሎ ሚሊዮኖች መኖሪያቸውን ጥለው እንዲሰደዱ ማድረጉ ተዘግቧል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዴ ይህ ከጦርነቱ መቀስቀስ በኋላ የታየው የሰዎች ስደት እጅግ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህ በሁለት ሳምንት ውስጥ የታየው የዩክሬናውያን ስደት በከፍተኛ መጠን እየጨመረ ሲሆን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ በአውሮፓ ውስጥ የታየ ግዙፍ መፈናቀል መሆኑን አመልክተዋል።
በምሥራቅ በኩል የሚካሄደውን ጦርነት በመሸሽ ከዩክሬን የሚሰደዱት ሰዎች በስተምዕራብ ወደ ሚገኙት ፖላንድ፣ ሩሜኒያ፣ ስሎቫኪያ፣ ሃንጋሪ እና ሞልዶቫን ወደ መሳሰሉ የፈለሱ ሲሆን፣ የተወሰነ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች ወደ ሩሲያና ቤላሩስ መግባታቸው ተነግሯል።
በተባበሩት መንግሥታት መረጃ መሠረት አስካሁን ከዩክሬን የሄዱ ስደተኞችን እያስተናገዱ ያሉት አገራት የሚከተሉት ናቸው፡
• ፖላንድ = ከ1,204,000 በላይ
• ሃንጋሪ = 191,000
• ስሎቫኪያ = 141,000
• ሞልዶቫ = 83,000
• ሩሜኒያ = 82,000
• ሩሲያ = 99,300
• ቤላሩስ = 453
ሲሆኑ ከእነዚህ ባሻገር ደግሞ ከ83,000 በላይ ሰዎች ከዩክሬን ወጥተው ወደ ሌሎች የአውሮፓ አገራት መሸጋገራቸውን የመንግሥታቱ ድርጅት አመልክቷል።