ባለፉት ቀናት የሄዝቦላህ “ወታደራዊ መሠረተ
ልማቶች” ስትል በገለጸቻቸው ዒላማዎች ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ያባባሰችው እስራኤል፤ ከሊባኖስ ጋር የምታደርገው ድርድር በሚቀጥለው ሳምንት ዋሽንግተን ከተማ ውስጥ እንደሚካሄድ የአሜሪካ የውጭ
ጉዳይ መስሪያ ቤት አስታወቀ።
አሜሪካ እና ኢራን የደረሱት የተኩስ አቁም ሊባኖስንም
የሚያካትት የመሆን፣ አለመሆኑ ጉዳይ ሲያወዛግብ ከቆየ በኋላ በትናንትናው ዕለት የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ
ከሊባኖስ ጋር ድርድር እንዲጀመር ማዘዛቸውን አስታውቀዋል።
የሊባኖስ ባለሥልጣናት የተኩስ አቁም ተደርጎ
ድርድር እንዲጀመር ጠይቀዋል። ከዚህ ጥያቄ በኋላ ለሰሜናዊ እስራኤል ነዋሪዎች መልዕክት ያስተላለፉት ኔታንያሁ ግን “ሊባኖስ ውስጥ
የተኩስ አቁም አይኖርም” ብለዋል።
እስራኤል በሊባኖስ የምትፈጽማቸው ጥቃቶች
ባለፉት ቀናት በከፍተኛ መጠን ጨምረው ከቆዩ በኋላ ከትናንት ምሽት አንስቶ ለጊዜው ጋብ ያለ ይመስላል። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለኤንቢሲ ኒውስ በሰጡት ቃለ መጠይቅ፤ እስራኤል የሰላም ንግግሩን ለማገዝ ሲባል የምትፈጽመውን ጥቃት “እየቀነሰች” መሆኑን ገልጸዋል።
“ከቢቢ [የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚስትር] ጋር ተነጋግረናል፤ እናም [ጥቃቱን]
ይቀንሰዋል። ከዚህም የበለጠ መቀነስ እንዳለብን አስባለሁ” ሲሉ ከኔታንያሁ ጋር በስልክ ካደረጉት ንግግር በኋላ አቋማቸውን አስረድተዋል።
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት መረጃ እንደሚያመለክተው
እስራኤል እና ሊባኖስ በሚቀጥለው ሳምንት “ዋሽንግተን ውስጥ እየተተገበረ ስላለው የተኩስ አቁም ድርድር” ይነጋገራሉ።
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ትናንት ባስተላለፉት
መልዕክት ከሊባኖስ ጋር የሚደረገው ድርድር ሄዝቦላህን እና በኢራን የሚደገፉ አማጺ ቡድኖችን ትጥቅ ማስፈታት ላይ እንደሚያተኩር
ገልጸዋል። በሁለቱ አገራት መካከል ሰላማዊ ግንኙነት የመመስረት ጉዳይም የድርድሩ አካል ነው ተብሏል።
ይሁን እንጂ የሊባኖስ መንግሥት እና እስራኤል
የሚያደርጉት ድርድር ሄዝቦላህ ላይ ምን አይነት ተጽዕኖ እንደሚኖረው ግልጽ አይደለም።
የሊባኖስ መንግሥት ከእስራኤል ጋር ጦርነት ከተጀመረበት
መጋቢት አንስቶ የሄዝቦላህን ወታደራዊ እንቅስቃሴ አግዷል። ይህ እገዳ ግን ቡድኑ እስራኤል ላይ ሮኬቶችን ከማስወንጨፍ አላገደውም።
በተጨማሪም እስራኤል ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ለማድረግ
ቁርጠኝነት ባላሳየችበት ሁኔታ ውስጥ የሚደረግ ድርድር ፍሬያማ የመሆኑ ጉዳይ አጠያያቂ ሆኗል።
እግረኛ ወታደሮቿን ሊባኖስ ውስጥ ያሰማራችው
እስራኤል፤ በአገሪቱ ደብባዊ ክፍል ውስጥ የሚገኙ ግዛቶችን መውረሯን ቀጥላለች።
ባለፉት ቀናትም ሊባኖስ ግዛት ውስጥ የሚገኙ መንደሮችን ሆነ ብላ አውድማለች። የእስራኤላውያን ደኅንነት እስካልተጠበቀ ድረስ የተፈናቀሉ ነዋሪዎች ወደ መኖሪያቸው እንዲመለሱ እንደማትፈቅድ
አስታውቃለች።