በዓለም ላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ3 ሚሊዮን አለፈ

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የምድራችንን ነዋሪ ጤናና ህይወት አደጋ ላይ ከመጣሉ ባሻገር የዓለምን ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴ ክፉኛ አስተጓጉሏል። በበሽታው ክፉኛ የተጠቁ አገራት ውስጥ በወረርሽኙ ሳቢያ የሚሞቱ ሰዎች አሃዝ ባለፉት ጥቂት ቀናት የመቀነስ አዝማሚያ እንደታየ ቢዘገብም አሳሳቢነቱ ግን ገና አልተወገደም። እስካሁን በኮቪድ-19 በመላው ዓለም ከ3 ሚሊዮን በላይ ሰዎች እንደተያዙ የተረጋገጠ ሲሆን ከ200 ሺህ የሚበልጡ ሰዎች ደግሞ ለሞት ተዳርገዋል።እኛም ከእዚህ አሃዝ ውስጥ ላለመግባት ሳንዘናጋ የመከላከያ መንገዶች ተግባራዊ እናድርግ። ስለበሽታው ትኩስ ዜናና መረጃ ለማግኘት የቀጥታ ዘገባ ገጻችንን ተከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በስፔን በቫይረሱ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር መቀነሱን ቀጥሏል

    በኮሮናቫይረስ ክፉኛ በተጠቃችው ስፔን በቫይረሱ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር እየቀነሰ መምጣቱ ተነገረ፡፡

    በስፔን ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ የሞቱት 301 ሰዎች ሲሆኑ ትናንት ከነበረው ቁጥሩ በ30 ቀንሷል፡፡

    በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ግን በ1 ሺህ 308 ጨምሮ አጠቃላይ ቁጥሩን 210 ሺህ 773 አድርሶታል፡፡

    ከአውሮፓ ስፔን በቫይረሱ ክፉኛ ከተጠቁ አገራት አንዷ ስትሆን በአንድ ወር ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በቫይረሱ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር መቀነሱን ያሳወቀችው ባሳለፍነው እሁድ ነበር፡፡

    አገሪቷ ወረርሽኙን ለመቆጣጠር የጣለቻቸውን ገደቦች ማላላት የጀመረች ሲሆን በስድስት ሳምንታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ከ14 ዓመት በታች ያሉ ህጻናት ከቤት እንዲወጡ ፈቅዳለች፡፡

  2. ከለይቶ ማቆያ አምልጣለች የተባለችው ግለሰብ ይቅርታ ተጠየቀች

    በስህተት ከለይቶ ማቆያ አምልጣለች የተባለችውን ግለሰብ የናይጄሪያዋ ቦርኖ ግዛት ኃላፊዎች ይቅርታ ጠየቁ።

    ግለሰቧና አንድ ሌላ ታካሚ ከህክምና መስጫ ተቋም አምልጠዋል ተብሎ ነበር። ሌላኛው ግለሰብ በጠና ታሞ ቤቱ የተገኘ ሲሆን፤ ህክምና እየተደረገለት ይገኛል።

    ግለሰቧ ግን በራሷ ተነሳሽነት ወደ ህክምና መስጫ ስለሄደች ኃላፊዎቹ ይቅርታ ጠይቀዋታል።

    ኃላፉዎቹ በሰጡት መግለጫ፤ መጀመሪያ ላይ ግለሰቧ በኮሮናቫይረስ መያዟ አልተነገራትም ነበር።

    አሁን ከሁለቱ ሰዎች ጋር ንክኪ የነበራቸው ሰዎች እየተፈለጉ ነው።

    በቦርኖ ግዛት በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች 30 ደርሰዋል። አካባቢው ቦኮ ሀራም በስፋት የሚንቀሳቀስበት በመሆኑ የበሽታው ስርጭት ሊጨምር ይችላል የሚል ስጋት አለ።

  3. ዩናይትድ ኪንግደም በኮቪድ-19 የሞቱ ቁልፍ ሠራተኞችን አሰበች

    ዩናይትድ ኪንግደም በኮሮናቫይረስ ሳቢያ ሕይወታቸው ያለፉትን ቁልፍ ሠራተኞች በአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት አሰበች

    በፕሮግራሙ ላይ የመንግሥት ሠራተኞች የተሳተፉ ሲሆን ሌሎችም መካፈላቸውን ባለስልጣናት አስታውቀዋል፡፡

    ፕሮግራሙ እንዲካሄድ በሮያል የአዋላጅ ነርሶች ኮሌጅ፣ በሮያል የነርሲንግ ኮሌጅ እንዲሁም በዩኒሰን ንግድ ሕብረት ዘመቻ ከተካሄደ በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ሐሳቡን ደግፈውታል፡፡

    በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ቢያንስ 90 የብሔራዊ ጤና አገልግሎት ሠራተኞች በቫይረሱ ሕይወታቸው አልፏል፡፡

    ከእነዚህ መካከል አብዛኞቹ የእንክብካቤና የትራንስፖርት አገልግሎት ሠራተኞች መሆናቸው ተነግሯል፡፡

  4. እድሜያቸው ከ55 ዓመት በላይ የሆነ የሙምባይ ፖሊሶች በቤት እንዲቆዩ ተነገራቸው

    በህንዷ ከተማ ሙምባይ የሚገኙ ፖሊሶች እድሜያቸው ከ55 ዓመት በላይ ከሆነ በቤታቸው እንዲቆዩ ተነገራቸው፡፡

    ትዕዛዙ የተላለፈው ሦስት ፖሊሶች በኮቪድ -19 ሳቢያ ከሞቱ በኋላ ነው፡፡

    ባለሥልጣናት እንዳሉት እድሜያቸው የገፋ ፖሊሶች የእንቅስቃሴ ገደቡ እስከሚያበቃበት የፈረንጆቹ ሜይ 3 ድረስ በቤታቸው ይቆያሉ፡፡

    ሰኞ እለት በከተማዋ የ56 ዓመቱ ፖሊስ በቫይረሱ ተይዞ በሕክምና ክትትል ላይ እያለ ሕይወቱ ማለፉን የአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡

    ሙምባይ በህንድ ምዕራባዊ ግዛት ማሃራሽትራ ውስጥ የምትገኝ ከተማ ናት፡፡ በህንድ በአጠቃላይ በቫይረሱ ከተያዙ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛው የተመዘገበውም በዚችው ግዛት ነው፡፡ በግዛቷ ማክሰኞ እለት ብቻ ከ500 በላይ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው መረጋገጡን የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያሳያል፡፡ ይህም በግዛቷ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር ከ8 ሺህ 500 በላይ አድርሶታል፡፡

  5. በኢትዮጵያ ኮሮናቫይረስ የተገኘባቸው ሰዎች 126 ደረሰ

    ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ በተካሄደ 1080 የላብራቶሪ ምርመራ ሁለት ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው መረጋገጡን ጤና ሚንስቴር አስታወቀ።

    እስካሁን ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች 126 የደረሱ ሲሆን፤ ዛሬ ቫይረሱ እንዳለባቸው የተገለጸው ሁለት ግለሰቦች ከእንግሊዝ መጥተው በለይቶ ማቆያ የነበሩ ናቸው ተብሏል።

    በለይቶ ህክምና ውስጥ 71 ህሙማን አሉ። 50 ሰዎች ደግሞ ከቫይረሱ አገግመዋል።

  6. በኒው ዮርክ ጥንዶቹ በኦንላይን ጋብቻቸውን ፈጸሙ

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በዓለም ላይ በሺህዎች የሚቆጠሩት ሰርጋቸውን ለመሰረዝ ተገደዋል፡፡

    ይህንን ችግር ለመፍታት በቫይረሱ ክፉኛ በተመታችው የአሜሪካዋ ከተማ ኒው ዮርክ በቪዲዮ ሰርግ ማካሄድ ሕጋዊ ሆኗል፡፡

    ይህንን እድል ከተጠቀሙት ጥንዶች መካከል ደግሞ ሳያካ ፉኩዳ እና ጀምስ ስቶር ብራውን ይጠቀሳሉ፡፡

    ጀምስ እንደሚለው ሰርጋቸውን ጃፓንና እና ኒዮርክ ለማድረግ አስበው ነበር፡፡ በሚቀጥለው ወር ጋብቻቸውን ለመፈጸም አቅደው ነበር፤ ከዚያም ሰኔ ላይ ደግሞ ኒው ዮርክ ላይ በርካታ ጓደኞቻቸውና ቤተሰቦቻችን በተገኙበት ለመቀላቀል አስበው ነበር፡፡

    "ነገር ግን ፌብሩዋሪ መጀመሪያ ላይ ይህ ሊሆን እንደሚችል እርግጠኞች ነበርን፡፡ ምክንያቱም ምን ሊፈጠር እንደሚችል የምናውቀው ነገር አልነበረም፡፡ ግን ያሰብነው አልሆነም" ብሏል።

    በመሆኑም የኒው ዮርክ ከተማ ከንቲባ አንድሪው ኮሞ በኦንላይን መጋባት እንደሚቻል ከፈቀዱ በኋላ ነበር በቴክኖሎጅ በመታገዝ ሰርጋቸውን ለማካሄድ የወሰኑት፡፡

    ሙሽራዋ ሳያካም በሰርጓ እለት አምራና ተውባ ለመታየት ዲዛይነር መሆኗ እንደጠቀማት ተናግራለች፡፡

  7. ኢትዮጵያን ጨምሮ በርካታ አገሮችን እየረዳ ያለው ቢሊየነር ጃክ ማ ማነው?

  8. በ2020 የኮሮናቫይረስ ስርጭት ካልተገታ የቶኪዮ ኦሊምፒክ አይካሄድም

    በቀጣዩ ዓመት የኮሮናቫይረስ ስርጭት ካልተገታ የቶኪዮ ኦሊምፒክ እንደማይካሄድ አዘጋጅ ኮሚቴው ተናገረ።

    ዘንድሮ ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው ውድድሩ በአንድ ዓመት መገፋቱ ይታወሳል።

    የቶኪዮ 2020 ኢሊምፒክ ፕሬዘዳንት ዮሺሮ ሞሪ እንዳሉት ግን ውድድሩ ከአንድ ዓመት በላይ ዘግይቶም ሊካሄድ ይችላል።

    “በ2021 ቫይረሱ በቁጥጥር ሥር ካልዋለ ውድድሩ ይሰረዛል” ብለዋል።

    የጃፓን የሕክምና ማኅበር ኃላፊ ዮሺቴክ ዮኮኩራ፤ ለበሽታው ክትባት ካልተገኘ ውድድሩን ማካሄድ ከባድ ነው ብለዋል።

  9. በኢንዶኔዥያ ከ2 ሺህ በላይ ያልተመዘገበ ሞት አለ ተባለ

    በርካታ በማደግ ላይ ያሉ የዓለም አገራት በቫይረሱ የተያዙ አሊያም የሞቱ ሰዎች በይፋ የተመዘገበ ቁጥር ዝቅተኛ ነው። ይሁን እንጂ ቁጥሩ አገራቱ ካሳወቁት ሊበልጥ እንደሚችል ይታመናል።

    ለዚህም የኢንዶኔዥያን ማንሳት ይቻላል፤ በሮይተርስ የተሰራ አንድ ጥናት እንዳመላከተው ከ2 ሺህ 200 በላይ የቫይረሱ ምልክት የታየባቸው ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል። ነገር ግን ይህ ቁጥር ባለሥልጣናት ከመዘገቡትና በይፋ ካሳወቁት ቁጥር ጋር አልተካተተም።

    በኢንዶኔዥያ ከ10 ሺህ የሚያንሱ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውንና 765 ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው ማለፉን መንግሥት አስታውቋል።

    አገሪቷ የምታደርገው ምርመራ ቁጥር ዝቅተኛ በመሆኑም በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል ስጋትን ፈጥሯል።

  10. በኒው ዮርክ ዋነኛዋ ዶክተር እራሷን አጠፋች

  11. የተባበሩት መንግሥታት በወረርሽኙ ወቅት ያልተገባ ኃይል የሚጠቀሙ አገራትን አስጠነቀቀ

    የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብት ቢሮ በኮቪድ- 19 ወረርሽኝ ወቅት የኃይል እርምጃ የሚወስዱ አገራትን አስጠነቀቀ።

    ኤጀንሲው ‘ችግሩ ቫይረሱ እንጂ ሰዎች እንዳልሆኑ’ መንግሥታት ሊረዱ ይገባል ሲል አሳስቧል፡፡

    ወረርሽኙን ለመግታት የተጣሉ ገደቦችን ለማስፈጸም የጸጥታ ኃይሎች ያልተገባ እርምጃ ከሚወስዱባቸው አገራት መካከል ደቡብ አፍሪካ፣ ኬንያ ፣ ኡጋንዳ እና ሩዋንዳ ይገኙበታል፡፡

    የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ሚሼል ባቼሌት፤ አገራት ዜጎችን ለመቆጣጠርና ለመጨቆን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን እንደ መሳሪያ መጠቀም የለባቸውም ብለዋል፡፡

    ሚሼል አክለውም የእለት ጉርሳቸውን ለመፈለግ ሲሉ የሰዓት እላፊ የጣሱ ሰዎችን መግደል ፣ ማሰርና በእነርሱ ላይ ጥቃት መፈጸም ተቀባይነት የሌለውና ሕጋዊ አይደለም ሲሉ ድርጊቱን ኮንነዋል፡፡

    እርሳቸው የሚመሩት ቢሮ እንዳስታወቀው ከ17 ሺህ በላይ የደቡብ አፍሪካ ዜጎች ከኮቪድ-19 ገደቦች ጋር በተያያዘ ለእስር ተዳርገዋል፡፡

    በኬንያም የሰዓት እላፊውን የሚጥሱ ሰዎችን ወደ ለይቶ ማቆያ ማዕከላት እንዲገቡ መደረጉን ተከትሎ 27 የሚደርሱ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች መንግሥት ከዚህ ድርጊቱ እንዲታቀብ የሚጠይቅ ደብዳቤ ጽፈዋል፡፡

    እስካሁን በ52 የአፍሪካ አገራት 32 ሺህ 100 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ሲረጋገጥ 9 ሺህ 741 ሰዎች ከቫይረሱ አገግመዋል፡፡ 1 ሺህ 428 ሰዎች ደግሞ ህይወታቸው አልፏል፡፡

  12. ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቻይና ላይ ቅሬታቸውን አሰሙ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቻይና የኮሮናቫይረስን በተመለከተ በተከተለችው መንገድ ደስተኛ አለመሆናቸውን ለጋዜጠኞች ተናገሩ።

    ፕሬዝዳንቱ ቻይና የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ገና ከመነሻው ልታስቆመው ትችል እንደነበር በመናገር ነው ቅሬታቸውን ያቀረቡት።

    "ማንም ሰው አሁን ለተፈጠረው ነገር አንድ አገር ተጣያቂ ሊሆን ይችላል ብሎ አይጠብቅም” ሲሉም ተናግረዋል።

    ቻይና የወረርሽኙን መከሰት በተመለከተ ገና በተቀሰቀሰበት ወቅት የሚያስፈልጉ መረጃዎችን በመስጠት በኩል ግልጽነት አልነበራትም የሚል ክስ በተደጋጋሚ ቢቀርብባትም አሁንም ድረስ እያስተባበለች ነው።

  13. አርጀንቲና ለተጨማሪ አራት ወራት በረራዎችን አገደች

    አርጀንቲና በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት እስከ መስከረም ድረስ ሁሉንም የአገር ውስጥና የውጭ የመንገደኞች በረራን አገደች።

    አየር መንገዶች ለመጪዎቹ አራት ወራት ማንኛውንም የመንገደኞች አውሮፕላን በረራ ማድረግ ስለማይችሉ ከወዲሁ ትኬት እንዳይሸጡ ባለስልጣናት አሳስበዋል።

    በዚህም ምክንያት በሺህዎች የሚቆጠሩ ሠራተኞች ሥራቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ የአቪዬሽን ቡድኑ አስታውቋል።

    የብሔራዊ ሲቪል አቪዬሽን አስተዳደር የመንገደኞች በረራ እንዲቋረጥ ውሳኔ ያሳለፈው ትናንት ነበር። እገዳው በአገሪቷ ባለስልጣናት አልጸደቀም ተብሏል።

    አርጀንቲና ከባለፈው ወር አንስቶ የነዋሪነት ፈቃድ ለሌላቸው ሰዎች ድንበሯን መዝጋቷ የሚታወስ ሲሆን አስገዳጅ የለይቶ ማቆያ እርምጃዎችንም ወስዳለች።

    እንደ ጆንስ ሆፕኪንስ መረጃ አገሪቷ እስካሁን 4 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 192 ሞት መዝግባለች።

  14. እውን የትግራይ ክልል የራሱን ምርጫ ማካሄድ ይችላል?

  15. በኮሮናቫይረስ በተያዙ ህፃናት ላይ ያልተለመደ ምልክት መታየቱ ተገለፀ

    የብሔራዊ ጤና አገልግሎት (ኤንኤችኤስ) የሕክምና ባለሙያዎች ሕፃናት ላይ ያልተለመደ ነገር ግን አደገኛ የሆነ ምልክትን በሚገባ እንዲመለከቱ አስጠነቀቀ።

    ይህ ለዶክተሮቹ የተገለፀው ምናልባት ያልተለመደው ምልክት የኮሮናቫይረስ ኢንፌክሽን ምልክት ሊሆን ይችላል በሚል ነው።

    ለጠቅላላ ሐኪሞች በአስቸኳይ የተላከው መልዕክት እንደሚለው ከሆነ በሎንዶንም ሆነ በዩናይትድ ኪንግደም የተለያዩ አካባቢዎች በጽኑ ሕሙማን ክፍል የሚገኙ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሕፃናት ያልተለመዱ ምልከቶች እንደሚታይባቸው ይጠቅሳል።

    ይህም ከፍሉ ምልክት በተጨማሪ "የተለያዩ አካል ክፍሎች በአንድ ላይ መቆጣት"መሆኑን በመጥቀስ እንዲህ አይነት ምልክት ከታየባቸው ህፃናት መካከል አንዳንዶቹ በኮሮናቫይረስ ተይዘው መገኘታቸውን ይገልፃል። ዝርዝሩን ከእዚህ ያንብቡ፡ በዩናይትድ ኪንግደም ኮሮናቫይረስ በተያዙ ህፃናት ላይ ያልተለመደ ምልክት መታየቱ ተገለፀ

  16. የሰኞ ሚያዝያ 20/2012 ዓ.ም የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ

    እንደምንአደራችሁ?

    ሰኞ ሚያዝያ 20/2012 ዓ. ም የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ እነሆ ጀመረ።

    በዚህ የቀጥታ ዘገባ ገጽ ከኢትዮጵያ፣ ከአፍሪካ በአጠቃላይ ደግሞ ከዓለም ዙሪያ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ዙሪያየ ሚወጡ ዜናና መረጃዎችን እናቀርባለን።

    ባገኛችሁት አጋጣሚ ሁሉ የቀጥታ ዘገባገ ጻችንን እንድትጎበኙ በአክብሮት እንጋብዛለን ። መልካም ዕለት!

  17. የቤልጄም አርሶ አደሮች ብዙ ድንች ጥብስ ብሉ አሉ

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት ምርታቸውን ለውጪ ገበያ ማቅረብ ያልቻሉ የቤልጄም አርሶ አደሮች፤ ዜጎች ብዙ ድንች ጥብስ እንዲበሉ እየተማጸኑ ነው።

    ከወትሮውም ቤልጄማውያን ድንች ጥብስ ይወዳሉ፤ ያዘወትራሉም። አሁን ደግሞ አርሶ አደሮች ቢያንስ በሳምት ሁለቴ ድንች ጥብስ ብሉ ብለዋል።

    የድንች አምራቾች ማህበር እንዳለው፤ 750,000 ቶን ድንች ተከማችቷል።

    ካለፈው ወር አጋማሽ ጀምሮ የቤልጄም ሬስቶራንቶች ዝግ ናቸው። የቤልጄም የበጋ ፌስቲቫል መሰረዙም ድንች ያለ ገዢ እንዲከማች ምክንያት ሆኗል።

    ቤልጄም በዓለም ግንባር ቀደም ድንች ላኪ አገር ናት። በዓመት ለ100 አገራት 1.5 ሚሊዮን ቶን ታከፋፍላለች።

  18. ታዋቂ የፊልም ፌስቲቫሎች በዩቲዩብ ሊታዩ ነው

    እውቆቹ የፊልም ፌስቲቫሎች በርሊን፣ ካንስ፣ ቶሮንቶ እና ቪንስ ተጣምረው የድረ ገጽ መሰናዶ ሊያቀርቡ ነው።

    We Are One ወይም ‘አንድ ነን’ የተሰኘው መሰናዶ ግንቦት 29 በዩቲዩብ ይሰራጫል።

    የፊልም ፌስቲቫሎች እንደሌሎች መሰናዶዎች ሁሉ በኮሮናቫይረስ ሳቢያ ተሰርዘዋል።

    ለአስር ቀናት የሚቆየው መሰናዶ፤ ለዓለም ጤና ድርጅት ገንዘብ ማሰባሰቢያ ጭምርም ነው።

    የለንደን፣ የእየሩሳሌም፣ የሙምባይ እና ሌሎችንም ጨምሮ 20 የፈልም ፌስቲቫሎች ይሳተፋሉ።

    በሮበርት ዲኒሮ እና ጄን ሮዘንታል ጥምረት የተመሰረተው የመላው ዓለም ፊልም ሰሪዎችን ያስተሳስራል፤ ለተመልካቾች የአዕምሮ እረፍት ይሰጣልም ተብሏል።

    ዝግጅቱ የሚታየው በነጻ ሲሆን፤ ዘጋቢ ፊልሞች፣ ሙዚቃና ሌሎችም መዝናኛዎች ይቀርባሉ ተብሏል።

  19. አሜሪካ ለዓለም ጤና "ከየትኛውም አገር በላይ" እያደረገች ነው

    የአሜሪካ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ማይክ ፖምፒዮ አገራቸው ከማንኛውም አገር በበለጠ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመዋጋት የሚደረገውን ጥረት እየደገፈች ነው አሉ።

    ከአፍሪካ የተለያየ አገራትና መገናኛ ብዙኀን ለተውጣጡ ጋዜጠኞች በስልክ ቃለ መጠይቅ በሰጡበት ወቅት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ላይ የሚቀርበው ትችትና ወቀሳ ከተሰሳተ መረጃ በመነሳት ነው ብለዋል።

    ማይክ ፖምፒዮ አሜሪካ ምንም እንኳ ለዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት የምታደርገውን ድጋፍ ብታቋርጥም ከመቼውም ጊዜ በላይ በዓለም አቀፍ ጤና ላይ ገንዘቧን ማፍሰስ ትፈልጋለች ብለዋል።

    የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ፖምፒዮ ማንም አገር አድርጎትም የማያውቀውንና ሊያደርገውም በማይችለው መልኩ ለዓለም አቀፍ ጤና እንታገላለን ብለዋል።

    ውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ አገራቸው በአፍሪካ ብቻ በኮሮናቫይረስ መከላከል ላይ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ 170 ሚሊየን ዶላር ለማፍሰስ በጅታለች ብለዋል።

    ፖምፒዮ አክለውም የውጪ አገር መንግሥታትና መገናኛ ብዙኀን ስለ መንግሥታቸው የተሳሳተ መረጃ እያሰራጩ መሆኑን ጠቅሰው ይህ ደግሞ የአፍሪካ አገራትን ትንሽ እርዳታ እየሰጧቸው ወደማይወጡት ብድር እየከተቷቸው ነው ሲሉ ተችተዋል።

  20. በዩናይትድ ኪንግደም በኮቪድ-19 የሞቱት ሰዎች ቁጥር ከ21,000 በላይ መሆኑ ተገለፀ

    የዩናይትድ ኪንግደም የጤና ሚንስቴር እስካሁን ድረስ በኮሮናቫይረስ ከተያዙት መካከል 21,092 ሰዎች መሞታቸውን አስታወቀ።

    ከሞቱት መካከል የጤና ባለሙያዎች የሚገኙበት ሲሆን እነዚህም 82 የብሔራዊ ጤና አገልግሎት (ኤንኤችኤስ) አባላት፣ 16 ደግሞ እንክብካቤ ሰጪ ባለሙያዎች መሆናቸው ተገልጿል።

    በዩኬ ባለፉት 24 ሰዓታት ብቻ 360 በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል።

    በተጨማሪም " ከነገ ጀምሮ የብሔራዊ ጤና አገልግሎት (ኤንኤችኤስ) ሌሎች አገልግሎቶች፣ እንደ ካንሰርና የአእምሮ ጤና ያሉት፣ መሰጠት ይጀምራሉ" ተብሏል።

    "የጤና አገልግሎቶቹ ሙሉ በሙሉ መሰጠት የሚጀምሩት መቼ እንደሆነ የሚወሰነው በህብረተሰቡ ውስጥ ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ከታየ በኋላ ነው" ብለዋል የጤና ሚኒስትሩ ሃንኩክ።