ሰበር, በኢትዮጵያ በአንድ ቀን ውስጥ ሁለተኛው የኮሮናቫይረስ ታማሚ ህይወት አለፈ
የጤና ጥበቃ ሚኒስትሯ ዶ/ር ሊያ ታደሰ፣ እንዳሳወቁት የ56 ዓመቱ የበሽታው ተጠቂ የህክምና ክትትልና ድጋፍ ሲደረግላቸው ቆይተው በዛሬው ዕለት ህይወታቸው አልፏል።
ኢትዮጵያዊው ግለሰብ ሐሙስ መጋቢት 24/2012 ዓ.ም የኮሮናቫይረስ እንደተገኘባቸው ከተረጋገጠ በኋላ በለይቶ ህክምን መስጫ ማዕከል ውስጥ ክትትልና አስፈላጊው ህክምና ሲደረግላቸው እንደቆየ ተገልጿል።
ታማሚው ወደ ህክምና ማዕከሉ ከገቡበት ዕለት አንስቶ የጽኑ ህሙማን ክትትል ሲደረግላችው ቆይተው፣ እሁድ አመሻሽ 12 ሰዓት አካባቢ ላይ ነው ህይወታቸው ማለፉ የተነገረው።
ሁለተኛው ወንድ ሟች ይፋ ከመደረጉ ከሰዓታት በፊት የመጀመሪያዋ 60 ዓመት ኢትዮጵያዊት በበሽታው ሳቢያ ህይወታቸው ማለፉ ተገልጾ ነበር።
በዚህም በአገሪቱ በአንድ ቀን ውስጥ በኮቪድ-19 ምክንያት የመጀመሪያዎቹ ሁለት ሰዎች ህይወት አልፏል።
እስከ እሁድ ጠዋት አንድ ሰዓት ድረስ በኢትዮጵያ 1843 ሰዎች ላይ ምርመራ ተደርጎ በ43 ሰዎች ላይ ቫይረሱ ተገኝቷል።
ከእነዚህም መካከል አራቱ ከበሽታው ሙሉ በሙሉ መዳናቸው የተነገረ ሲሆን የሁለቱ ህይወት ደግሞ ዛሬ ማለፉን የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል::