የኢራን ፕሬዝዳንት “ጣቶቻችን አሁንም ቃታው ላይ ናቸው” ሲሉ አስጠነቀቁ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት አጠናክራ በቀጠለችበት በአሁኑ ጊዜ ኢራን በተጠንቀቅ ላይ እንደሆነች ፕሬዝዳንቷ አስታወቁ።
የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን እስራኤል ሊባኖስ ላይ የምትፈጽመው ጥቃትም "ግልጽ የተኩስ አቁም ጥሰት” ነው ብለዋል።
የእስራኤል ጥቃቶች መቀጠላቸው ሊደረስ ለሚችል ስምምነት ቁርጠኝነት እንደሚጎድል የሚሳይ “አደገኛ ምልክት” ነው ሲሉም ወቅሰዋል።
የኢራኑ ፕሬዝዳንት ይህንን አስተያየት በኤክስ ገጻቸው ያሰፈሩት የእስራኤል ጦር የሄዝቦላህ ዒላማዎች እንደሆኑ በገለጻቸው የሊባኖስ ስፍራዎች ላይ ከ100 በላይ የአየር ጥቃቶችን በፈጸመ ማግሥት ነው።
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያናሁ “አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ” ሄዝቦላህ ላይ ጥቃት እንደሚፈጽሙ በዛሬው ዕለት ተናግረዋል።
የኢራኑ ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን በኤክስ ልጥፋቸው የጥቃቶች መቀጠል ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን ድርድር ወደ “ትርጉም የለሽነት” እንደሚያወርደው ገልጸዋል። የኢራን ጣቶች “ቃታው ላይ ሆነው እንደሚቀጥሉም” ጽፈዋል።
የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ በበኩላቸው “የተኩስ አቁም ጥሰቶች ግልጽ ዋጋ” እንደሚያስከፍሉ እና “ጠንካራ ምላሽ” እንደሚያስከትሉ ተናግረዋል።
ሊባኖስ “የማትነጠል የተኩስ አቁሙ አካል” መሆኗን ገለጹት አፈ ጉባኤው ሞሐማድ ባገር ጋሊባፍ፤ “ለክህደት እና ማፈግፈግ የሚሆን ቦታ እንደሌለ” አሳስበዋል።
“በአስቸኳይ እሳቱን አጥፉ” ሲሉም አክለዋል።






















