ሶማሊያ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ ለጫት ታወጣው የነበረን 3 ሚሊዮን ዶላር አዳነች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ሶማሊያ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል ስትል ባለፈው ሳምንት ከዋና ከተማዋና ወደ ዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ በሚደረጉ የዓለም አቀፍ በረራዎች ላይ የጣለችው እገዳ አገሪቱ ለጫት የምታወጣውን የውጪ ምንዛሪ እንዳዳነላት ተነገረ።
ጫት እንዲታገድ በመቀስቀስ በቀዳሚነት የሚታወቁት አቡከር አዋሌ እንዳሉት በመንግሥት በጫት ንግድ ላይ በጊዜያዊነት የተጣለው እገዳ ከሦስት ሚሊዮን ዶላር በላይ እንዳዳነ አመልክተዋል።
ይህም ከጎረቤት አገራት ተመርቶ ወደ ዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ በአውሮፕላን በመምጣት ለከተማው ነዋሪ ይቀርብ ለነበረ ጫት የሚወጣ ወጪ እንደነበረ ተገልጿል።
የዓለም አቀፍ በረራዎች እገዳው ከተጣለ ሁለት ሳምንት እንኳን ሳይሞላው ነው ሦስት ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ የጫት ምርት ወደ ሶማሊያ ሳይገባ የቀረው ተብሏል።
በሶማሊያዊያን ወንዶች ዘንድ በስፋት ጥቅም ላይ የሚውለውን ጫት ብሔራዊ አደጋ ነው የሚሉት አቡካር አዋሌ፤ በኮሮናቫይረስ ምክንያት የተጣለው እገዳ በጫት ላይ በቋሚነት እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
ሶማሊያ ከፍተኛ መጠን ያለው ጫት በየዕለቱ የምታስገባ ሲሆን ከዚህ ውስጥ አብዛኛውን ከኬንያ ነበር የምታስመጣው። በበርካታ አገራት ውስጥ ጫትን መቃም ሕገ ወጥ ነው።
