እስራኤል የሊባኖስን ጥንታዊ አምባ መቆጣጠሯን ተከትሎ የፀጥታው ምክር ቤት እንዲወያይ ተጠየቀ

እስራኤል የሊባኖስን ጥንታዊ አምባ መቆጣጠሯን ተከትሎ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ እንዲያካሂድ መጠየቃቸውን የፈረንሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጄን-ኖኤል ባሮው አስታወቁ። በደቡብ ሊባኖስ የሚገኘውን ታሪካዊ እና ስትራቴጂያዊ አምባ ሻቂፍ (ቢዩፎርት) እስራኤል በቁጥጥሯ ሥር ማዋሏን መከላከያ ሚኒስትሩ መግለጻቸው አይዘነጋም።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካ እና ኢራን ከስምምነት መድረሳቸውን እና ትራምፕ እስኪያጸድቁት እየተጠበቀ መሆኑን አክሲዮስ ዘገበ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁሙን በ60 ቀናት ለማራዘም እና በኒውክሌር ፕሮግራሟ ላይ ለመደራደር መስማማታቸው ተዘገበ።

    አክሲዮስ ሁለት የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ጠቅሶ እንደዘገበው ስምምነቱን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እስኪያጸድቁት ድረስ እየተጠበቀ ነው።

    ሁለቱ አገራት ከስምምነት ላይ መድረሳቸው የተዘገበው ኢራን በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ጦር ሠፈር ላይ ጥቃት መሰንዘሯ ከተዘገበ በኋላ ነው።

    አክሲዮስ ሁለቱ አገራት መስማማታቸውን ከዘገበ በኋላ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ላይ ቅናሽ ታይቷል።

    አሜሪካ ሌሊት ላይ በኢራን የወደብ ከተማ ባንዳር አባስ ውስጥ በሚገኝ የአውሮፕላን ማረፊያ አቅራቢያ ለአየር እና ለባሕር ኃይሏ ስጋት እንደሆኑ የገለጸቻቸውን ወታደራዊ ማዕከላት መምታቷን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ ኃይሎች "በሆርሙዝ ወሽመጥ ዙሪያ ስጋት ደቅነው የነበሩ" አራት የኢራን ድሮኖችንም መትተው እንደጣሉ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ገልጿል።

    እንደ ሴንትኮም ገለጻ ባንደር አባስ ውስጥ የሚገኘው ወታደራዊ ስፍራ ጥቃት የተፈጸመበት አምስተኛውን ድሮን ለመተኮስ ሲዘጋጅ ነው። የኢራን መገናኛ ብዙኃን ከከተማው በስተምሥራቅ አቅጣጫ የፍንዳታ ድምፆች መሰማታቸውን ዘግበዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የራዳር መከታተያውን አጥፍቶ ሊያልፍ የነበረ የአሜሪካ ነዳጅ ጫኝ መርከብን ማስቆሙን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዘገባው እንዳመለከተው የአብዮታዊ ዘቡ ባሕር ኃይል በመርከቡ ላይ ተኩስ ከፍቶ ወደ መጣበት እንዲመለስ ማስገደዱንም ገልጿል።

  2. የፓኪስታን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አርብ ወደ ዋሺንግተን አምርተው ከማርኮ ሩቢዮ ጋር ሊነጋገሩ ነው

    የፓኪስታን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አይሻቅ ዳር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የፓኪስታን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አይሻቅ ዳር

    የፓኪስታን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አይሻቅ ዳር አርብ ወደ ዋሺንግተን አምርተው ከአሜሪካው አቻቸው ጋር ተገናኝተው እንደሚወያዩ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታቸው አስታወቀ።

    ሚኒስትሩ ወደ ዋሺንግተን የሚያመሩት ኢዝላማባድ በኢራን እና በአሜሪካ መካከል በቋሚነት የሚካሄደውን ጦርነት ለማስቆም የሚያስችል ሰላም እንዲመጣ ጥረት እያደረገች ባለችበት ወቅት ነው።

    የፓኪስታን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለቻው ዳር ከሩቢዮ ጋር በሚኖራቸው ውይይት “በሁለትዮሽ ግንኙነት እና የጋራ ፍላጎት ባላቸው ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች ላይ ሃሳብ ይለወወጣሉ” ብሏል።

    አሜሪካ እና ኢራን የሚያደርጉት የሰላም ንግግር ፍሬ ማፍራት ባለመቻሉ ዋሺንግተን በዚህ ሳምንት በተደጋጋሚ የአየር ድብደባዎች በደቡባዊ ኢራን ፈጽማለች።

    አሜሪካ የፈጸመችው ጥቃት ተከትሎ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የአጸፋ እርምጃ በመውሰድ “የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈርን” መምታቱን ተናግሯል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረገው ጦርነት ሦስት ወር የሞለው ሲሆን በሆርሙዝ ወሽመጥ ለሚደረግ የመርከብ ጉዞ መቆም እንዲሁም የዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መናር ምክንያት ሆኗል።

    ይህንን ሦስት ወር የሞላው ጦርነት ለማቆም የሚደረጉ ረጅም ድርድሮች እስካሁን መፍትሔ አላስገኙም።

    አሜሪካ ራሷን ለመከላከል እንደሆነ በመግለጽ በሦስት ቀናት ውስጥ ሁለቴ ኢራን ውስጥ ባሉ ዒላማዎች ላይ ጥቃት ፈጽማለች። እንደ አዲስ ጥቃቶች መፈጸማቸው የተኩስ አቁም ስምምነቱን አደጋ ላይ ጥሎታል።

  3. የቀድሞው የየመን ፕሬዚዳንት አብድ ራቡህ ማንሱር ሃዲ ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ ሕይወታቸው አለፈ

    በፕሬዚዳንት አሊ አብዱላህ ሳላህ የሥልጣን ዘመን እአአ ከ1994 እስከ 2012 ድረስ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ያገለገሉት ሃዲ፣ የአረብ የጸደይ አብዮት ሳላህን ከሥልጣን ሲያወርዳቸው እርሳቸው ቦታውን ተረክበዋል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የቀድሞው የየመን ፕሬዚዳንት አብድ ራቡህ ማንሱር ሃዲ ሥልጣናቸውን የለቀቁት እአአ በ2022 ነበር

    የቀድሞው የየመን ፕሬዚዳንት አብድ ራቡህ ማንሱር ሃዲ በ80 ዓመታቸው በሳዑዲ አረቢያ ዋና ከተማ ሪያድ ሕይወታቸው ማለፉ ተገለጸ።

    ለፕሬዚዳንቱ ቅርብ የሆኑ ምንጮች ለኤኤፍፒ እንዳስታወቁት ሃዲ “በሳዑዲ ዋና ከተማ ባጋጠማቸው ድንገተኛ ሕመም ሕይወታቸው አልፏል” ብለዋል።

    ሃዲ በሳዑዲ በሚደገፈው መንግሥት እና በሁቲዎች መካከል ግጭት መቀስቀሱን ተከትሎ እአአ በ2015 ወደ ሪያድ በመሸሽ ኑሯቸውን በዚያ አድርገዋል።

    በፕሬዚዳንት አሊ አብዱላህ ሳላህ የሥልጣን ዘመን እአአ ከ1994 እስከ 2012 ድረስ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ያገለገሉት ሃዲ፣ የአረብ የጸደይ አብዮት ሳላህን ከሥልጣን ሲያወርዳቸው እርሳቸው ቦታውን ተረክበዋል።

    በየመን የሁቲ አማጺያን ተቃውሞ ተፋፍሞ ዋና ከተማዋን ሰነዓን በቁጥጥር ሥር ሲያውሉ ሃዲ ወደ ሳዑዲ አረቢያ ሸሽተዋል።

    እአአ በ2022 ሥልጣናቸውን ለፕሬዚዳንታዊ ምክር ቤት ሲያስረክቡ በየመን የተቀሰቀሰው ጦርነት በሺህዎች የሚቀጠሩትን በሞት ቀጥፎ አገሪቱን ለከፋ የሰብዓዊ ቀውስ አጋልጦ ነበር።

    ምንጮች ለኤኤፍፒ የሃዲ የቀብር ሥነ ስርዓት ነገ አርብ በሪያድ እንደሚፈጸም አስታውቀዋል።

  4. የአውሮፓ ኅብረት የሆርሙዝ ሁኔታ በሚቀጥሉት ሳምንታት የማይሻሻል ከሆነ የአውሮፕላን ነዳጅ ላይ ተጽዕኖ እንደሚኖረው አስታወቀ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የምትቀዝፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽን በሳምንታት ውስጥ የሆርሙዝ ወሽመጥ ጉዳይ የማይሻሻል ከሆነ በአውሮፓ የአውሮፕላን ነዳጅ እጥረት ሊፈጠር ወይንም የዋጋ ጭማሪ ሊታይ እንደሚችል ሐሙስ ዕለት አስታወቀ።

    የአውሮፓ ኮሚሽን የኢነርጂ ቢሮ ከነዳጅ እና ጋዝ አስተባባሪ ቡድኖች ጋር ስብሰባ ካደረገ በኋላ ሐሙስ ዕለት መግለጫ አውጥቷል።

    “የነዳጅ ማስተባበሪያ ቡድኑ የሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት በድፍድፍ ነዳጅ እና በዋና ዋና የፔትሮሊየም ምርቶች ላይ ተጽዕኖ ማሳረፉን አስታውቋል። እንዲሁም ሁሉም የአውሮፓ አገራት በዚህ ጉዳት ደርሶባቸዋል። እስካሁን በአውሮፓ ኅብረት የዋጋ ጭማሪ ቢታይም ተጠቃሚዎች ግን እጥረት አላጋጠማቸውም” ብሏል።

    “ይሁን እንጂ በሚቀጥሉት ሳምንታት ሁኔታው ለውጥ የማያሳይ ከሆነ በተለይ የአውሮፕላን ነዳጅ ላይ ገበያው ጭማሪ ሊያሳይ ወይንም እጥረት ሊፈጠር ይችላል" ሲል አስጠንቅቋል።

  5. አሜሪካ እና ኢራን ጥቃት ከፈጸሙ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    ነዳጅ የሚቀዳ የማደያ ሠራተኛ

    የፎቶው ባለመብት, Hindustan Times via Getty Images

    አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ጥቃት መፈጸማቸው ተኩስ አቁሙ ሊቋረጥ ይችላል የሚል ስጋት በመፍጠሩ፤ የነዳጅ ዋጋ በድጋሚ ጨመረ።

    በዛሬው ዕለት ሦስት ወር የሞላውን ጦርነት ሙሉ ለሙሉ ለመቋጨት የሚያስችል ስምምነት ላይ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይደረሳል የሚል ተስፋ መፈጠሩን ተከትሎ ረቡዕ ዕለት የነዳጅ ቅናሽ አሳይቶ ነበር። የዛሬው ጭማሪ ትናንት የታየውን ቅናሽ ወደ ቦታው የመለሰ ሆኗል።

    ለዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ በጠቋሚነት የሚወሰደው የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ የአንድ በርሜል ዋጋ ሐሙስ ንጋት ላይ ዋጋው በ3.75 በመቶ ጨምሮ 97.83 ዶላር ገብቷል። የአሜሪካው ዌስት ቴክሳስ ኢንተርሚዲየት (WTI) ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋም የ4 በመቶ ዕድገት በማሳየት በበርሜል ወደ 92.22 ዶላር አሻቅቧል።

    የነዳጅ ዋጋ እንዲጨምር ምክንያት የሆነው ጥቃት የተፈጸመው ቴህራን እና ዋሽንግተን ጦርነቱን ለመቋጨት ንግግራቸውን በቀጠሉበት ወቅት ነው። የካቲት ላይ በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት የተከፈተባት ኢራን በምላሹ የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷ የዓለም የኤነርጂ ገበያ እንዲቃወስ አድርጓል።

    ከዓለም ነዳጅ እና ወደ ፈሳሽነት የተቀየረ የተፈጥሮ ጋዝ ውስጥ 20 በመቶው ገደማው የሚተለላፈው በዚህ ወሽመጥ ነው።

    ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የዓለም የኤነርጂ ዋጋ መዋዠቁን ቀጥሏል። ከጦርነቱ በፊት በበርሜል 70 ዶላር ሲሸጥ የነበረው ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ፤ 120 ዶላር የደረሰበት ጊዜም ነበር።

  6. አሜሪካ፤ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስተዳደር በመሠረተችው አዲስ ተቋም ላይ ማዕቀብ ጣለች

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚጓዝ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኢራን በሆርሙዝ በኩል የሚደረጉ የባሕር ጉዞዎችን ለመቆጣጠር በቅርቡ ባቋቋመችው “የፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወሽመጥ ባለሥልጣን” (Persian Gulf Strait Authority) ላይ ማዕቀብ መጣሉን አስታወቀ።

    ግምጃ ቤቱ ባወጣው መግለጫ፤ የዚህ መስሪያ ቤት መቋቋም የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ከሚያልፉ መርከቦች ገቢ ለመሰብሰብ" የሚያደርገው ሙከራ አካል ነው ብሏል።

    በዚህም ምክንያት መስሪያ ቤቱ እና "ከተቋሙ ጋር የሚተባበሩ በሙሉ” የማዕቀብ ዝርዝር ውስጥ መግባታቸውን አስታውቋል።

    የተከፈተባትን ጦርነት ተከትሎ ሆርሙዝ ወሽመጥን የዘጋችው ኢራን፤ ይህንን ተቋም የመሠረተችው አሜሪካ ወደ ወደቦቿ የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ እግድ ከጣለች በኋላ ነው።

    ተቋሙ በወሽመጡ የሚደረግ የመርከቦች ጉዞን የመቆጣጠር እና የማቀናጀል ሥልጣን አለው።

    ባለ ሥልጣን መስሪያ ቤቱ ከዚህ ቀደም በቲውተር ገጹ ባወጣው ካርታ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገኝ "የክትትል ዞን" አሳይቷል። በዚህ ዞን ውስጥ የሚደረግ ጉዞ ከተቋሙ ጋር “መቀናጀት እንደሚያስፈልገውም” አስታውቋል።

    በዚህ የወሽመጡ ክፍል በኩል ማለፍ የሚፈልጉ መርከቦች ከፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወሽመጥ ባለሥልጣን ፈቃድ ማግኘት እንዳለባቸውም አሳስቧል።

    ባለፉት ቀናትም በዚህ የውሃ ክፍል የሚያልፉ መርከቦች በኢራን ኃይሎች ታጅበው እንዲጓዙ ወይም እንዲቆሙ እንደተደረጉ ዘገባዎች አመልክተዋል።

  7. እስራኤል የደቡባዊ ሊባኖስ ነዋሪዎች አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ አዘዘች

    የእስራኤል ድብደባ በሊባኖስ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል ረቡዕ ዕለት በደቡባዊ ጣይር ከተማ ድብደባዎችን ከፈፀመች በኋላ ወደ ሰማይ የሚጎን ጭስ ታይቷል

    የእስራኤል ጦር በደቡባዊ ሊባኖስ የሚገኝን ግዙፍ ክፍል “የግጭት ዞን” የሚል ምድብ ውስጥ እንዳስገባው በመግለጽ ነዋሪዎች አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ ሰጠ።

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት፤ ነዋሪዎች ከድንበር 40 ኪሎ ሜትር ገደማ በዛህራኒ ወንዝ ሰሜን አቀጣጫ እንዲጓዙ አሳስቧል።

    ጦሩ እጅግ ከባድ የሆነ የኃይል እርምጃ እንደሚወስድ ያስታወቀ ሲሆን፤ ሄዝቦላህ በተደጋጋሚ የተኩስ አቁሙን ጥሷል በሚል ከስሷል።

    የተኩስ አቁሙ ከታወጀ ከሚያዚያ መጀመሪያ ወዲህ 14 በመቶ የሚሆነውን የሊባኖስ ግዛት ከሚሸፍነው አካባቢ ነዋሪዎች ለቀው እንዲወጡ ሲጠየቅ ይህ የመጀመሪያው ነው።

    ረቡዕ ዕለት እስራኤል በደቡባዊ ጣይር ከተማ ድብደባዎችን ፈፅማለች። እስራኤልን የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣስ የሚከስሰው ሄዝቦላህ ተዋጊዎቹ ከእስራኤል ወታደሮች ጋር መጋጨታቸውን ተናግሯል።

    የረቡዕ ጥቃት የመጣው ሄዝቦላህ በሊባኖስ ግዛት በሚገኙ ወታደሮች እና በሰሜናዊ እስራኤል ንፁሃን ላይ የድሮን ጥቃት መፈፀሙን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የምድር ዘመቻቸውን እንደሚያስፋፉ ካስታወቁ በኋላ ነው።

    ባለፉት 24 ሰዓታት የእስራኤል ጦር ዘጠኝ የአካባቢውን ለቃችሁ ውጡ መመሪያዎችን አውጥቷል። ይህም በእስራኤል-ሊባኖስ ድንበር ግዙፍ ግጭት ይቀሰቀሳል የሚል ስጋት የደቀነ ሲሆን፤ በርካታ ሰዎችንም እንደሚያፈናቅል ተገምቷል።

  8. የኢራን አብዮታዊ ዘብ በአጸፋ እርምጃ ‘የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈርን’ መምታቱን አስታወቀ

    የአብዮታዊ ዘቡ ፈጣን ጀልባ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    አሜሪካ የፈጸመችው ጥቃት ተከትሎ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ወሰድኩት ባለው የአጸፋ እርምጃ “የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈርን” መምታቱን አስታወቀ።

    አሜሪካ ሌሊት ላይ በኢራን የወደብ ከተማ ባንዳር አባስ ውስጥ በሚገኝ የአውሮፕላን ማረፊያ አቅራቢያ ለአየር እና ለባሕር ኃይሏ ስጋት እንደሆኑ የገለጸቻቸውን ወታደራዊ ማዕከላት መምታቷን አስታውቃለች።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ጥቃቱ ምንም ጉዳት እንዳላደረሰ በመጥቀስ በምላሹ የአሜሪካ የወረራ ጥቃት መነሻ ነው ባለው የአየር ኃይል ሰፈር ላይ ጥቃት መፈጸሙን የኢራን ዜና ወኪል ታስኒም ይዞት በወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል።

    ይህ ጥቃት የተፈጸመበት ወታደራዊ ማዕከል የት እንደሚገኝ ግን በትክክል አልተገለጸም።

    የአብዮታዊ ዘቡ ጨምሮም “የጠብ ጫሪነት ጥቃቶች አጸፋ እንደሚሰጣቸው” በማመልከት ጥቃቶች የሚቀጥሉ ከሆነ “የበለጠ ከባድ” ምላሽ እንደሚኖር ገልጿል።

    ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ቅርብ የሆነው ታስኒም የዜና ወኪል ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው አሜሪካ ሌሊት ላይ የፈጸመችው ጥቃት ምንም ነገር በሌለበት ቦታ ላይ መሆኑን እና ፍንዳታውም የተሰማው ከዚያ ጋር የተያያዘ መሆኑን አመልክቷል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የራዳር መከታተያውን አጥፍቶ ሊያልፍ የነበረ የአሜሪካ ነዳጅ ጫኝ መርከብን ማስቆሙን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዘገባው እንዳመለከተው የአብዮታዊ ዘቡ ባሕር ኃይል በመርከቡ ላይ ተኩስ ከፍቶ ወደ መጣበት እንዲመለስ ማስገደዱንም ገልጿል።

  9. አሜሪካ በሦስት ቀናት ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ኢራን ላይ ጥቃት ፈጸመች

    የአሜሪካ ተዋጊ ጄት ባህር ላይ ከሚገኝ የጦር መርከብ ተነስቶ ሲበርር

    የፎቶው ባለመብት, US Navy via Getty Images

    የአሜሪካ ጦር በኢራን ስትራቴጂካዊ የወደብ ከተማ ባንደር አባስ የሚገኝ ወታደራዊ ስፍራን ዒላማ ያደረጉ የአየር ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ኃይሎች "በሆርሙዝ ወሽመጥ ዙሪያ ስጋት ደቅነው የነበሩ" አራት የኢራን ድሮኖችንም መትተው እንደጣሉ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ገልጿል።

    እንደ ሴንትኮም ገለጻ ባንደር አባስ ውስጥ የሚገኘው ወታደራዊ ስፍራ ጥቃት የተፈጸመበት አምስተኛውን ድሮን ለመተኮስ ሲዘጋጅ ነው። የኢራን መገናኛ ብዙኃን ከከተማው በስተምስራቅ አቅጣጫ የፍንዳታ ድምፆች መሰማታቸውን ዘግበዋል።

    ጥቃቱ የተፈጸመው በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተደረሰው ጠንካራ ያልሆነ ተኩስ አቁም ተግባራዊ መሆን ባላቆመበት ነው።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ለሚደረግ የመርከብ ጉዞ መቆም እንዲሁም የዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መናር ምክንያት የሆነውን ይህንን ሦስት ወር የሞላው ጦርነት ለማቆም የሚደረጉ ረጅም ድርድሮች እስካሁን መፍትሔ አላስገኙም።

    አሜሪካ ራሷን ለመከላከል እንደሆነ በመግለጽ ኢራን ውስጥ ባሉ ዒላማዎች ላይ ጥቃት ስትፈጽም ይህ በሦስት ቀናት ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። እንደአዲስ ጥቃቶች መድረሳቸው የተኩስ አቁም ስምምነቱን አደጋ ላይ ጥሎታል።

    ሴንትኮም የተወሰደውን ወታደራዊ እርምጃ “የተመጠነ፣ በግልጽ ራስን የመከላከል የሆነ እንዲሁም የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለማስቀጠል ያለመ" ሲል ገልጾታል።

    አሜሪካ ሰኞ ዕለት ደቡባዊ ኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የኢራንን የሚሳኤል ጣቢያዎች እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ፈንጂ ለማጥመድ የሞከሩ መርከቦች ዒላማ እንደተደረጉ ተገልጿል። ሴንትኮም እነዚህ ጥቃቶች የተወሰዱት "ወታደሮቻችንን ከኢራን ኃይሎች ከሚመጡ ስጋቶች ለመጠበቅ" ነው ብለዋል።

    ጥቃቶቹን “ትልቅ የተሰስ አቁም ጥሰት” ስትል ያወገዘችው ኢራን፤ “የትኛውም ጠበኛ ድርጊት ምላሽ ሳይሰጠው እንደማያልፍ” ዝታለች።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ማክሰኞ ዕለት የአሜሪካ ድሮንን መትቶ መጣሉን እንዲሁም ወደ ኢራን የአየር ክለል የገቡ ተዋጊ ጄት እና ድረኖን ላይ ተኩስ መክፈቱን ገልጿል። እነዚህ እርምጃዎች የተወሰዱት መቼ እንደነበር ግን አልተጠቀሰም።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው ትናንት በተካሄደ የካቢኔ ስብሰባ ላይ፤ ኢራን “በንዴት እየተደራደረች ነው” ሲሉ ተደምጠዋል። አክለውም በመጪው ህዳር የሚካሄደው የአጋማሽ ጊዜ የሥልጣን ዘመን ምርጫ የጦርነት ስትራቴጂያቸው ላይ ተጽዕኖ እንደማያሳድር ተናግረዋል።

  10. ትራምፕ ከኢራን ጋር የተደረገው ድርድር “እስካሁን አልተሳካም” አሉ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር እየተደረገ ያለው ድርድር “እስካሁን አልተሳካም” አሉ።

    ድርድሩ “ገና ደስተኛ አላደረገንም” ያሉት ትራም “ነገር ግን [ደስተኛ] እንሆናለን” ብለዋል።

    ትራምፕ በአስተዳደራቸው ሥር ካሉ ባለሥልጣናት ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ “መሆን ያለበት በዚህ መንገድ ነው፤ አለበለዚያ ግን እንጨርሰዋለን” ሲሉም ገልጸዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት ድርድሩን እያካሄዱ ያሉት “ደካማ ሆነው ነው” ብለዋል።

    “ምን እንደሚሆን እናያለን። ተመልሰን ሥራውን መጨረስ ይኖርብን ይሆናል። ወይም አይኖርብንም” ሲሉም አክለዋል።

    የኢራን መሪዎች “ስምምነት ላይ ለመድረስ ይፈልጋሉ” ሲሉም ትራምፕ ተደምጠዋል።

    የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው ስምምነት ላይ መድረስ እንደሚፈልጉ ገልጸው “ካልተሳካ ግን ፕሬዝዳንቱ አማራጭ አላቸወ” ብለዋል።

    በሌላ በኩል ኢራን ከአሜሪካ ጋር በምታደርገው ድርድር፤ የመጀመሪያ ደረጃ ላይ የሚገኝ፣ ይፋዊ ያልሆነ፣ የመግባቢያ ሰነድ ማዕቀፍ ረቂቅ እንደደረሳት የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ቢዘግቡም ዋይት ሀውስ ግን ይሄንን "ፍጹም ፈጠራ" ሲል አስተባብሏል።

  11. ኢራን "የመግባቢያ ሰነድ ረቂቅ” ደርሶኛል ብትልም አሜሪካ አስተባበለች

    ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር በምታደርገው ድርድር፤ የመጀመሪያ ደረጃ ላይ የሚገኝ፣ ይፋዊ ያልሆነ፣ የመግባቢያ ሰነድ ማዕቀፍ ረቂቅ እንደደረሳት የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ቢዘግቡም ዋይት ሀውስ ግን ይሄንን "ፍጹም ፈጠራ" ሲል አስተባብሏል።

    የዋይት ሀውስ ቃል አቀባይ ኦሊቪያ ዌልስ “ፕሬዝዳንት ትራምፕ እንደተናገሩት ድርድሩ እየተሻሻለ ነው። [ፕሬዝዳንቱ] ቀይ መስመሮቻቸውን በግልጽ አስምረዋል” ብለዋል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ከሆነ ቴህራን በአንድ ወር ውስጥ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ያለውን የጉዞ መጠን ከጦርነቱ አስቀድሞ ወደነበረው ትመልሳለች። በምላሹ አሜሪካ ወታደሮቿን ከኢራን ዙርያ ታስወጣለች፤ በባሕር ኃይሉ ላይ የጣለችውን ማዕቀብም ታነሳለች።

    የመርከቦችን ጉዞ ማስተዳደሪያ መንገድ የሚወሰነው በኢራን እና ኦማን እንደሆነ ተገልጿል።

    ነገር ግን “ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለአሜሪካ ሕዝብ የሚጠቅም እና ኢራን መቼም ቢሆን ኒውክሌር መሣሪያ እንዳይኖራት የሚያግድ ስምምነት ብቻ ነው የሚቀበሉት” ብለዋል።

    የኢራን የብሔራዊ ደኅንነት ጠቅላይ ምክር ቤት የውጭ ጉዳይ እና የዓለም አቀፍ ደኅንነት ምክትል ዳይሬክተር አሊ ባግሪ፤ ቴህራን ከዋሽንግተን ጋር እያደረገችው ባለው ድርድር የዩራኒየም ጉዳይ በአጀንዳነት እንዳልቀረበ ተናግረዋል።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦችን በማስተዳደር ረገድ ኢራን እና ኦማን ሚና እንዲኖራቸው እየተደራደሩ መሆኑን አረጋግጠዋል።

    “በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የማለፍ ሁኔታ እና አካሄድ የኢራን ጦርነት ከመጀመሩ በፊት ከነበረው ፈጽሞ የተለየ ይሆናል” ብለዋል።

    “ሁሉም ነጥቦች ላይ ካልተስማማን በስተቀር ስምምነት ላይ ደርሰናል ብለን አናምንም” ሲሉም አክለዋል።

  12. ኢራን በዩራኒየም ይዞታዋ ላይ እንደማትደራደር አስታወቀች

    አሊ ባግሪ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, አሊ ባግሪ

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር እያደረገችው ባለው ድርድር የዩራኒየም ጉዳይ በአጀንዳነት እንዳልቀረበ በኢራን የብሔራዊ ደኅንነት ጠቅላይ ምክር ቤት የውጭ ጉዳይ እና የዓለም አቀፍ ደኅንነት ምክትል ዳይሬክተር አሊ ባግሪ ተናገሩ።

    ባለሥልጣኑ ይህንን ያሉት በሩሲያ ዋና ከተማ ሞስኮ ውስጥ እየተካሄደ ባለው 14ኛው ከፍተኛ የደኅንነት ባለሥልጣናት ስብሰባ ወቅት በተጓዳኝ ለተነሳላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ ነው።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግን ቀደም ሲል የዳበረው የኢራን ዩራኒየም ክምችት፤ በሚደረስ ስምምነት ወደ አሜሪካ ተወስዶ ወይም በሌላ ስፋራ ላይ እንዲወድም እንደሚደረግ ተናግረው ነበር።

    የተኩስ አቁም ከተደረገ በኋላ ለወራት ያለመቋጫ እየተካሄደ ያለው የኢራን እና የአሜሪካ ድርድር ወደ ስምምነት መቃረቡን የአሜሪካ ባለሥልጣናት ባለፉት ቀናት ሲናገሩ ቆይተዋል።

    የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ዋነኛ መነጋገሪያ ቢሆንም አሳልፋ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆኗን እና የድርድሩ ቀይ መስመር መሆኑን በተደጋጋሚ ስትገልጽ ነበር።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ግን ኢራን በኒውክሌር ፕሮግራሟ ላይ የቀረበላትን ሃሳብ የማትቀበል ከሆነ ሌላ ዙር ከባድ ጥቃት እንደሚጠብቃት እያስጠነቀቁ ነው።

  13. የኮንጎ ግጭት ኢቦላን ለመቆጣጠር የሚደረገውን ጥረት እንዳሰናከለ ዶ/ር ቴድሮስ ገለጹ

    የኢቦላ ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ያለው ግጭት የኢቦላን ሥርጭት ለመቆጣጠር የሚደረገው ጥረት ላይ ጫና ማሳደሩን የዓለም ጤና ድርጅት ኃላፊ ዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም ገለጹ።

    በአገሪቱ “ግጭት እና አደገኛ በሽታ” መደራረባቸውን የተናገሩት ዶ/ር ቴድሮስ፤ በኢቱሪ ግዛት በሽታውን የመከላከል እንቅስቃሴ ማድረግ መስተጓጎሉን አክለዋል።

    ኃላፊው በኤክስ ገጻቸው ባወጡት መግለጫ የዓለም ጤና ድርጅት “ቦምብ እየዘነበ የማኅበረሰቡን እምነት ማግኘት ወይም ታማሚዎችን መለየት አይችልም”

    ዶ/ር ቴድሮስ ቫይረሱን በቁጥጥር ሥር የማዋል ጥረቱን ለመምራት ዛሬ ኮንጎ እንደሚገቡ ተገልጿል። በኢቦላ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 220 ደርሷል።

    የአገሪቱ መንገዶች አመቺ ባለመሆናቸው የእርዳታ ሠራተኞች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው ለመሥራት ተቸግረዋል። ግጭት እና መፈናቀልም የጤና ሥርዓቱን አናግተዋል። በተጨማሪም ዓለም አቀፍ እርዳታ ተቋርጧል።

    ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች በቫይረሱ የተያዙባት ኢቱሪ ግዛት ከአውሮፓውያኑ 2021 አንስቶ በወታደራዊ አስተዳደር ሥር ናት።

  14. ኢራን እና አሜሪካ ልዩነቶቻቸውን ያጠብባሉ ብላ ተስፋ እንደምታደርግ ቻይና ገለጸች

    የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ የኢራን ጦርነት ተፋላሚ ወገኖች የተኩስ አቁሙን ለማስቀጠል ቁርጠኛ ሆነው እንደሚቀጥሉ እና ልዩነቶቻቸውን ያጠብባሉ ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ገለጹ።

    አሜሪካ በደቡብ ኢራን የመከላከል ያለችውን ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ቴህራን ማክሰኞ ዕለት ዋሺንግተንን የተኩስ አቁሙን በመጣስ ከስሳለች።

    ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግጭት ለማስቆም የሚደረገው ድርድር “የተወሰነ ቀናት ሊወስድ ይችላል” ብለዋል።

    ዋንግ በኒውዮርክ የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ በተገኙበት ወቅት "ሰላም በተቻለ ፍጥነት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ እንዲመለስ ተፋላሚ አካላት የተኩስ አቁምን ለማስቀጠል በቁርጠኝነት እንደሚቆዩ እና ልዩነቶቻቸውን ለማጥበብ ግማሽ መንገድ እንደሚገናኙ ተስፋ እናደርጋለን” ብለዋል።

    ዋንግ አክለውም ሁሌም እንደምንለው ሰላም እና መፍትሄ ለማምጣት ጊዜ ይፈልጋል ያሉት ሚኒስትሩ “ለረዥም ጊዜ የቆዩ ችግሮች ቶሎ አይፈቱም” ብለዋል።

    “ይሁን እንጂ በድርድሩ የሚደረግ እያንዳንዱ እርምጃ የበለጠ ተስፋን ይሰጣል፤ እንዲሁም ግጭቱ ቶሎ በተቋጨ ጊዜ የሰላማዊ ዜጎችን ጉዳት መቀነስ ይቻላል” ብለዋል።

  15. የዩኬ የደህንነት ተቋም ሩሲያ ወሳኝ የመሠረተ ልማቶችን እና ዲሞክራሲን “ያለመታከት ዒላማ እያደረገች” ነው ሲል ወነጀለ

    የሩሲያ ባንዲራ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዩናይትድ ኪንግደም የስለላ፣ ደህንነት እና ሳይበር ኤጀንሲ ሩሲያ ያለ መታከት ወሳኝ መሠረተ ልማቶችን እና አገልግሎቶችን ማጥቃት በመቀጠሏ አገሪቱ አሳሳቢ እና ወሳኝ ጊዜ ላይ እንደምትገኝ ገለጸ።

    የዩኬ የስለላ ተቋም ኃላፊ የሆኑት አኔ ኪአስት በትለር ረቡዕ ዕለት የሩሲያ እርምጃ ለዩናይትድ ኪንግደም የሚኖረውን ስጋት በሚመለከት እንዲሁም እንዴት መመከት እንዳለባት የሚገልጽ ንግግር ያደርጋሉ ተብሏል።

    ከኃላፊዋ ንግግር ተቀንጭቦ የተጋራው መልዕከት ላይ ሩሲያ “ወሳኝ የሆነ መሠረተ ልማቶችን፣ የዲሞክራሲ ሂደቶችን፣ የአቅርቦት ሰንሰለቶችን እና የሕዝብ እምነትን ዒላማ አድርጋለች” ብለዋል።

    ሩሲያ በብሪታኒያ ግዛት ውስጥ የአገር ክህደት ወንጀልን በማበረታታት የምትወቀስ ሲሆን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዩኬ እና የኔቶ አባል አገራት ላይ በይፋ ያልታወጀ ‘የተቀናጀ ጦርነት’ ከፍታለች በሚል ትከሰሳለች።

    ክሬምሊን ውንጀላውን ያስተባብላል።

    በትለር ተቋማቸው “ግድየለሽነት የተሞላበት” ያሉትን የሳይበር ጥቃቶች ለመመከት እንዲሁም “የግድያ ሙከራዎችን” ለመከላከል ያለ እረፍት እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።

    አክለውም “በእንዲህ ዓይነት ጠብ አጫሪት እና ግርግር ውስጥ ተቋማችን ያለመታከት ከደህንነት እና መከላከያ አጋሮቻችን ጋር በመሆን የሩሲያን ስጋት ለመቀነስ ይሰራል” ብለዋል።

    ክሬምሊን የኬጂቢ ባልደረባ የነበረውን አሌክሳንደር ሊትቪኔንኮን በለንደን ሆቴል ውስጥ ሳለ በጠጣው ሻይ ውስጥ መርዛማ ኬሚካል በመጨመር ለመግደል ሙከራ አድርጓል መባሉን አስተባብሏል።

    እአአ በ2018 የቀድሞው የሩሲያ ወታደራዊ ደህንነት ባልደረባ የነበረውን ሰርጌይ ስክሪፓልን ለመግድል ሙከራ በማድረግ ተከስሷል።

    ሩሲያ እአአ በ2022 ዩክሬንን መውረሯን ተከትሎ ዩናይትድ ኪንግደም ከኪየቭ ጎን በመቆሟ በምዕራባውያን አገራት ላይ “የተቀናጀ ጦርነት” በመክፈት ትወነጀላለች።

  16. በቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የሚመራ የአፍሪካ ኅብረት የምርጫ ታዛቢዎች ቡድን አዲስ አበባ ገባ

    የቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ
    የምስሉ መግለጫ, የቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ

    በመጪው ሰኞ ሰባተኛውን አጠቃላይ ምርጫን የሚታዘቡ የአፍሪካ ኅብረት የምርጫ ታዛቢዎች አዲስ አበባ መግባታቸውን ኅብረቱ አስታወቀ።

    በቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የሚመራው የኅብረቱ ታዛቢዎች ከ37 አገራት የተውጣጡ እና 73 አባላትን የያዘ መሆኑን በመግለጫው ላይ ተገልጿል።

    ይህ አምባሳደሮችን፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት ተወካዮች፣ የምርጫ ባለሙያዎች፣ የሰብኣዊ መብት፣ የሥርኣተ ፆታ፣ የወጣቶች እና የመገናኛ ብዙኃን ተወካዮችን ያከላተተ መሆኑ ተገልጿል።

    የአፍሪካ ኅብረት ማክሰኞ ግንቦት 18/2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ የምርጫ ታዛቢዎች በምርጫው ዕለት የድምጽ አሰጣጥ ሂደትን እና ቆጠራን ለመታዘብ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚሰማሩ መሆኑ አስታውቋል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በመላ አገሪቱ ሰኞ ግንቦት 24 የሚደረገው ሰባተኛው ጠቅላላ አገራዊ ምርጫ ለመታዘብ ከአፍሪካ ኅብረት ታዛቢዎች በተጨማሪ የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) ታዛቢዎች እንደሚገኙ አስታውቋል።

    የአፍሪካ ብረት እና የኢጋድ የምርጫ ታዛቢዎች ወደ ኢትዮጵያ የመጡት በኢትዮጵያ መንግሥት ግብዣ መሠረት መሆኑን የምርጫ ቦርድ እና ኅብረቱ አስታውቀዋል።

    የምርጫ ታዛቢ ቡድኑ ግምገማውን በኢትዮጵያ የምርጫ ሕግ፣ በአፍሪካ ኅብረት እንዲሁም አስፈላጊ በሆኑ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ለማድረግ በተቀመጡ መስፈተርቶች ላይ በመመሥረት ግምገማውን እንደሚያደርግ ተገልጿል።

    ታዛቢዎቹ ከምርጫ ቦርድ፣ ከፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ከዕጩዎች፣ ከመገናኛ ብዙኃን እንዲሁም ከሌሎች የምርጫ ታዛቢዎች ጋር በትብብር እንደሚሠሩ ተጠቅሷል።

    ታዛቢ ቡድኑ የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርቱን ግንቦት 26/2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ይፋ የሚያደርግ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ የመጨረሻ ሪፖርቱን ደግሞ ከምረጫው በኋላ በሁለት ወር ውስጥ ያቀርባል ተብሏል።

    የኢትዮጵያ ሲቪክ ማኅበራት ሰባተኛውን ጠቅላላ ምርጫ ለመታዘብ ከ500 በላይ የሚሆኑ የረጅም ጊዜ ታዛቢዎችን ማሰማራታቸውን አስታውቀዋል።

  17. እስራኤል በጋዛ ከተማ በፈጸመችው ጥቃት አዲሱን የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ አዛዥ መግደሏን አስታወቀች

    ጥቃቱ በተፈጸመበት አካባቢ በርካታ ሰዎች ተሰብሰብው ታይተዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል ማክሰኞ ዕለት በጋዛ ከተማ በፈጸመችው ጥቃት በዲሱን የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ አዛዥ መግደሏን አስታወቀች።

    የእስራኤል ጦር በጋዛ ከተማ በተጨናነቀ የገበያ ስፍራ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ በፈጸመው ከፍተኛ የአየር ድብደባ ቢያንስ ሦስት ፍልስጤማውያን መሞታቸውን የሕክምና ባለሙያዎችና የዓይን እማኞች ተናግረዋል።

    ጥቃቱ የኢድ አል-አድሃ በዓል ከመከበሩ በፊት ጎዳናዎች በገበያተኞች ተጨናንቀው ባለበት ወቅት በጋዛ ከተማ መሃል በሚገኘው የአል-ካያሊ ሕንፃ የላይኛውን ሦስት ፎቅ ዒላማ ማድረጉ ተገልጿል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ቢሮ ቀደም ሲል የእስራኤል ጦር የሐማስን የጦር ክንፍ አዛዥ መሐመድ ኦዴህን ዒላማ እንዳደረገ አስታውቋል። ይህም የቀድሞው የጦር አዛዥ በተመሳሳይ ጥቃት ከተገደለ ከጥቂት ቀናት በኋላ የተፈጸመ ነው።

    ይህ እስራኤል ከሐማስ ጋር የተኩስ አቁም ስምምነት ካደረገች በኋላ በጋዛ የተፈጸመ የቅርብ ጊዜ ከባድ ጥቃት ነው።

    ኦዴህ በጥቃቱ መገደሉን በተመለከተ የእስራኤል መንግሥት ሲያስታውቅ ሐማስ ግን ምንም አስተያየት አልሰጠም።

    የነፍስ አድን ሠራተኞች በስፍራው ሲደርሱ በአካባቢው በደረሰው ከባድ ጉዳት እና በነበረው መጨናነቅ ምክንያት ወደ ላይኛው ፎቅ ለመውጣት ተቸግረዋል።

    የዓይን እማኞች ቢያንስ አምስት ሚሳኤሎች ሕንፃውን ከተለያየ አቅጣጫ በተመሳሳይ ጊዜ መምታታቸውን ተናግረዋል።

    አንድ ነዋሪ ጥቃቱ ከመፈጸሙ በፊት የሄሊኮፕተር ድምፅ መስማቱን ተናግሯል።

    ከቦታው የተገኘ ተንቀሳቃሽ ምስል እንደሚያሳየው አምቡላንሶች እና የሲቪል መከላከያ ሠራተኞች በተመታው ሕንፃ ውስጥ የተረፉ ሰዎች ካሉ ሲፈልጉ የሚያሳይ ሲሆን በአቅራቢያው በርካታ ሰዎች ተሰብስበው ነበር።

    የኔታንያሁቢሮ የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት መስከረም 26 2016 ዓ.ም. ሐማስ የፈጸመውን ጥቃት “ካቀነባበሩ ሰዎች መካከል አንዱን” መሐመድ ኦዴህን ዒላማ እንዳደረገውአስታውቋል።

    “ኦዴህ በበርካታ የእስራኤልዜጎችን እና የመከላከያ ሠራዊት አባላት ግድያ፣ ጠለፋ እና መቁሰል ተጠያቂ ነው” ሲል መግለጫውአክሏል።

    የቡድኑ ታጣቂ ክንፍ አዛዥ የነበሩት ኢዝ አድ-ዲን አል-ሃዳድ በግንቦት ወር መጀመሪያ ላይ በእስራኤል የአየር ጥቃት ተገድለዋል።

    ይህ ጥቃት በአንድ የመኖሪያ ሕንፃ ላይ ያነጣጠረ ሲሆን ቢያንስ ሦስት ሰዎችን ገድሏል ሲሉ የዓይን እማኞች እና የአካባቢው ምንጭ ተናግረዋል።

    እስራኤል የተኩስ አቁም ከተደረሰበት እአአ ከጥቅምት 10 ጀምሮ በጋዛ ዙሪያ ጥቃቶችን ስትፈጽም ቆይታለች።

    ሐማስ እስራኤል የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣስ እና ሲቪሎችን በማጥቃት በተደጋጋሚ ሲከስ ቆይቷል።

    የጋዛ የጤና ሚኒስቴር በተኩስ አቁም ስምምነቱ ወቅት በእስራኤል በተሰነዘረው ጥቃት ከ800 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ይፋ አድርጓል።

  18. እስራኤል በሊባኖስ በተከታታይ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች ቢያንስ 31 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በምሥራቅ ሊባኖስ በሚገኘው ቤካ ሸለቆ እና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ላይ ጥቃት በመክፈት ሄዝቦላህን እየመታ መሆኑን ይናገራል።

    እስራኤል በተከታታታይ በምሥራቃዊ እና ደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት በርካታ ሕጻናትን ጨምሮ ቢያንስ 31 ሰዎች መገደላቸውን የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የእስራኤል ጦር በሊባኖስ የሚፈጽመውን ከባድ ጥቃት የቀጠለው ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በሄዝቦላህ ላይ የሚወሰደው ወታደራዊ እርምጃ እንዲጠናከር ትዕዛዝ ከሰጡ በኋላ ነው።

    የእስራኤል መከላከያ ከ100 በላይ የሄዝቦላህ መሠረተ ልማቶችን እና ተዋጊዎችን ዒላማ አደርጎ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።

    ኔታንያሁ ሰኞ ምሽት በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ እስራኤል “ከሄዝቦላህ ጋር ጦርነት ላይ” እንደሆነች ተናግረው ሠራዊቱ “አድቃቂ ምት” እንዲፈጽም ማዘዛቸውንም ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እስራኤል በከፈተችው ወታደራዊ ዘመቻ "ከ600 በላይ አሸባሪዎች” መገደላቸውንም ተናግረዋል። "አሁን ከእኛ የሚጠበቀው ጥቃቱን ማጠናከር እና ጥንካሬውን ይበልጥ መጨመር ነው" ሲሉም ተደምጠዋል።

    ኔታንያሁ ማክሰኞ ዕለት በደህንነት ካቤኔ ስብሰባቸው ላይ “በሊባኖስ የምናካሄደውን ዘመቻ እያሰፋ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    “የእስራኤል ጦር በምድር ከፍተኛ ኃይል አሰማርቶ ዘመቻ እያካሄደ እና ገዢ መሬቶችን እየተቆጣጠረ ነው” ብለዋል።

    አክለውም በሰሜን እስራኤል የሚገኙ እስራኤላውያንን ከሄዝቦላህ ጥቃት ለመከላከል “የደህንነት ቀጣናዎች እየመሰረተ ነው” ብለዋል።

    በእስራኤል እና ሊባኖስ መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም በተደጋጋሚ ተጥሷል።

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በየዕለቱ የአየር ድብደባ የምትፈጽም ሲሆን ሄዝቦላህም ሮኬቶችን እና ድሮኖችን ይተኩሳል።

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በምሥራቅ ሊባኖስ በሚገኘው ቤካ ሸለቆ እና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ላይ ጥቃት በመክፈት ሄዝቦላህን እየመታ መሆኑን ይናገራል።

    የተወሰኑ ጥቃቶች በተባበሩት መንግሥታት በቅርስነት የተመዘገበ እና የ900 ዓመት እድሜ እንዳለው የሚገመት ቤተ መንግሥት ላይ ጥቃት ማድረሳቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

  19. በኢራን ለሦስት ወራት ተቋርጦ የነበረው የኢንተርኔት አገልግሎት ተጀመረ

    በኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የኢንተርኔት አገልግሎት ተቋርጧል

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የኢንተርኔት አገልግሎት ተቋርጧል

    በኢራን ለሦስት ወራት ያህል ተቋርጦ የቆየው የኢንተርኔት አገልግሎት ዳግም መጀመሩን የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት አስታወቁ።

    ሞሃማድ ሬዛ አረፍ ማክሰኞ ዕለት በኤክስ ገጻቸው ላይ “ነጻ እና ቁጥጥር የሚደረግበት የኢንተርኔት አገልገሎት ለመስጠት የመጀመርያ እርምጃ ወስደናል” ብለዋል።

    ኔትብሎክስ እና ኬንቲክ የተባሉ የዓለም አቀፍ የኢንተርኔት ግንኙነትን የሚከታተሉ ተቋማት በኢራን ዛሬ ከምሳ ሰዓት ጀምሮ “በከፊል” የኢንተርኔት አገልግሎት መጀመሩን ተናግረዋል።

    በኢራን የኢንተርኔት አገልግሎት የተቋረጠው አሜሪካ እና እስራኤል የካቲት 21 2018 ዓ.ም. በአገሪቱ ላይ ጦርነት መክፈታቸውን ተከትሎ ነበር።

    የኢራን ባለሥልጣናት በጦርነቱ ወቅት ኢንተርኔት የተዘጋው ከደኅንነት ጋር በተያያዙ ምክንያት እንደሆነ ይናገራሉ። ይህንን በማድረግ ክትትል፣ ስለላ እና የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል እንዳሰቡ ጠቁመዋል።

    በቴህራን የሚገኝ አንድ ግለሰብ ዛሬ የዋይፋይ አገልግሎት መጀመሩን ለቢቢሲ ተናግሯል።

    ኔትብሎክስ የኢንተርኔት አገልግሎት “የሚቀጥል” ስለመሆኑ “ግልጽ አይደለም” ብሏል።

  20. እስራኤል በሊባኖስ መንደሮች ላይ በፈጸመችው ጥቃት አስራ አንድ ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    እስራኤል ሰኞ ዕለት በደቡባዊ ሊባኖስ ናቤታህ መንደር የፈጸመችው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ የምትወስደውን ወታደራዊ እርምጃ እንደምታጠናክር ከገለጸች በኋላ በደቡብ እና ምሥራቃዊ ሊባኖስ በርካታ ድብደባዎችን መፈጸሟ ተገለጸ።

    የእስራኤል ጦር ከ100 በላይ የሄዝቦላህ መሠረተ ልማቶችን እና ተዋጊዎች ላይ የአየር ድብደባ መፈጸሙን ተናግሯል።

    በሚያዚያ ወር አጋማሽ ላይ በእስራኤል እና ሊባኖስ መካከል በአሜሪካ አደራዳሪነት የተኩስ አቁም ተደርሷል።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር በቤካ ቫሊ በሚገኝ ማሽጋሃራ በተሰኘ መንደር በተፈጸመ ጥቃት ሁለት ሕጻናትን ጨምሮ 11 ሰዎች መገደላቸውን አስታውቋል።

    የእስራኤል ጦር ግን “የአሸባሪዎች እንቅስቃሴ” በታየበት አካባቢ ጥቃት መፈጸሙን ተናግሯል።

    የእስራኤል ጦር ጥቃቱን አጠናክሮ የቀጠለው ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በሄዝቦላህ ዒላማዎች ላይ “ጠንከር ያለ ጥቃት” እንዲፈጸም ትዕዛዝ ከሰጡ በኋላ ነው።

    በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም በተደጋጋሚ ተጥሷል።

    እስራኤል በተለይ በደቡባዊ ሊባኖስ በተደጋጋሚ የአየር ድብደባ የምትፈጽም ሲሆን ሄዝቦላህም ሮኬቶችን እና ድሮኖችን በሰሜን እስራኤል ወደሚገኙ አካባቢዎች ይተኩሳል።