የኢራን እና አሜሪካ ንግግር አደራዳሪዎች በተገኙበት በስዊትዘርላንድ ተጀመረ

የኢራን እና አሜሪካ ድርድር የኳታር አደራዳሪዎች በተገኙበት በስዊትዘርላንድ ተጀመረ። ድርድሩ በሊባኖስ የተኩስ አቁም ላይ እና በኢራን እንዳይንቀሳቀሱ በተደረጉ ሃብቶች ላይ እንደሚያተኩር ተገልጿል። ኳታር በኢራን እና አሜሪካ መካከል ድርድር መጀመሩን አረጋግጣለች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ‘ኢራን [ስምምነቱ] ቶሎ እንዲጠናቀቅ ትፈልጋለች”-ዶናልድ ትራምፕ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የዩኤኢው ሼክ ሞሐመድ ቢን ዛይድ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የዩኤኢው ሼክ ሞሐመድ ቢን ዛይድ

    በቡድን ሰባት ስብሰባ ላይ ለመካፈል ፈረንሳይ የሚገኙት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚያካሄዱት ሁለተኛው ዙር ድርድር “ጊዜውን ጠብቆ ይሄዳል” ብለው እንደሚያምኑ ተናገሩ።

    “ኢራን በቶሎ እንዲጠናቀቅ ትፈልጋለች፤ ወደ መደበኛ ሕይወታቸው መመለስ ይፈልጋሉ” ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ስምምነቱ ይፋ ለምን እንደማይሆን ሲጠየቁ “መጀመሪያ በይፋዊ መፈራረሙ እንዲቀድም” እንደሚፈልጉ ተናግረዋል።

    “ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ አይኖራትም፤ ያንን ነው የሚለው. . . ያ ነው 99.9 በመቶ የምፈልገው የነበረው”

    የሆርሙዝ ወሽመጥ ከ60 ቀናት በኋላም “ያለምንም ክፍያ” ክፍት ይሆናል ሲሉም አብራርተዋል።

    ትራምፕ ስምምነቱን “ቃል በቃል” ለማንበብ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚጠሩም ጨምረው አስረድተዋል።

    “ምክንያቱም በጣም ወሳኝ ሰነድ ነው” ሲሉ አክለዋል።

    ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ አይኖራትም ካሉ በኋላ “እውነቱን ለመናገር ሌላው አስፈላጊ አይደለም” ሲሉ ተደምጠዋል።

    ስምምነቱን “ከኒውክሌር ጦር መሣሪያ በተቃራኒ የቆመ ግድግዳ” ሲሉ ገልጸውታል።

    የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ከኢራን ጋር ካደረጉት ስምምነት ጋር በማነጻጸርም “መካከለኛው ምሥራቅን ሊያጠፋ ይችል ነበር” ብለዋል።

    የተብላላውን ዩራኒየም ከኢራን ያወጡ እንደሆን ሲጠየቁም፣ መቼ ይወጣል የሚለው ላይ ምንም ጥድፊያ እንደሌለ ተናግረዋል።

    ትራምፕ ስምምነቱ እንዲጸድቅ ወደ ኮንግረስ እንደሚላክ ጨምረው አስረድተዋል።

  2. ሄዝቦላህ፣ ኢራን ከአሜሪካ ጋር በሚኖራት ድርድር እስራኤል ከሊባኖስ እንድትወጣ ለመጠየቅ ቃል መግባቷን ገለጸ

    በሊባኖስ በእስራኤል ጥቃት የወደመ ቤታቸውን የሚመለከቱ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሊባኖስ በእስራኤል ጥቃት የወደመ ቤታቸውን የሚመለከቱ ሰዎች

    ሄዝቦላህ ኢራን ከአሜሪካ ጋር በሚኖራት ቀጣይ ድርድር የእስራኤል ወታደሮች ሊባኖስን ለቅቀው እንዲወጡ እንደምትጠይቅ ማረጋገጫ ማግኘቱን አስታወቀ።

    የሄዝቦላህ የሕዝብ ግንኙነት ቢሮ ለሮይተርስ የዜና ወኪል ማክሰኞ ዕለት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰው ስምምነት አርብ ዕለት ከተፈረመ በኋላ በሚደረገው ንግግር የእስራኤል ጦር ከሊባኖስ ለቅቆ መውጣት ይኖርበታል ብሏል።

    ቡድኑ ለሮይተርስ “እስራኤል [ከሊባኖስ] ለቅቃ እስካልወጣች በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የኒውክሌር ስምምነት አይኖርም” ሲል ተናግሯል።

    የሄዝቦላህ ዋና ፀሐፊ ናኢም ቃሴም ለኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋሊባፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

    ቡድኑ ከሄዝቦላህ ጋር ግንኙነት ባለው አል ማናር ቴሌቪዢን ጣቢያ ቴሌግራም ገጽ ላይ ባስተላለፈው መልዕክት ቃል አቀባዩ ለሊባኖስ ስላሳዩት “ጠንካራ አቋም እና አጋርነት” አመስግነዋል።

    አክለውም እስራኤል ወታደራዊ ዘመቻዋን እንድታቆም በኢራን እና አሜሪካ ስምምነት ውስጥ “መሠረታዊ አንቀጽ” ሆኖ እንዲገባ በማድረጋቸው አመስግነዋቸዋል።

  3. በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰውን ስምምነት በተመለከተ ማን ምን አለ?

    መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሆርሙዝ አርብ ዕለት ሙሉ ለሙሉ እንደሚከፈት ይጠበቃል

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር የተደረሰው የሰላም ስምምነት በጥሩ ሁኔታ ላይ በመሄድ “ወደ ሁለተኛ ደረጃ ደርሷል” ቢሉም ዝርዝር ከመስጠት ተቆጥበዋል።

    ከሦስት ወራት በላይ የቆየውን ጦርነት ለማስቆም ከስምምነት የተደረሰው እሁድ ዕለት ቢሆንም አስካሁን ሙሉው የስምምነት ዝርዝር ይፋ አልሆነም።

    ሰኞ ዕለት ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ስምምነቱ ተፈርሟል” በማለት ዝርዝሩ “በጣም በቅርቡ” ሙሉ ለሙሉ ይፋ ይሆናል ብለው ተናግረው ነበር።

    ፕሬዝዳንቱ ጨምረውም ስምምነቱ ሁለቱ ወገኖች በይፋ ስዊትዘርላንድ ውስጥ ከፈረሙት በኋላ ይፋ ሊደረግ እንደሚችል ጨምረው ገልጸዋል።

    የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣናት እንዳሉት በተደረሰው ስምምነት መሠረት የሆርሙዝ ወሽመጥ አርብ ዕለት ሙሉ ለሙሉ ክፍት ይደረጋል።

    የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ በበኩላቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕ የስምምነቱን ይዘት ቀደም ብለው ይፋ እንዲደረግ ሊወስኑ ይችላሉ ብለዋል።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ደግሞ የተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት ስዊትዘርላንድ ውስጥ ሲፈረም እዚያው የመጨረሻውን ስምምነት ለማድረግ የሚያስችል ድርድር እንደሚካሄድ አመልክተዋል።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት በበኩላቸው በኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ዙሪያ የሚካሄደው የቴክኒክ ንግግር በዚህ ሳምንት በሚካሄደው ድርድር ወቅት ይጀመራል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል።

  4. የኢራን ብሔራዊ ቡድን በዓለም ዋንጫ “በጣም መጨቆኑን” አሠልጣኙ ተናገሩ

    አሠልጣኝ አሚር ጋሌኖይ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን ብሔራዊ ቡድን አሠልጣኝ አሚር ጋሌኖይ በዓለም ዋንጫ ቡድናቸው “በጣም መጨቆኑን” ተናገሩ።

    ከኒው ዚላንድ ጋር ሁለት አቻ መውጣታቸውን ተከትሎ በሰጡት አስተያየት ከሁሉም የዓለም ዋንጫ ተሳታፊ አገራት የኢራን ቡድን “መጨቆኑን” ገልጸዋል።

    ተጫዋቾቹ በመጨረሻው ሰዓት የጉዞ ክልከላ እንደተጣለባቸው አሠልጣኙ ተናግረዋል።

    ከኒው ዚላንድ ጋር ከተጋጠሙ በኋላ በሎስ አንጀለስ ቆይተው ማረፍ ቢፈልጉም በአፋጣኝ ሜክሲኮ ወደሚገኘው የሥልጠና ማዕከል እንዲመለሱ ትዕዛዝ መተላለፉን አስረድተዋል።

    መጀመሪያ ላይ በተያዘው ዕቅድ መሠረት የዓለም ዋንጫ እስከሚጠናቀቅ ድረስ የኢራን ብሔራዊ ቡድን በአሪዞና ይቆያል ተብሎ ነበር። ኋላ ላይ ግን ወደ ሜክሲኮዋ ቲጁአና እንዲዛወሩ ተደርጓል።

    “ጨዋታው እንዳለቀ ‘ውጡ’ አሉን። አውሮፕላን ተሳፍረን ቲጁአና እንድንሄድ ተነገረን። በዚህም በጣም ተረብሸናል” ብለዋል።

    አሠልጣኙ አክለውም “ቀድመን እንድንሄድ እያስገደዱን ነው። ነገሮችን የበለጠ አክብደዋቸዋል። ነገር ግን በእነሱ ምክንያት ቡድናችን ምርጥ ከመሆን ወደኋላ አይልም” ሲሉ ተናግረዋል።

  5. “በሊባኖስ ላይ የሚፈጸም የእስራኤል ጥቃት ከአሜሪካ ጋር የተደረገው ስምምነት ጥሰት ነው” ኢራን

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    ከዚህ በኋላ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመው የትኛውም ዓይነት ጥቃት ከአሜሪካ ጋር የተደረሰውን የመግባቢያ ስምምነት የሚጥስ ነው ስትል ኢራን አስጠነቀቀች።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እንዳሉት ስምምነቱ ሲደረስ በአንድ በኩል ኢራን እና ሄዝቦላህ በሌላ በኩል ደግሞ አሜሪካ እና እስራኤል ሆነው ነው በማለት የእስራኤል ጥቃት እንዲቆም አሳስበዋል።

    አራግቺ አጽንኦት ሰጥተው እንደተናገሩት "በሊባኖስ ያለው ጦርነት ማብቃት ከአጠቃላዩ ጦርነት ማብቃት ተነጥሎ የሚታይ አይደለም፣ የጦርነቱ ማብቃት በተጨማሪም የወረራ ማብቃትንም የሚያካትት ነው” ብለዋል።

    በዚህም መሠረት “ከዚህ በኋላ የእስራኤል ወረራ በሊባኖስ መሬት ላይ የሚቀጥል ከሆነ የተደረሰውን የመግባቢያ ስምምነት ጥሰት ነው ብለን በእኛ በኩል እንመለከተዋለን” ሲሉ አራግቺ አስጠንቅቀዋል።

    ይህ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ንግግር የተሰማው እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ ወደሚገኙ ወታደሮቿ እየተጠጉ ነበር ያለቻቸው “ሽብርተኞች” ላይ ጥቃት መፈጸሟን ካሳወቀች በኋላ ነው።

    የሊባኖሱ ሄዝቦላህ ቡድን በበኩሉ ለእስራኤል ጥቃት ምላሽ ሚሳዔሎች እና ድሮኖችን ማስወንጨፉን ተናግሯል።

    አሜሪካ እና ኢራን ከስምምነት መድረሳቸው ይፋ ከሆነ በኋላ እስራኤል “የደኅንነት ቀጣና” ባለችው የሊባኖስ ግዛት ውስጥ ኃይሎቿ እንደሚቆዩ አሳውቃለች።

    በርካታ የእስራኤል መንግሥት ባለሥልጣናት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰውን የመግባቢያ ስምምነት አውግዘውታል።

  6. አሜሪካ 300 ሚሊዮን ዶላር ለኢራን ልትሰጥ ነው መባሉን ትራምፕ አስተባበሉ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ እና ኢራን ከስምምነት ከደረሱ በኋላ አሜሪካ እና አጋሮቿ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ለኢራን መልሶ ግንባታ ይሰጣል መባሉን ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተባበሉ።

    ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ እንደጻፉት ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ፈጽሞ እንደማይኖራት ከስምምነት ላይ መደረሱን ጠቅሰው፤ ነገር ግን አሜሪካ ለኢራን 300 ሚሊዮን ዶላር ለመስጠት ተስማምታለች የሚሉ ዘገባዎችን አስተባብለዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ "አሜሪካ ለኢራን 300 ሚሊዮን ዶላር ልትከፍል ነው በሚል የሚነገረው በደደብ ዲሞክራቶች የሚነገር ሐሰተኛ ዜና ነው” ብለዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ ደረሱበት የተባለው እና እራሳቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ፈርመውበታል የተባለው ጦርነቱን የሚያስቆመው የመግባቢያ ሰነድ ዝርዝር ዋነኛው ይዘት ይፋ አልሆነም። ነገር ግን ከኢራን እና ከአሜሪካ በኩል እየወጡ ያሉ የስምምነቱ ይዘቶች ላይ አንዳንድ ልዩነቶች እየታዩ ነው።

    ሁለቱም አገራት ከርቀት በኤሊክትሮኒክ መንገድ ተቀብለው የፈረሙትን የመግባቢያ ሰነድ ሙሉ ለሙሉ የተቀበሉት ሲሆን፣ የመጨረሻው ስምምነት አርብ ዕለት ስዊትዘርላንድ በተወካዮቻቸው አማካይነት ይፈረማል ተብሎ ይጠበቃል።

  7. የኢራንን ጦርነት የሚያስቆመው ስምምነት እንደተፈረመ፣ ዝርዝሩም በቅርቡ ይፋ እንደሚደረግ ትራምፕ አስታወቁ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን ጦርነት የሚያስቆመው ስምምነት እንደተፈረመ እና ዝርዝሩም ይፋ እንደሚደረግ አስታወቁ።

    የስምምነቱ ዝርዝር ይፋ ይደረጋል ተብሎ እየተጠበቀ ሲሆን፤ ይፋዊ ፊርማ የማኖር ሥነ ሥርዓቱ የፊታችን አርብ በጄኔቫ የሚከናወን ይሆናል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በበኩላቸው “ትግሉ አላከተመም” ብለዋል። አገራቸው አሁንም በተጠንቀቅ እንደቆመች እና በደቡብ ሊባኖስ “ከውጊያ ነጻ የሆነ ቀጣና” እንደሚኖራት ገልጸዋል።

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤሽኪያን ስምምነቱ በአግባቡ ከተተገበረ ለኢራን “የሚያኮራ ሰነድ” ነው ማለታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    አንድ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣን እንደተናገሩት የመግባቢያ ስምምነቱ መፈረሙን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ “በአፋጣኝ” ይከፈታል ተብሎ ይጠበቃል።

    በስምምነቱ መሠረት በሊባኖስ “ወታደራዊ ዘመቻ” መቆም እንዳለበት ተገልጿል። የሊባኖስ ባለሥልጣናት ተፈናቃዮች የአካባቢው ደኅንነት ሳይረጋገጥ እንዳይመለሱ ቢያሳስቡም ብዙዎች ወደ ቤታቸው እየተመለሱ ነው።

  8. በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ መርከቦች ክፍያ መፈጸም አይጠበቅባቸውም ተባለ

    ጄዲ ቫንስ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    አሜሪካ እና ኢራን በተስማሙበት የመግባቢያ ሰነድ መሠረት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚተላለፉ መርከቦች ክፍያ መፈጸም እንደማይጠበቅባቸው የአሜሪካው ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ገለጹ።

    ምክትል ፕሬዝዳንቱ ከሲኤንቢሲ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃል ምልልስ “የሆርሙዝ ወሽመጥ ለረዥም ጊዜ ከክፍያ ነጻ ይሆናል ብለን እንጠብቃለን” ብለዋል።

    ጦርነቱ መነሳቱን ተከትሎ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ለሚያልፉ መርከቦች የክፍያ ሥርዓት ዘርግታ ቆይታለች።

    አሁን ከአሜሪካ ጋር በተደረሰው ስምምነት አማካኝነት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ያለ ክፍያ ማለፍ ጊዜያዊ ሊሆን እንደሚችል የተናገሩት ጄዲ ቫንስ፤ ዘላቂ መፍትሔ ለማግኘት ከኢራን ጋር መወያየት እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል።

    ክፍያውን ማስቀረት “በቴክኒክ ድርድሩ ወቅት የምናነሳው ጉዳይ ይሆናል። አብረን በጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠን የምንወያይባቸው በጣም ጠቃሚ ነጥቦች ይኖራሉ” ብለዋል።

  9. የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት በቀጣይ ቀናት እንቅስቃሴ እንደሚጀመር ማክሮን ገለጹ

    ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን

    የፎቶው ባለመብት, YOAN VALAT/EPA/Shutterstock

    ከሁለት ወይም ከሦስት ቀናት በኋላ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ጥምር እንቅስቃሴ እንደሚጀመር የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ገለጹ።

    ዛሬ በፈረንሳይ እየተካሄደ ባለው የቡድን ሰባት ጉባዔ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ፈረንሳይ እና ዩናይትድ ኪንግደም የሆርሙዝ ወሽመጥን ነጻ እንቅስቃሴ ወደነበረበት ለመመለስ “በፍጥነት እርምጃ ለመውሰድ” ዝግጁ ናቸው ብለዋል።

    የሁለቱ አገራት ጥምር እንቅስቃሴ ወደ አካባቢው ተዋጊ አውሮፕላን እና ፈንጂ አምካኝ ባለሙያዎችን መላክን እንደሚያካትት ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

    “በቀጣናው ተዋጊ አውሮፕላን ጫኙ መርከብ ቻርለስ ደ ጎል አለን። የድጋፍ ቁሳቁስ ጭኗል። ስምምነቱ በተረጋገጠ በሁለት ወይም ሦስት ቀናት ሊሰማራ ይችላል” ብለዋል።

    ስምሪቱ የሚከናወነው ከአሜሪካ እና “በትይዩ ደግሞ ከኢራናውያን ጋር” መሆኑን ማክሮን ጠቅሰዋል። በዚህም የሆርሙዝ ወሽመጥ “በሰላም ተከፍቶ መዝለቁን” ማረጋገጥ እንደሚቻል አክለዋል።

  10. የኒውክሌር መርሃ ግብር እና ተያያዥ ጉዳዮች በሚቀጥሉት 60 ቀናት ውይይት ይደረግባቸዋል- የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዚም ጋሪባባዲ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዚም ጋሪባባዲ ከአሜሪካ ጋር የተደረሰውን ስምምነት ለማረጋገጥ እና የፊታችን አርብ በስዊትዘርላንድ ስለሚደረገው ይፋዊ የፊርማ ሥነ ስርዓት ለብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    ቴህራን አሜሪካ ላይ ስላላት የአመኔታ ችግር በድጋሚ ገልፀው፤ አገራቸው የአሜሪካን ቃል ኪዳኖች አፈፃፀም “እንደምትከታተል” ጠቅሰዋል።

    እስራኤል ቤይሩትን ማጥቃቷን ተከትሎ ቴህራን መዛቷ “የስምምነቱን ይዘት እንዲፋጠን ያገዘ እና አንዳንድ ጉዳዮችን የፈታ” እንደነበር ጠቁመዋል።

    ምክትል ሚኒስትሩ ኢራን ድርድሩ በ60 ቀናት ውስጥ ይጠናቀቃል የሚል ተስፋ እንዳላት ተናግረዋል። በኢራን ላይ የተጣሉ ሁሉም ማዕቀቦች እንዲነሱ እና ከአገሪቱ የኒውክሌር መርሃ ግብር ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ድርድር ከሚደረግባቸው ጉዳዮች ውስጥ መሆናቸውንም ገልፀዋል።

    በዚህ 60 ቀናት ውስጥ ጦርነቱን ተከትሎ ጉዳት የደረሰበትን የአገሪቱን ምጣኔ ሀብት ዳግም ለመገንባት የሚያስችሉ ጉዳዮችም የድርድሩ አካል ናቸው ብለዋል።

  11. ኢራን፤ እስራኤል በሊባኖስ የምትፈጽመው ጥቃት “ሙሉ በሙሉ መቆም አለበት” አለች

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰይድ አባስ አራጋቺ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/ Shutterstock

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰይድ አባስ አራጋቺ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ዛሬ ሰኞ ማለዳ ከቱርክ፣ ከኢራቅ እና ከግብፅ አቻዎቸው ጋር በስልክ መወያየታቸውን በቴሌግራም ገጻቸው ላይ አስታወቁ።

    አራግቺ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቹ ጋር እስራኤል በሊባኖስ የምትፈጽመው ጥቃት “ሙሉ በሙሉ መቆም እንዳለበት” መወያየታቸውን አስፍረዋል።

    አራግቺ አክለውም ይህንን ተግባራዊ ማድረግ የአሜሪካ ኃላፊነት እንደሆነም ገልጸዋል።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ አገራቸው ጦሯን የደኅንነት ቀጣና ብላ ከከለለችው ደቡባዊ ሊባኖስ፣ ጋዛ እና ሶሪያ እንደማታስወጣ አስታውቀዋል።

    ኢራን በሊባኖስ ባለው ሁኔታ የተነሳ ጥቃት የምትፈጽም ከሆነም አገራቸው “ሙሉ ኃይሏን ተጠቅማ” ምላሽ እንደምትሰጥ አስጠንቅቀዋል።

    ካትዝ በደቡባዊ ሊባኖስ ያለው የደኅንነት ቀጣና ከአካባቢው ነዋሪዎች እና “ከሁሉም የሽብር መሠረተ ልማቶች፣ በመንደሩ ከሚገኙ ከሄዝቦላህ ጋር ግንኙነት ያላቸው ቤቶች” ነጻ እንደሚሆን በመግለጫቸው ላይ ተናግረዋል።

  12. የእስራኤል ጦር በሊባኖስ ያለ ጊዜ ገደብ ለመቆየት እንደሚያስብ ሚኒስትሩ ገለጹ

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እዝራኤል ካትዝ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እዝራኤል ካትዝ

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል በሊባኖስ ያለምንም የጊዜ ገደብ የመቆየት ሃሳብ እንዳለው ሚኒስትሩ እዝራኤል ካትዝ አስታወቁ።

    ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት አሜሪካ እና ኢራን አደራዳሪዋ ፓኪስታን ባቀረበችው የመግባቢያ ሰነድ ላይ መስማማታቸውን ተከትሎ ነው።

    ሁለቱ አገራት“የትኛውንም ወታደራዊ ዘመቻዎች፣ በሊባኖስ ጨምሮ” ለማቆም ተስማምተዋል።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር በሂብሩ በጻፉት መግለጫ ጦራቸው ከሊባኖስ ይውጣ የሚለውን “ግልጽ በሆነ እና በሚጠበቁ ጫናዎች የተነሳ” ይቃወማል ብለዋል።

    መከላከያ ሚኒስትሩ ከቤንያሚን ኔታንያሁ ጋር ጦሩ በሊባኖስ፣ በሶሪያ እና ጋዛ “የደህንነት ቀጣናዎች ያለ ጊዜ ገደብ” እንደሚቆይ መነጋገራቸውን ጠቅሰዋል።

    አክለውም “ሁሉም የሽብር መሠረተ ልማቶች”፤ “የእስራኤልን ድንበሮች ለመከላከል” ይወድማሉ እንዲሁም ይህንን አቋሟን ለአሜሪካ ማሳወቋን ገልጸዋል።

    “ኢራን በሊባኖስ ባለው ሁኔታ የተነሳ ጥቃት ከፈጸመች ሙሉ ኃይላችንን ተጠቅመን ጥቃት እንፈጽማለን። ያለንንም የመከላከያ የበላይነት እናሳያለን።”

  13. ሊባኖስ ከአሜሪካ እና ኢራን የሰላም ስምምነት በኋላ ከቤታቸው የተፈናቀሉ ሰዎች ለመመለስ እንዳይቸኩሉ አስጠነቀቀች

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ከስምምነት መደረሱን የሰሙ የደቡብ ሊባኖስ፣ ሲዶን ነዋሪዎች ወደ ቀያቸው መመለስ ጀምረዋል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ከስምምነት መደረሱን የሰሙ የደቡብ ሊባኖስ ነዋሪዎች ወደ ቀያቸው መመለስ ጀምረዋል

    የደቡብ ሊባኖስ ባለሥልጣናት በሦስት ወሩ የእስራኤል እና ሄዝቦላህ ውጊያ የተፈናቀሉ ሰዎች ሰኞ ዕለት በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተደረሰውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ ለመመለስ እንዳይጣደፉ አስጠነቀቁ።

    ባለሥልጣናቱ ማስጠንቀቂያውን የሰጡት እስራኤል ጦሯን ከደቡባዊ ሊባኖስ እንደማታስወጣ በመናገሯ ነው።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ጦርነት ከተቀሰቀሰ በኋላ ሄዝቦላህ ወደ እስራኤል ሮኬቶችን በማስወንጨፉ በደቡባዊ ሊባኖስ ከፍተኛ አየር ድብደባ አካሄዳለች።

    እስራኤል በሊባኖስ ላይ በፈጸመችው ጥቃት 3,700 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፤ 1.2 ሚሊዮን ያህል ሰዎች ደግሞ ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራንን የምታሸማግለው ፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ አገራቱ ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን ይፋ ባደረጉበት ወቅት “ሊባኖስን ጨምሮ በሁሉም ግንባሮች የሚደረጉ ወታደራዊ ዘመቻዎች በቋሚነት እና አሁኑኑ እንዲቆሙ” መግባባታቸውን ተናግረዋል።

    የእስራኤል ጦር በተቆጣጠሯቸው የደቡባዊ ሊባኖስ አካባቢዎች የሚገኙ አስተዳዳሪዎች ነዋሪዎች እንዳይመለሱ ማስጠንቀቃቸውን የአገሪቱ ብሔራዊ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እዝራኤል ካትዝ አገራቸው ጦሯን የደህንነት ቀጣና ብላ ከከለለችው ደቡባዊ ሊባኖስ፣ ጋዛ እና ሶሪያ እንደማታስወጣ ገልጸው፣ ኢራን በሊባኖስ ባለው ሁኔታ የተነሳ ጥቃት የምትፈጽም ከሆነ ምላሽ እንደምትሰጥ ተናግረዋል።

    ካትዝ በደቡባዊ ሊባኖስ ያለው የደህንነት ቀጣና ከአካባቢው ነዋሪዎች እና “ሁሉም የሽብር መሠረተ ልማቶች፣ በመንደሩ የሚገኙ [ከሄዝቦላህ ጋር] ግንኙነት ያላቸው ቤቶች” ነጻ እንደሚሆን ተናግረዋል።

  14. ‘በዚህ ስምምነት እኛ አጋሮች አይደለንም፤ እኛን አይገዛም’- የእስራኤል ሚኒስትር

    እስራኤል ብሔራዊ የደኅንነት ሚኒስትር የሆኑት ኢትማር ቤን-ጋቪር

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የምስሉ መግለጫ, ቤን-ጋቪር እስራኤል ነፃ አገር እና በአሜሪካ ተገዢ እንዳልሆነች ተናግረዋል

    እሁድ ምሽት በፓኪስታን ይፋ በተደረገው የአሜሪካ እና የኢራን የስምምነት ማዕቀፍ ላይ እስራኤል ይፋዊ አስተያየት እስካሁን አልሰጠችም።

    ዛሬ ሰኞ ጠዋት ቀኝ አክራሪው የእስራኤል ብሔራዊ የደኅንነት ሚኒስትር ኢትማር ቤን-ጋቪር ግን አስተያየት ሰጥተዋል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረገውን ስምምነት በመተቸት “ደኅንነታችን በማያስጠብቀው በዚህ ስምምነት እኛ አጋሮች አይደለንም። እናም በየትኛውም መንገድ እኛን እይገዛም” ብለዋል።

    እስራኤል “ሄዝቦላህን ከመበታተን ያነሰ ነገር መቀበል የለባትም” ያሉት ሚኒስትሩ፤ በሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ላይ የሚደረገው እርምጃ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።

    “እያንዳንዱ ከእስራኤል ወደ ሊባኖስ የሚጓዝ ድሮን፣ ሰው አልባ በራሪ ወይም ሚሳዔል በዳሂያ ጥቃት ይፈጽማል” ሲሉም አክለዋል።

    ቤን-ጋቪር የራሳቸውን መንግሥት በተደጋጋሚ የሚተቹ ሲሆን፤ በዩናይትድ ኪንግደም እና በሌሎች አገራት “በፍልስጤም ማኅበረሰብ ላይ ተደጋጋሚ የግጭት ቅስቀሳ” በማድረግ ማዕቀብ ተጥሎባቸዋል።

  15. የአሜሪካ እና ኢራን ስምምነት ይፋ ከሆነ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ አሳየ

    ነዳጅ የሚቀዳ ግለሰብ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    አሜሪካ እና ኢራንን የምታሸማግለው ፓኪስታን ሁለቱ አገራት በመግባቢያ ስምምነቱ ላይ መስምምታቸውን ይፋ ካደረገች በኋላ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ አሳየ።

    ዶናልድ ትራምፕ ከስምምነቱ በኋላ የነዳጅ ዘይት መተላለፊያ የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ ዳግም ይከፈታል ብለዋል።

    ሰኞ ዕለት የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በ4.3 በመቶ ቀንሶ በበርሜል 83.55 ዶላር ተሸጧል።

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው ስምምነት አርብ ሰኔ 12 2018 ዓ.ም. በስዊትዘርላንድ ይፈረማል ብለዋል።

    የኢራን ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዘም ጋህሪባባዲ ለአገሪቱ ቴሌቪዥን በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ከአሜሪካ ጋር ድርድር ሲደረግበት የቆየው ሰነድ ላይ መስማማታቸውን አረጋግጠዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያቸው ላይ “ነዳጁ መፍሰስ ይጀምር” ሲሉ ጽፈዋል።

    የኢነርጂ ግብይት ተንታኝ የሆኑት ቫንዳና ሃሪ ግን የስምምነቱ ዝርዝር ነጥቦች ይፋ ባለመሆናቸው “በገበያው ላይ አለመረጋጋር እና እርግጠኝነት ማጣትን ሊያስከትል ይችላል” ሲሉ ተናግረዋል።

    አክለውም በዚህ ሳምንት በነዳጅ ገበያው ላይ መዋዠቅን እና እርግጠኛ አለመሆንን ልናይ እንችላለን ብለዋል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ የተዘጋው አሜሪካ እና እስራኤል ቴህራን ላይ የካቲት 21 2018 ኣ.ም. ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ ነው።

    ከጥቃቱ በኋላ ቴህራን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ በሚያልፍበት ሆርሙዝ በኩል በሚቀዝፉ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም ዝታለች።

    ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የዓለም አቀፉ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።

    ከግጭቱ በፊት ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት በበርሜል 70 ዶላር ይሸጥ ነበር።

    ጦርነቱ በተቀሰቀሰ በጥቂት ቀናት ይህ ዋጋ ወደ 120 ዶላር ከፍ ብሎ ነበር።

  16. የተባበሩት መንግሥታት እና የተለያዩ አገራት በኢራን እና አሜሪካ መካከል የተደረሰውን ስምምነት አደነቁ

    ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, Bloomberg via Getty Images

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉታሬዝ ቃል አቀባይ “ዩናይትድ ስቴትስ እና ኢራን የሰላም ስምምነቱ ላይ መድረሳቸውን ይፋ በማድረጋቸው” ደስተኛ መሆናቸውን ተናገሩ።

    ቃል አቀባዩ አክለውም “ይህ ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ወሳኝ እርምጃ” መሆኑን ገልጸዋል።

    የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሳናኤ ታካኢቺ በበኩላቸው የሰላም ስምምነቱን ካደነቁ የዓለም መሪዎች መካከል ናቸው።

    ጠቅላይ ሚኒስትሯ ጃፓን “በሆርሙዝ ወሽመጥ ነጻ እና ደኅንነቱ የተጠበቀ እንቅስቃሴ በተግባር እንደሚረጋገጥ በብርቱ ተስፋ ታደርጋለች” ካሉ በኋላ “በኢራን የኒውክሌር እና ሌሎች ጉዳዮች ላይ የመጨረሻው ስምምነት በቅርቡ ይደረሳል” ብለው እንደሚጠብቁም ተናግረዋል።

    የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒሲትር አንቶኒ አልባኔዝ ስምምነቱ “ቋሚ እና ዘላቂ ሰላም” ያመራል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

    “ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ ጊዜ ቢወስድም ይህንን ወሳኝ የንግድ መተላለፊያ መልሶ መክፈት በኢነርጂ ዋጋ እና ምጣኔ ሀብት ላይ የሚያደርሰውን ጫና ይቃለላል” ብለዋል።

    የኒው ዚላንድ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዊንስተን ፒተርስ “ወሳኝ እና ገንቢ ስምምነት” እንዲሁም “ውጥረትን ለመቀነስ እንዲሁም መረካካትን ለዓለም ምጣኔ ሀብት ደኅንነት ወሳኝ በሆነው ቀጣናው ለማምጣት” ቁልፍ እርምጃ መሆኑን ተናግረዋል።

    ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን እና ጣሊያን ከስምምነቱ በኋላ በጋራ ባወጡት መግለጫ አሜሪካን እና ኢራንም እንዲሁ በድርድሩ ውስጥ የተሳተፉትን በሙሉ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።

    “ይህ ቀጣናዊ መረጋጋት ለማምጣት እና ዓለም ምጣኔ ሀብትን ለማረጋጋት ጥሩ ዕድል ነው” ብለዋል።

    ስምምነቱ በፍጥነት እና በተሟላ መልኩ ተግባራዊ አንዲሆን ጥሪ ያቀረቡት አገራቱ የሆርሙዝ ወሽመጥ “ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እና ያለገደብ” እንዲከፈት ጠይቀዋል።

  17. አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለማቆም ከስምምነት የደረሱባቸው የመግባቢያ ነጥቦች ይፋ ሆኑ

    የአሜሪካ እና ኢራን ባንዲራዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን በቴህራን እና ዋሺንግተን መካከል ጦርነቱን ለማስቆም ስምምነት በተደረሰበት የመግባቢያ ሰነድ ውስጥ የተካተቱ ነጥቦችን ይፋ አድረገዋል።

    የመገናኛ ብዙኃኑ ባቀረቧቸው ዝርዝሮች ውስጥ የተካተቱት ነጥቦች በሁለቱም ወገን ማረጋገጫ አልተሰጠባቸውም።

    ሜህር የዜና ወኪል ከዘረዘራቸው ነጥቦች መካከል

    • በሁሉም ግንባሮች ሊባኖስን ጨምሮ በቋሚነት ተኩስ ይቆማል
    • አሜሪካ በኢራን ውስጣዊ ጉዳይ ጣልቃ አትገባም
    • በ30 ቀናት ውስጥ የአሜሪካ የባሕር ዕገዳ ይነሳል
    • የአሜሪካ ጦር ከኢራን ለቅቆ ይወጣል
    • የሆርሙዝ ወሽመጥ “በኢራናውያን ቁጥጥር” በ30 ቀናት ውስጥ ዳግም ይከፈታል
    • አሜሪካ እና አጋሮቿ 300 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የመልሶ ግንባታ ዕቅድ ያቀርባሉ
    • በኢራን የነዳጅ ዘይት እና ኢነርጂ ምርቶች ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ማንሳት
    • ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ላለማምረት ዳግም ታረጋግጣለች
    • አሜሪካ በቀጣናው ያላትን ጦር አትጨምርም እና አዲስ ማዕቀብም አትጥልም

    ሜህር አክሎም የስምምነቱ መጨረሻ የኢራን እንዳይንቀሳቀሱ የታገዱ ግማሽ ሃብቷ እስኪለቀቅ፣ የኢራን ነዳጅ ዘይት ላይ የተጣለው ማዕቀብ እና የባሕር ላይ ዕገዳው እስኪነሳ ድረስ የመጨረሻው ድርድር አይጀመርም ሲል ዘግቧል።

    እንዲሁም የመጨረሻው ስምምነት በተባበሩት መንግሥታት በፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔ እንደሚጸድቅ ዘግቧል።

  18. 15 ሰዓት የፈጀ ንግግር ወደ ስምምነት አድርሷል

    የኢራን ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዘም ጋህሪባባዲ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዘም ጋህሪባባዲ

    የኢራን ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የኳታር አሸማጋዮች ትናንት በቴህራን ተገኝተው በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ከስምምነት እንዲደረስ በረቂቅ የመግባቢያ ሰነዱ ላይ “ከ14 እስከ 15 ሰዓታት ያህል የረዘመ ንግግር” ማድረጋቸውን ገለጹ።

    ካዘም ጋህሪባባዲ ለኢራን መገናኛ ብዙኃን ሰኞ ዕለት እንደተናገሩት “ይህ ድርድር ረዥም ጊዜ የወሰደ ነው” ብለዋል።

    “የኳታር የልዑካን ቡድን ኢራን እና በዩናይትድ ስቴትስ ኢዝላማባድ ባቀረበችው የመግባቢያ ስምምነት ሰነድ ዙሪያ ውይይቶታቸውን እንዲቋጩ ለማስቻል ትናንት ቴህራን ነበሩ” ብለዋል።

    “ወደ 14 እና 15 ሰዓት የፈጀ ረዥም ንግግር ተካሄዷል። በዚህ ጊዜ የእስላማዊ ሪፐብሊክ ሰነዱ ላይ የመጨረሻውን ማሻሻያ አቅርባለች። እነዚያ ማሻሻያዎች ተቀባይነት አግኝተዋል። እንዲሁም ኢዝላማባድ ያቀረበችው የመግባቢያ ሰነድ ጸድቋል”

    ምክትል ሚኒስትሩ የኢራን ዋና ፍላጎት የተጣሉባት ማዕቀቦች እንዲነሱ ቢሆንም ”በርካታ የምታነሳቸው ጉዳዮች ስላሏት” የስምምነቱ የመጨረሻው ክፍል ላይ በ60 ቀናት ውስጥ ውይይት ይካሄዳል ብለዋል።

  19. ስምምነቱ “መካከለኛው ምሥራቅን ለሚቀጥሉት 50 ዓመታት በመሠረታዊነት የሚለውጥ ነው”-ቫንስ

    ጄዲ ቫንስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ ምክትል ፕሬዚዳንት ጄዲ ቫንስ ለፎክስ ኒውስ ስምምነቱ “በመሠረታዊነት መካከለኛው ምሥራቅን ለሚቀጥሉት 50 ዓመታት የሚለውጥ ነው” ሲሉ ተናገሩ።

    “ይህ የዓለማችን ቀጣና በእኔ የእድሜ ዘመን በሙሉ ከዚያም ለረዘመ ጊዜ የአለመረጋጋት ምንጭ ነበር” ሲሉ ለመገናኛ ብዙኃኑ ገልጸዋል።

    ቫንስ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ “የኢራንን ስጋትነት ማስወገድ ችለዋል” ሲሉም አሞካሽተዋቸዋል።

    አክለውም አሁን “የመካከለኛው ምሥራቅ ብልጽግና እና ስኬት አዲስ ዘመንን መገንባት ይቻላል” ብለዋል።

    “እውነቱን ለመናገር ከቀጣናው ለአሜሪካ ሕዝብ በርካታ ሃብት ማመንጨት እንችላለን” ሲሉም ተደምጠዋል።

  20. አሜሪካ እና ኢራን በሁሉም ግንባሮች፣ ሊባኖስን ጨምሮ ጦርነቱን ለማቆም ተስማሙ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ከሦስት ወር በላይ የቆየውን ጦርነት ለማስቆም የሚያስችል ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተናገሩ።

    ፕሬዚዳንቱ “ከእስላማዊ ሪፐብሊክ ጋር እያደረግን የነበረው ስምምነት አሁን ተሟልቷል” ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ድረ ገጻቸወ ላይ አስታውቀዋል።

    ትራምፕ ስምምነቱን ተከትሎ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ዘግቶት የነበረውን የኢራን ወደብ እንዲከፍት ያዘዙ ሲሆን መርከቦችም ያለምንም ክፍያ በወሽመጡ መጓዝ እንዲጀምሩ ተናግረዋል።

    “የዓለም መርከቦች አሁን ሞተራችሁን አንቀሳቅሱ። ነዳጅ መፍሰሱን ይቀጥል።”

    ሁለቱን አገር ስታደራድር የነበረቸው ፓኪስታን በጠቅላይ ሚኒስትሯ ሼህባዝ ሻሪፍ በኩል ባወጣችው መግለጫ ደግሞ “በተከታታይ ከተደረገ ንግግር በኋላ በዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ እና የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ መካከል ስምምነት ላይ መደረሱን ስናሳውቅ በደስታ ነው” ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ሁለቱም ወገኖች አሁኑኑ በሁሉም ግንባሮች፣ ሊባኖስን ጨምሮ ቋሚ የሆነ ወታደራዊ ዘመቻዎችን ለማቋረጥ መስማማታቸውን ገልጸዋል።

    “የፊርማ ሥነ ስርዓቱ አርብ ሰኔ 12 በስዊዘርላንድ ይካሄዳል። ጠቅላይ ሚኒስትር ሻሪፍ ሁለቱ አገራት ጦርነቱን ለማቆም ዲፕሎማሲያዊ መንገድን ለመፈለግ ላሳዩት ቁርጠኝነት እናመሰግናለን።"

    ለድርድሩ አስተዋጽኦ ያደረጉ ያሏቸውን ኳታርን፣ ሳዑዲ አረቢያን፣ እንዲሁም ቱርክን ጨምረው አመስግነዋል።

    “ከስምምነት ላይ በመደረሱ በዚህ ሳምንት ተከታታይ የሆኑ ስብሰባዎችን እናዘጋጃለን። ይህ የቅድመ ትግበራ ውይይት ዝርዝር ነገሮችን ለመነጋገር እና ለይፋዊ የፊርማ ሥነ ስርዓቱ መሠረት የሚጥል ይሆናል”ብለዋል።

    ኢራን በበኩሏ በምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ካዘም ጋሪባባዲ በኩል ሁለቱ አገራት ከስምምነት መድረሳቸውን አረጋግጠው አርብ እንደሚፈረም ተናግረዋል።

    “ከአሁን ጀምሮ በሁሉም ግንባሮች የሚደረጉ ወታደራዊ ዘመቻዎች፣ ሊባኖስን ጨምሮ እንደሚቆሙ" ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ተናግረው፣ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ እንቅስቃሴን ላይ የጣለችውን እገዳም እንደምታነሳ አስታውቀዋል።