በአሜሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 6 ሚሊዮን ተቃረበ

በአሜሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 6 ሚሊዮን ተቃረበ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በዛሬው ዕለት 1 ሺህ 173 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ፣ 19 ሞቱ

    ግራፊክስ

    በዛሬው ዕለት ለ18 ሺህ 160 ሰዎች በተከናነው የላብራቶሪ ምርመራ 1 ሺህ 173 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    በዚህም መሰረት በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 53 ሺህ 304 መድረሱን የጤና ሚኒስቴርና የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት መግለጫ አመላክቷል።

    በባለፉት 24 ሰዓታት 19 ሰዎች ህይወታቸው ማለፉ የተገለፀ ሲሆን አገሪቱ በአጠቃላይ ያጣቻቸው ዜጎች ቁጥርም 828 ሆኗል።

    ከዚህም በተጨማሪ 493 ሰዎች ማገገማቸውንም ተከትሎም ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 19 ሺህ 487 አድርሶታል።

    አገሪቱ የመርመር አቅሟን በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረች ሲሆን እስካሁንም ድረስ 928 ሺህ 453 የላብራቶሪ ምርመራዎችን አከናውናለች።

  2. ልጆቻችንን ትምህርት ቤት ባንልካቸውስ?

  3. ኮቪድ-19 ያሰናከለው ምርጫና ያልተረጋጋው የኢትዮጵያ የፖለቲካ

  4. የኮሮና ወረረሽኝ 'ፍርቱና' ያመጣለት ዙም ሚሊዮን ዶላሮች አተረፈ

  5. የቬኒስ አለም አቀፍ ፌስቲቫል ሊጀመር ነው

    የቬኒስ ከተማ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    እንደ ሌሎች ዝግጅቶች ሁሉ የቬኒስ ፊልም ፌስቲቫልም በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ተቋርጦ ነበር። የወረርሽኙ ስጋት ባይቀረፍም አለም አቀፉ የቬኒስ ፊልም ፌስቲቫል በነገው እለት እንደሚጀመር ይፋ ሆኗል። በወረርሽኙ ምክንያት ተቋርጠው ከነበሩ የፊልም ፌስቲቫሎችና ውድድሮች መካከል የቬኒስ መጀመር ቀዳሚው አድርጎታል።

    ስመ ጥሩው የካንስ ፊልም ፌስቲቫልን ጨምሮ በርካታ አለም አቀፍ ፌስቲቫሎች ፊልሞቻቸውን በበይነ መረብ አማካኝነት ለማሳየት ተገደዋል።

    ሆኖም ቬኒስ ፌስቲቫሉን በበይነ መረብ አላካሂድም፤ ታዳሚዎች በተገኙበት ነው ፊልሞቹ የሚታዩት የሚል ውሳኔም ላይ ደርሷል።

    የፌስቲቫሉ ዳይሬክተር አልበርቶ ባርቤራ እንዳሉት የቬኒስ ፊልም ፌስቲቫል በታቀደበት መልኩ፤ ታዳሚዎች በተገኙበት ሁኔታ መካሄዱ አዎንታዊ መልዕክት አለው ብለዋል።

    "በአሁኑ ሰዓት ፊልሞች በሲኒማ ቤቶች መታየት መጀመር አለባቸው ብለን የምናምንበት ጊዜ ነው" ማለታቸውንም ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    "ቲያትር ቤቶች መከፈት አለባቸው። አዳዲስ ፊልሞች መታየት መጀመር አለባቸው። የፊልሞች ቀረፃ ሊጀመር ይገባል፤ የፌስቲቫሉ መጀመር በፊልም ኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሚሳተፉ አካላት ያበረታታል ብለን እናምናለን" ብለዋል።

    ፌስቲቫሉ 77ኛ ሲሆን ለአስር ቀናትም ያህል ይካሄዳል።

  6. ባለፉት 24 ሰዓታት ከ1ሺህ በላይ በኮሮና መያዛቸው ተነገረ

    የኮሮናቫይረስ ሁኔታ መግለጫ

    ባለፉት 24 ሰዓታት ለ19 ሺህ 364 ሰዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ተደርጎ 1 ሺህ 9 ሰዎች ላይ በሽታው መገኘቱን ጤና ሚንስቴር አስታወቀ።

    ከቅርብ ወራት ወዲህ በአገሪቱ በኮቪድ-19 የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ይገኛል።

    በሌላ በኩል ባለፉት 24 ሰዓታት በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር 16 መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን 612 ሰዎች ደግሞ ከኮቪድ-19 አገግመዋል።

    በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ50 ሺህ በላይ ሆኗል።

  7. የሕንድ የቀድሞ ፕሬዝዳንት በኮሮናቫይረስ ከተያዙ በኋላ ሕይወታቸው አለፈ

    የሕንዱ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ፕራናብ ሙከርጂ

    የፎቶው ባለመብት, GETTY IMAGES

    የሕንዱ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ፕራናብ ሙከርጂ በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን ካስታወቁ ከ21 ቀናት በኋላ ሕይወታቸው አልፏል።

    የ84 ዓመቱ የቀድሞ ፕሬዝዳንት በአንጎላቸው ውስጥ የነበረን የረጋ ደም ለማስወጣት በሄዱበት ነበር ኮሮናቫይረስ እንዳለባቸው የተነገራቸው።

    51 ዓመታት በቆየው የአመራር አገልግሎታቸው ፕራናብ ሙከርጂ በተለየዩ ኃላፊነቶች የሰሩ ሲሆን ከአውሮፓውያኑ 2012 እስከ 2017 ደግሞ የሕንድ ፕሬዝዳንት ነበሩ።

    በእነዚህ ዓመታትም በገንዘብ፣ የውጭ ጉዳይ እና መከላከያ ሚኒስትር በመሆን ሰርተዋል።

  8. የዘጠና በመቶ አገራት የጤና ስርዓት ተቃውሷል- የዓለም ጤና ድርጅት

    ሆስፒታል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዓለም ጤና ድርጅት ሰራሁት ባለው የዳሰሳ ጥናት መሰረት 90 በመቶ የሚሆኑ አገራት የጤና ስርአት በኮሮናቫይረስ ምክንያት መቃወሱን ገለጸ።

    ድርጅቱ መረጃውን የሰበሰበው ከመጋቢት እስከ ሰኔ ባለው ጊዜ ውስጥ ነው።

    የዓለም ጤና ድርጅት ባገኘው መረጃ መሰረት በርካታ የሕክምና ቀጠሮዎች እና ምርመራዎች በተጠቀሰው ወቅት እንዲሰረዙ ሆኗል።

    ወረርሽኙ በተለይ ደግሞ እንደ የካንሰር ታካሚዎችና ሌሎች አስጊ የሚባል የጤና ሁኔታ ያላቸውን ሰዎች በእጅጉ ጎድቷል።

    መካከለኛና ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው አገራት ደግሞ በወረርሽኙ ምክንያት ክፉኛ መጎዳታቸውን ተገልጿል።

    ከግማሽ በላይ በሚሆኑት የዓለም አገራት ውስጥ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት (60 በመቶ) ጉዳት የደረሰበት ሲሆን የአእምሮ ጤና ህክምና ደግሞ (61 በመቶ) ጉዳት ደርሶበታል።

    የካንሰር ህክምናም ቢሆን ቀላል የማይባል (55 በመቶ) ጉዳት አስተናግዷል።

  9. የፍቅር ጓደኛውን ለማየት ከለይቶ ማቆያ ያመለጠው ተፈረደበት

    አውስትራሊያ ውስጥ የፍቅር ጓደኛውን ለማየት በሚል ከለይቶ ማቆያ ማዕከል ያመለጠው ግለሰብ የስድስት ወር እስራት ተፈረደበት።

    በሐምሌ ወር መጀመሪያ አካባቢ ይህ ግለሰብ በነበረው የጉዞ ታሪክ ምክንያት ነበር እራሱን ለሁለት ሳምንታት ለይቶ እንዲያቆይ የታዘዘው።

    ነገር ግን እራሱን ከለየ በሶስት ቀናት ውስጥ ውጭ ካለ ጓደኛው ጋር በመተባበር ከለይቶ ማቆያው አምልጧል ተብሏል።

    ከሆቴሉ ሲሲቲቪ ካሜራ የተገኘው ተንቀሳቃሽ ምስል ግለሰቡ በጣራ ላይ ተንላጥሎ በመሰላል ሲወርድ ያሳያል።

    ግለሰቡ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሲውል የፍቅር ጓደኛው ባኞ ቤት ውስጥ ተደብቆ ነበር።

    ግለሱ ከለይቶ ማቆያው ያመለጠው የፍቅረኛውን ልደት ለማክበር መሆኑም ተገልጿል።

  10. ቬንዙዌላ የሩሲያውን ክትባት በበጎ ፈቃደኞች ላይ ልትሞክር ነው

    ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቬንዙዌላው ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮ በሩሲያ የተመረተውን የኮቪድ-19 ክትባት ፈቃደኛ የሆኑ ዜጎች ላይ እንዲሞከር ዜጎችን እንደሚጠይቁ አስታውቀዋል።

    ሩሲያ በያዝነው ወር አጋማሽ አካባቢ ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የሚሆን ክትባት በይፋ ፍቃድ የሰጠች የመጀመሪያዋ አገር ስትሆን ተመራማሪዎች ግን ክትባቱ የተሰራበት ፍጥነት አሳሳቢ ነው ብለዋል።

    ምክንያታቸው ደግሞ የሙከራው ጊዜ ከዚህም በላይ መውሰድ ነበረበት የሚል ነው።

    ከሩሲያ በቢሊየኖች የሚቆጠር ዶላር በብድር ያገኘው የቬንዙዌላ መንግስት ክትባቱ ላይ ክሊኒካዊ ሙከራ ለማድረግ ፈቃደኝነቱን ገልጿል።

    ''በሚቀጥሉት ቀናት ፍቃደኛ ዜጎች ክትባቱን እንዲወስዱ መጠየቅ እንጀምራለን'' ብለዋል ፕሬዝዳንት ማዱሮ።

    ቬንዙዌላ እስካሁን ከ50 ሺ በላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን የመዘገበች ሲሆን ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች ደግሞ 381 ደርሰዋል።

  11. በአሜሪካ በኮሮረናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 6 ሚሊየን ተጠጋ

    አሜሪካ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ ውስጥ በኮሮረናቫይረስ ወረርሽኝ መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ቁጥር ወደ ስድስት ሚሊየን ተጠግቷል።

    ይህም ከዓለም የመጀመሪያውን ስፍራ እንድትይዝ ያደረጋት ሲሆን በቫይረሱ ሳቢያ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ደግሞ ከ180 ሺ በላይ ሆኗል። የሟቾችም ቁጥር ቢሆን ከዓለም ከፍተኛው ነው።

    ምንም እንኳ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በአሜሪካ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ካላት ህዝብ አንጻር ዝቅተኛ ነው ቢሉም በሌሎች መረጃዎች መሰረት ግን አሜሪካ በቫይረሱ በእጅጉ የተጠቃች አገር ናት።

    የአሜሪካ የሕዝብ ቁጥር እስካሁን ከሞቱት ጋር ሲነጻጸር ደግሞ በዓለም ካሉት ከፍተኛ ቁጥር ካስመዘገቡት 10 አገራት መካከል አስቀምጧታል።

  12. ለ111 ቀናት በድጋፍ መሳሪያ የቆዩት አዛውንት አገገሙ

    ቻይና

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ቻይና ውስጥ በኮሮረናቫይረስ ከተያዙ በኋላ ለሶስት ወራት በሳንባ ቦታ ሆኖ ለመተንፈስ በሚያግዝ መሳሪያ ሲረዱ የነበሩ የ62 ዓመት አዛውንት ማገገማቸው ተገልጿል።

    አዛውንቱ በወረርሽኙ ከተያዙ በኋላ ባሳለፍው ጥር ወር ላይ ነበር በደቡብ ምስራቅ ቻይና በሚገኘው ጉዋንግዡ ሆስፒታል የገቡት።

    የጤና ሁኔታቸው ባለመሻሻሉ የካቲት ወር ላይ ለሳንባ ድጋፍ የሚሰጥና ኦክስጅን የሚያቀርብ መሳሪያ ተገጥሞላቸው ነበር። ለ111 ቀናት የተደረገላቸው ይህ የሕክምና አይነት በጣም ውድ እንደሆነም ይነገራል።

    ምንም እንኳን አዛውንቱ ረዥም ጊዜያቸውን በድጋፍ መሳሪያው ቢቆዩም በተመሳሳይ ሁኔታ ለረዥም ጊዜ በመቆየት ግን አንዲት አሜሪካዊት ታዳጊ ትበልጣቸዋለች።

    የሰባት ዓመቷ ህጻን በመሳሪያው እየተደገፈች ለ551 ቀናት ሕክምና ተደርጎላታል።

    በመሳሪያው እየተደገፉ ለ60 ቀናት ለመቆየት ደግሞ 4.2 ሚሊየን ዶላር እንደሚያስፈልግ ጤና ላይ የሚሰራው 'ካይዘር ሄልዝ' የተባለው ድረገጽ አስነብቧል።

    ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ይህንን መሳሪያ የተጠቀሙ ታማሚዎች ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን የቻይናዊው አዛውንት ማገገም ጥሩ ዜና እንደሆነ ተገልጿል።

  13. በኢትዮጵያ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር 51 ሺህ በላይ ሆነ

    ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የጤና ሚኒስቴርና የኀብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ የ23 ሰዎች ህይወት ማለፉን በዕለታዊ ሁኔታ መግለጫቸው ላይ አስታወቁ።

    በአገሪቱ ባለፉት 24 ሰዓታት ለ21,499 ናሙናዎች የኮቪድ-19 ምርመራ የተደረገ ሲሆን 1,468 ሰዎችም በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    በተጨማሪም 266 ሰዎች ከወረርሽኙ ያገገሙ ሲሆን ይህም በአጠቃላይ ከቫይረሱ ያገገሙ ሰዎችን ቁጥርን 18 ሺህ 382 አድርሶታል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ለ890 ሺህ 929 ናሙናዎች ላይ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ሲደረግ 51 ሺህ 122 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተረጋግጧል።

  14. ሊዮኔል ሜሲ የሚጠበቅበትን የኮሮናቫይረስ ምርመራ ሳያደርግ ቀረ

    ሊዮኔል ሜሲ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የባርሴሎናው አርጀንቲናዊ የእግር ኳስ ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ቡድኑ ለሚያደርገው የኮሮናቫይረስ ምርመራ ሳይገኝ መቅረቱ ተሰማ።

    ቡድኑ ልምምድ ከመጀመሩ በፊት ዘወትር የኮቪድ-19 ምርመራ የሚያደርግ ሲሆን ሜሲ ግን ለዚህ ምርመራ ሳይገኝ ቀርቷል።

    የዓለማችን ኮከብ ተጫዋች ሜሲ ማክሰኞ ዕለት ቡድኑን ለቆ በሚሄድበት ሁኔታ ላይ ከባርሴሎና ክለብ አመራሮች ጋር ሳይግባባ ቀርቶ ነበር።

    ሜሲ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ለማድረግ ባለመገኘቱ የተነሳ ከቡድኑ ጋር ላይጫወት ይችላል ተብሏል።

    አርጀንቲናዊው የእግር ኳስ ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ የልቀቁኝ ደብዳቤውን ለባርሴሎና ኃላፊዎች ማስገባቱ የተሰማው ከቀናት በፊት ነበር።

    የ33 ዓመቱ የባርሴሎና ኮከብ አጥቂ ለቡድኑ ባስገባው መልቀቂያ፤ በዚህ የዝውውር መስኮት ባርሴሎናን መልቀቅ እንደሚፈልግ አሳውቋል።

  15. የእንግሊዝ ፖሊስ የተለያዩ ድግሶችን እያስቆመ ነው

    ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር የእንግሊዝ ፖሊስ ፈቃድ ያላገኙ ድግሶችንና የሰዎች መሰባሰብን ለማስወገድ የወጣውን አዲስ ደንብ ተግባራዊ ማድረግ ጀምሯል።

    በዚህም መሰረት እነዚህን ዝግጅቶች የሚያዘጋጁ ሰዎች እስከ 10 ሺህ ፓወንድ የሚደርስ የገንዘብ ቅጣት ያጠብቃቸዋል።

    በተጨማሪም በእነዚህ ዝግጅቶች ላይ ታድመው የተገኙ ሰዎች ከ100 ፓወንድ ጀምሮ ቅጣት እንደሚጣልባቸው ታውቋል።

    አስካሁንም ለእነዚህ ዝግጅቶች የሚያገለግሉ ከፍተኛ ገንዘብ የሚያወጡ ቁሳቁሶች በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸውም ተነግሯል።

    ፖሊስ ሃርሎው በተባለ ቦታ ፈቃድ ሳያገኝ ሊካሄድ የነበረን የሙዚቃ ዝግጅት ካስቆመ በኋላ አዛዡ ዋና ኢንስፔክተር ልዊስ ቤስፎርድ "እቃዎቹ የኪራይ ይሁኑ ወይም የግለሰቦቹ ይወርሳል ዝግጅቶቹንም እናስቆማልን" ብለዋል።

    ፖሊስ እንዳለው ከትልልቅ ዝግጅቶች ይልቅ በቤት ውስጥ የሚካሄዱ ድግሶች መበራከታቸውን በተመለከተ ከሚደርሱት ሪፖርት አረጋግጧል።

  16. በህንድ በአንድ ቀን ከ78 ሺህ በላይ ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ተረጋገጠ

    ምርመራ ሲደረግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በዓለማችን በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 25 ሚሊዮን አልፏል። ህንድ ደግሞ በ24 ሰዓት ውስጥ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን በኮቪድ-19 የያዙ ሰዎች በማስመዝገብ የዓለምን ክብረወሰን ይዛለች።

    ህንድ በዓለማችን በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ካለባቸው አገራት መካከል ሁለተኛ ስትሆን ከ1.3 ቢሊየን ዜጎቿ መካከል በአንድ ቀን ብቻ 78,761 ሰዎች መያዛቸውን በምርመራ ማረጋገጧ ተገልጿል።

    ወረርሽኙ መከሰቱ ከታወቀ ጊዜ ጀምሮም በቫይረሱ ምከንያት የሞቱ ሰዎች ቁጥር 63,000 ደርሷል።

    አሁንም በህንድ የሚደረገው የኮሮናቫይረስ ምርመራ አነስተኛ ነው እየተባለ ሲሆን ይህ ቁጥር በአገሪቱ ያለውን የቫይረሱን የስርጭት መጠን ሙሉ በሙሉ አያሳይም ተብሏል።

    በህንድ ከአንድ ሚሊየን ሰዎች መካከል 30 ሺህ ያህሉ ብቻ የኮሮናቫይረስ ምርመራ እንደሚያገኙ ሲገለጽ፤ ይህም በቫይረሱ ክፉኛ ከተጠቁ አገራት አንጻር አነስተኛው ነው ተብሏል።

  17. በኢትዮጵያ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች አሃዝ ወደ 50 ሺህ ተጠጋ

    ጭምብል ያጠለቁ ወጣት ሴቶች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በአጠቃላይ በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 49,654 የደረሰ ሲሆን ምርመራ የተደረገላቸው ሰዎች ቁጥር ደግሞ 869,430 ሆኗል።

    በኢትዮጵያ ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 770 ሲደርስ፣ ከቫይረሱ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 18,116 መድረሱን የጤና ሚንስቴርና የኅብረተሰብ ጤና ተቋም ቅዳሜ ምሽት ያወጡት አሃዝ አመልክቷል።

  18. በአውሮፓ ከተሞች "ኮቪድ-19 ውሸት ነው" የሚሉ ተቃውሞዎች እየተካሄዱ ነው

  19. ልጆች ኮሮናቫይረስን ያስተላልፋሉ?

  20. እንደምን አደራችሁ የቢቢሲ ቤተሰቦች

    የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ያደረገ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, GETTY IMAGES

    በኢትዮጵያ እስካዛሬ ድረስ ለ869 ሺህ 430 ናሙናዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራዎች ተደርገዋል።

    ከእነዚህም መካከል በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር 49 ሺህ 654 ደርሷል።

    በሌላ መልኩ ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 18 ሺህ 116 ሲደርስ የሟቾች ቁጥር ደግሞ 770 ሆኗል።

    የቫይረሱ ስርጭት በከተሞች ከፍ ብሎ የሚታይ ሲሆን አሁንም አዲስ አበባ ከሌሎቹ የአገሪቱ ክፍሎች ሁሉ ከፍ ያለ የስርጭት መጠን ይታያል።

    የሕክምና ባለሙያዎች አሁን ያለው መዘናጋት ከቀጠለ የጤና ተቋማት በህሙማን ይጨናነቃሉ የሚል ስጋት እንዳላቸው ይናገራሉ።

    ስለዚህ የራስዎን እንዲሁም የሌሎችንም ጤንነት ለመጠበቅ የኮቪድ-19 መከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ ማድረግ አይርሱ።