በዓለም ላይ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ3 ሚሊዮን አለፈ

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የምድራችንን ነዋሪ ጤናና ህይወት አደጋ ላይ ከመጣሉ ባሻገር የዓለምን ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴ ክፉኛ አስተጓጉሏል። በበሽታው ክፉኛ የተጠቁ አገራት ውስጥ በወረርሽኙ ሳቢያ የሚሞቱ ሰዎች አሃዝ ባለፉት ጥቂት ቀናት የመቀነስ አዝማሚያ እንደታየ ቢዘገብም አሳሳቢነቱ ግን ገና አልተወገደም። እስካሁን በኮቪድ-19 በመላው ዓለም ከ3 ሚሊዮን በላይ ሰዎች እንደተያዙ የተረጋገጠ ሲሆን ከ200 ሺህ የሚበልጡ ሰዎች ደግሞ ለሞት ተዳርገዋል።እኛም ከእዚህ አሃዝ ውስጥ ላለመግባት ሳንዘናጋ የመከላከያ መንገዶች ተግባራዊ እናድርግ። ስለበሽታው ትኩስ ዜናና መረጃ ለማግኘት የቀጥታ ዘገባ ገጻችንን ተከታተሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኤርትራ ከኮሮና ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 19 ደረሰ

    በኤርትራ በዛሬው እለት ተጨማሪ ስድስት ሰዎች ማገገማቸውን የሃገሪቱ የጤና ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። ያገገሙት ሰዎችም ምርመራ ተደርጎላቸውም ወደ ቤታቸው ተሸኝተዋል።

    በአገሪቱ ውስጥ ከኮሮና ያገገሙ ሰዎችም ቁጥር አስራ ዘጠኝ ደርሷል።

    እስካሁን ባለው መረጃ በኤርትራ ውስጥ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች 39 መሆናቸውንም የጤና ሚኒስቴሩ መግለጫ አመላክቷል።

    አገሪቷ የቫይረሱን መዛመትም ለመቆጣጠር ቤት መቀመጥን ጨምሮ ሌሎች መመሪያዎችንም አስተላልፋለች።

  2. በአራት ሰአታት ውስጥ የኮሮናቫይረስ የምርመራ ውጤት ማወቅ ተቻለ

    በአራት ሰአታት ውስጥ የኮሮናቫይረስ የምርመራ ውጤትን ማወቅ የሚቻልበትን መንገድ መፍጠር እንደተቻለ የኖርዝሃምፕተን አጠቃላይ ሆስፒታል አሳውቋል።

    ከዚህ ቀደም የምራቅ ናሙና ተወስዶ ከሆስፒታሉ ውጭ ወዳለ መመርመሪያ ጣቢያ ይላክ የነበረ ሲሆን በዚህም ሁኔታ አርባ ስምንት ሰአታትንም ይወስድ ነበር። በአሁኑ ወቅት ግን በሆስፒታሉ ባሉ ላብራቶሪዎች ናሙናዎች መመርመር ተጀምሯል።

    በሆስፒታሉ ውስጥ የአንደኛው የስራ ክፍል ዳይሬክተር የሆኑት ዶክተር ዴቪስ ቶማስ እንደሚሉት "ህሙማን ወደ ሆስፒታሎቻችን ሲመጡ ሳይጉላሉ ወደየትኛው መመርመሪያ ቦታ እንደሚሄዱ እናሳያቸዋለን። ፈጣን ምርመራ እናደርጋለን" ብለዋል።

    ሆስፒታሉ በአሁኑ ሰአት መቶ ሰዎችን በቀን የሚመረምር ሲሆን ለወደፊቱም አቅሙን በማጠናከር በርካታ ሰዎችን መመርመር እንደሚቻልም አሳውቋል።

  3. የማላዊ ፍርድ ቤት ከመንግሥት በተቃራኒ ቤት የመቀመጥ ውሳኔ አይተላለፍም አለ

    የማላዊ መንግሥት አስገዳጅ የቤት መቀመጥ ውሳኔ አስተላልፋለሁ ቢልም የማላዊ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ግን ለሁለተኛ ጊዜ ውሳኔውን ሽሮታል።

    ፍርድ ቤቱ መንግሥት የጠየቀውን አስገዳጅ ቤት ውስጥ የመቀመጥ ውሳኔ ገምግሞ ያፀድቀዋል ተብሎ ቢጠበቅም በተቃራኒው ውሳኔ ላይ ደርሷል።

    በማላዊ ያለ የሰብአዊ መብት ጠባቂ ጥምረት ቤት የመቀመጥ ውሳኔ ቢተላለፍ አቅም የሌላቸው በርካታ ማላውያን ለረሃብና ለችግር እንደሚጋለጡ በመጠቆም፣ መንግሥት ነፃ ምግብ እስካላከፋፈለ ድረስ ውሳኔ ሊያልፍ አይገባም በሚልም የፍርድ ቤት ማገጃ በመንግሥት ላይ ጠይቋል።

    የፍርድ ቤት ማገጃ በዚህ ድርጅት ብቻ ሳይሆን የተለያዩ የሃይማኖት ቡድኖችም ከእምነት ነፃነት ጋር የሚጣረስ ነው በሚል ለፍርድ ቤቱ ተቃውሟቸውን አቅርበዋል።

    ፍርድ ቤቱም በወረርሽኙ ወቅት የተነሱ ህገመንግሥታዊ አተረጓጎም የሚያስፈልጋቸው ጥያቄዎች ስላሉ ቤት የመቀመጥ ውሳኔ እንዲዘገይና፤ በአሁኑ ሰአትም እንደማይተላለፍ አሳውቋል።

    በማላዊ 36 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን፤ ሶስት ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

  4. ኡጋንዳ የኮቪድ-19 ህሙማን አሽከርካሪዎችን ወደየሃገራቸው መልሳለች የሚለውን አስተባበለች

    የኡጋንዳ ጤና ሚኒስቴር 14 ኮሮናቫይረስ የተያዙ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ወደየሃገራቸው እንዲመለሱ አድርጋለች የሚለውን አስተባብላለች።

    ሚኒስትሯ ጄን አቼንግ እንዳሉት አንድ አሽከርካሪ ብቻ ወደመጣበት እንዲመለስ የተደረገ ሲሆን ሌሎቹ አስራ ሶስቱ በፍቃዳቸው እንደተመለሱ ገልፀዋል።

    በዚህ ሳምነት ሰኞ የአገሪቷ የጤና አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሄንሪ ምዌብሳ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው የተረጋገጡ አስራ አራት አሽከርካሪዎች ወደየአገራቸው መመለሳቸውን ገልፀው ነበር።

    ይህንንም ተከትሎ በርካታ ኬንያውያንና ታንዛኒያውያን በተለያዩ ማህበራዊ ድረገፆች አስራ ሶስቱ አሽከርካሪዎች በምን መንገድ ወደየሃገራቸው እንደተመለሱ ዘርዘር ያለ ማብራሪያ ሊሰጠን ይገባል ሲሉ ጠይቀዋል።

    እስካሁን ባለው መረጃ በኡጋንዳ 79 ግለሰቦች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    በተለይም የኬንያና የታንዛንያ ድንበርን የሚሻገሩ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    ይህንንም ተከትሎ የኬንያ መንግሥት ድንበር ተሻጋሪ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ሳይመረመሩ ወደ ሃገሪቷ እንዳይገቡ ውሳኔ አስተላልፏል።

  5. የአሜሪካው አየር መንገድ ሁሉም መንገደኞች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲያደርጉ ወሰነ

    ጄትብሉ የተሰኘው የአሜሪካ አየር መንገድ ሁሉም መንገደኞቹ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲያደርጉ ወሰነ።

    አየር መንገዱ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ መንገደኞች አውሮፕላን ጣብያው ከደረሱበት ጊዜ ጀምሮ ጉዟቸውን አጠናቅቀው እስኪወርዱ ድረስ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲያደርጉ ይጠየቃሉ ብሏል።

    በዚህ የአየር መንገዱ መመሪያ ውስጥ ያልተካተቱት ጭምብል ማድረግ የማይገደዱት ጨቅላ ሕፃናት ብቻ መሆናቸው ተገልጿል።

    " የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ ራስን መከላከል አይደለም፤ በዙሪያዎ ያሉትን መከላከል ነው" ያሉት የጄት ብሉ ፕሬዝዳንት ጆና ጌሬጌቲ ናቸው።

    " ይህ አዲሱ የበረራ ስነምግባር ነው" ብለዋል አክለው። የአየር መንገዱ ደንበኞች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲያደርጉ የሚገልጽ ኢሜል የሚላክላቸው ሲሆን የራሳቸውን ጭምብል ወጪም ራሳቸው እንደሚችሉ ተገልጿል።

  6. በብሩንዲ የሚካሄዱ ትላልቅ ሕዝባዊ ስብሰባዎች የኮሮና ወረርሽኝን እንዳያባብሱት ተሰግቷል

    በብሩንዲ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ለፖለቲካ ድጋፍ አደባባይ መውጣታቸውን ተከትሎ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሊስፋፋ ይችላል የሚል ስጋት አጭሯል።

    የተላላፊ በሽታዎች ባለሙያ የሆኑት ኦሊቨር ማንኢ እንደዚህ አይነት ትልልቅ ስብሰባዎች ለቫይረሱ መስፋፋት ሁነኛ መንገድ ናቸው ብለዋል ለቢቢሲ።

    የዓለም ጤና ድርጅትም ቢሆን በወረርሽኙ ወቅት ሰዎች አካላዊና ማህበራዊ ርቀታቸውን እንዲጠብቁ ይመክራል።

    የብሩንዲ ምርጫ ኮሚሽን የገዢው ፓርቲና ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ባዘጋጇቸው የፖለቲካ ድጋፍ ሰልፎች ላይ ውሃና ሳሙና አቅርቧል።

    አንድ የድጋፍ ሰልፉ ተሳታፊ" በሰልፉ ላይ የተገኙ ሰዎችን ሁሉ እጅ ለማስታጠብ ወይንም በሳኒታይዘር ለማጽዳት የሰዉ ቁጥር እጅግ ብዙ ነበር" ብለዋል።

    ብሩንዲ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል በሚል ድንበሯን ከዘጋች ቆይታለች።

    በመላው አገሪቱ መንግሥት ሰዎች እጃቸውን እንዲታጠቡ እንዲሁም እንዳይጨባበጡ የሚያስተምር ሲሆን ከዚያ በዘለለ ግን ሕይወት እንደቀድሞው መቀጠሉን ታዛቢዎች ይናገራሉ።

    በብሩንዲ እስካሁን ድረስ 14 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ሲታወቅ አንድ ግለሰብ ደግሞ ሞቷል።

    የብሩንዲ መንግሥት ምንም እንኳ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ቢከሰትም ከ20 ቀን በኋላ ምርጫ እንዲካሄድ ወስኗል።

  7. አሜሪካዌው ራፐር ለቤት አልባ ምንዱባን ምግብ ሰጠ

    በአሜሪካዋ ጆርጂያ ግዛት የምግብ ቤት ባለቤቶች ስራ እንዲጀምሩ ሲነገራቸው ሁሉም በአንድነት ወደ ስራ አልገቡም። አሜሪካዊው ራፐር '2 ቼንዝ' በአትላንታ የሚገኘውን ኤስኮባር ምግብ ቤቱን ከመክፈት ይልቅ ለቤት አልባዎች ምግብ መስጠትን መርጧል።

    2 ቼንዝ ከተዘጋ የንግድ ስፍራው ውጪ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንዲሁም ጓንት አድርጎ ምግብ ሲያድል ታይቷል።

    የአሜሪካዋ ጆርጂያ ግዛት አስተዳዳሪ ብሪያን ኬምፕ በግዛቲቱ የሚገኙ ምግብ ቤቶች በአጠቃላይ ከሰኞ ዕለት ጀምሮ ወደ ስራ እንዲገቡ ጥሪ አስተላልፈው ነበር።

    ባለፈው አርብ ደግሞ የውበት ሳሎኖች፣ የአካል እንቅስቃሴ ማዘውተሪያ ስፍራዎች እንዲከፈቱ ተወስኖ ነበር።

    በጆርጂያ ብቻ ወደ 24 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሲሆን አንድ ሺህ ሰዎች ደግሞ መሞታቸው ታውቋል።

  8. በፈረንሳይ የእንቅስቃሴ ገደቡ የ62 ሺህ ሰዎችን ህይወት መታደግ ችሏል ተባለ

    የፈረንሳይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኤዶዋርድ ፍሊፕ አገራቸው የጣለችው የእንቅስቃሴ ገደብ በአንድ ወር ውስጥ ብቻ የ62 ሺ ሰዎችን ህይወት መታደጉን ተናገሩ።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ፍሊፕ ከሁለት ሳምንት በኋላ ቀስ በቀስ የእንቅስቃሴ ገደቡ እንደሚነሳ አስታውቀዋል።

    በፈረንሳይ ወደ 23 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ምከንያት ሲሞቱ 165 ሺ 842 ሰዎች ደግሞ ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ተገልጿል።

  9. በዩናይትድ ኪንግደም ኮሮናቫይረስ በተያዙ ህፃናት ላይ ያልተለመደ ምልክት መታየቱ ተገለፀ

  10. በዩኬ በኮሮናቫይረስ ምክንያት በእንክብካቤ ማዕከላት የሚሞቱ ሰዎች አሳሳቢ ነው ተባለ

    በዩኬ በኮሮናቫይረስ ከሚሞቱት መካከል በእንክብካቤ ማዕከላትና በየቤታቸው የሚሞቱት አንድ ሶስተኛውን እንደሚይዝ የወጡ መረጃዎች ያሳያሉ።

    የብሔራዊ ስታቲስቲክስ መረጃ እንደሚያሳየው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በአገሪቱ ከገባበት ጀምሮ በእንክብካቤ ማዕከላት 3ሺ096 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ምክንያት ሞተዋል። ይህ ቁጥርም በከፍተኛ ሁኔታ ሊጨምርም እንደሚችል እየተነገረ ነው።

    በአገሪቱ ሆስፒታሎች ውስጥ በኮሮናቫይረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከሃያ ሺ በላይ የሆነ ሲሆን ከሰሞኑ ግን መቀነስ አሳይቷል ተብሏል።

    በተቃራኒው በእንክብካቤ ማእከላት የሚሞቱ ሰዎች በከፍተኛ ሁኔታ ጭማሬ ማሳየቱ ብዙዎች አሳሳቢ እንደሆነ እየገለፁ ነው። የሌበር ፓርቲ ለዩኬ መንግሥት በፃፈው ደብዳቤ በእንክብካቤ ማእከላት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር አሳሳቢ እንደሆነና፣ መንግሥትም የዜጎችን ሞት ለመከላከል የተጠናከረና የተቀናጀ ስራ መስራት እንዳለበት አሳስቧል።

  11. በሩሲያ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከቻይናና ኢራን በለጠ

    በሩሲያ በኮሮናቫይረስ አዲስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከቻይናና ከኢራን መብለጡ ተነገረ።

    የሩሲያ መንግሥት ዛሬ እንዳስታወቀው በአንድ ቀን በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ቁጥር በ6ሺህ 411 ከፍ ብሏል።

    ይህም በአገሪቱ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎችን ቁጥር ወደ 93,558 ከፍ ያደረገው ሲሆን ከእነዚህም መካከል 867 ሰዎች መሞታቸው ታውቋል።

    በሩሲያ ካሉ ግዛቶች በአጠቃላይ በሞስኮ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች በቫይረሱ ተይዘው እንደሚገኙ ተገልጿል።

  12. ቺሊ ከኮሮናቫይረስ ላገገሙ "ከቫይረሱ ነፃ" የሚል የምስክር ወረቀት ልትሰጥ ነው

  13. የማሌዥያ ከፍተኛ ባለስልጣን የእንቅስቃሴ ገደቡን በመጣስ ተቀጡ

    በእስያ ያሉ አገራት የኮሮናቫይረስን መከላከል በሚመለከት ምን እያደረጉ ነው?

    • የማሌዥያ ምክትል ጤና ሚኒስቴር አገራቸው የእንቅስቃሴ ገደብ ላይ ያስተላለፈችውን መመሪያ በመጣስ በአንድ እስላማዊ ትምህርት ቤት በመገኘታቸው ቅጣት ተጥሎባቸዋል። ኑር አዝሚ ጋዛሊ፣ በእስላማዊ ትምህርት ቤት ተገኝተው ከተማሪዎቹ ጋር ሲመገቡ የሚያሳይ ምስል በማህበራዊ መገናኛ ብዙኀን ከተለቀቀ በኋላ 325 ዶላር ተቀጥተዋል። ማሌዥያ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል ጥብቅ ነው የተባለ የእንቅስቃሴ ገደብ የጣለች ሲሆን መመሪያውን ጥሰው የተገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ መቀጣታቸው ተገልጿል።
    • ከ2ሺ 200 በላይ ኢንዶኔዢያውያን ከመሞታቸው በፊት ምንም እንኳ የኮቪድ-19 ምልክት ያሳዩ የነበረ ቢሆንም በኮሮናቫይረስ ምክንየት መሞታቸው አለመመዝገቡን የሮይተርስ የምርመራ ዘገባ ያሳያል። ኢንዶኔዢያ እስካሁን ድረስ 765 ሰዎች በቫይረሱ ምክንያት መሞታቸውን የመዘገበች ሲሆን የሕክምና ባለሙያዎች ግን ቁጥሩ ከዚህ ይልቃል እያሉ ነው።
    • በሲንጋፖር በኮሮናቫይረስ የተያዙ ስደተኛ ሰራተኞች ቁጥር አሁን ካለው ቁጥር ሊበልጥ ይችላል ተባለ። እስካሁን ባለው መረጃ በሲንጋፖር 15 ሺህ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የታወቀ ሲሆን እያንዳንዱ ስደተኛ ወደ ለይቶ ማቆያ ከመግባቱ በፊት ሲመረመር ያለው ሁኔታ በትክክል ይታወቃል ተብሏል።
  14. ኬንያ ድንበር ተሻጋሪ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎችን ኮቪድ-19 እየመረመረች ነው

    በኬንያና በኡጋንዳ ድንበሮች ላይ አስገዳጅ የሆነ የኮሮናቫይረስ ምርመራ ማድረግ የሚጠበቅባቸው የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ረዣዥም ሰልፍ ይዘው እንደሚታዩ ተገለፀ።

    የከባድ ጭነት መኪኖቹ እስከ 40 ኪሎ ሜትር ድረስ ሰልፍ ሰርተው እንደሚታዩ ተገልጿል።

    አምስት የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች የኡጋንዳን ድንበር አልፈው ከገቡ በኋላ በተደረገላቸው ምርመራ ኮቪድ-19 ተኝቶባቸዋል።

    ይህም የኬንያ መንግሥት ለረዥም ርቀት አሽከርካሪዎች ምርመራ እንዲያደርግ አስገድዶታል።

    የድንበር አካባቢ ነዋሪዎች ሹፌሮቹ ምርመራ እስኪደረግላቸው ድረስ በአካባቢው ሲቆዩ ወዲያ ወዲህ ስለሚሉና ስለሚገበያዩ ቫይረሱን ያሰራጫሉ ሲሉ ይሰጋሉ።

    አንዳንድ አሽከርካሪዎች ምርመራው ዘገምተኛ ነው በሚል ቅሬታቸውን እያቀረቡ ሲሆን፣ ለምን 24 ሰዓት የምርመራ አገልግሎቱ አይሰጥም ሲሉ ይጠይቃሉ።

    የኬንያ የጤና ሚኒስቴር ወደ ድንበር ከተሞች በርካታ የጤና ባለሙያዎችመና የመመርመሪያ መሳሪያዎች እንደሚልክ አስታውቋል።

  15. ኡጋንዳ በየሳምንቱ 20 ሺህ ሰዎችን ለመመርመር አቅዳለች

    ኡጋንዳ ከ20 000 በላይ ሰዎችን በየሳምንቱ የኮቪድ-19 ምርመራ ለማድረግ አቅዳለች።

    ምርመራው የሚካሄደው የእንቅስቃሴ ገደቡ ከማብቃቱ በፊት ነው ተብሏል።

    የኡጋንዳ ጤና ሚኒስቴር እንዳሳወቀው ምርመራው የእንቅስቃሴ ገደቡ መቼ መላላት እንዲሁም መቼ ሙሉ በሙሉ መነሳት እንዳለበት ይጠቁማል።

    ኡጋንዳ 43 ሚሊዮን ሕዝብ ያላት ሲሆን እስካሁን ድረስ 79 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው በምርመራ ተረጋግጧል።

    በምርመራ ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል 20 ያህሉ የረዥም ርቀት መኪና አሽከርካሪዎች መሆናቸው የተገለፀ ሲሆን ፤ ኡጋንዳ ከፍተኛ ትኩረት አድርጋ ምርመራውን የምታደርገውም እነዚህ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ የሚሰሩ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ላይ መሆኑ ታውቋል።

    ምንም እንኳ የኡጋንዳ መንግሥት ማህበረሰቡን በመመርመር ረገድ በቂ ጥረት እያደረገ አይደለም በሚል ትችት ቢቀርብበትም ነጋዴዎች፣ የጤና ሰራተኞች፣ የኃይማኖት መሪዎችም እንደሚመረመሩ ተገልጿል።

    ኡጋንዳ ምርመራ ከምታደርግላቸው ሰዎች የደም ናሙና በመውሰድ በሽታውን ለመከላከል የሚያስችል 'አንቲቦዲ' መፈጠር አለመፈጠሩ እንደምታረጋግጥ ተገልጿል።

  16. ኮሮናቫይረስ ሁለቴ ሊይዘን ይችላል?

  17. የሕይወቱን የመጨረሻ ቀናት በብቸኝነት ያሳለፈው ሾፌር

    ለተሻለ ህይወት አገራቸውን ጥለው ወደ አውሮፓ እንደሚሄዱት በርካታ ስደተኞች ህንዳዊው ራጄሽ ጄያስሊንም ባለቤቱን፣ ልጆቹንና ቤቱን ትቶ ኑሮውን በለንደን አድርጓል። በለንደንም በኡበር አሽከርካሪነት ኑሮውን ይገፋል። ለከተማዋ ያለውንም ፍቅር በህንዷ ከተማ ባንጋሎር ለምትገኘው ባለቤቱ በተደጋጋሚ ይነግራት ነበር።

    ሆኖም ራጄሽ በኮሮናቫይረስ መያዙ ሲረጋገጥ የቤት አከራዩ ቤቱን ልቀቅ ብለው አስወጡት እናም ለተወሰኑ ቀናት መኪናው ውስጥ ለማደር ተገደደ። እንደምንም ብሎ ሌላ ቤት ቢያገኝም አምስት ሺ ዶላር ወዲያው እንዲከፍል ተነገረው።

    ብሩን አመጣለሁ ብሎ ቃል በመግባት ከዛሬ ነገ ያስወጡኛል ብሎ በፍራቻ ጥቂት ቀናትን አሳለፈ። በአንደኛው ቀን ግን መተንፈስ ሲያዳግተው ወደ ሆስፒታል አመራ፤ እናም ህይወቱ አለፈ።

    የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ለአለም ስጋት ቢሆንም፣ የኑሮ ሁኔታቸው ከእጅ ወደ አፍ በሆነው ማህበረሰብ ደግሞ ከፍተኛ ጫናን እያሳደረ ነው።

  18. የኤርትራውያን ስደተኞች ስጋት በኢትዮጵያ

  19. በአዲስ አበባ ሁለት ወጣቶች በጥይት የተመቱበት ክስተት ምንድን ነው?

  20. አንዳንድ አገራት በኮሮናቫይረስ ምክንያት የጣሉትን እገዳ እያነሱ ነው። እነማን?