የብራዚል ኮንግረስ የቦልሶናሮን የእስር ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ ለመቀነስ የሚያስችል ዕቅድ አጸደቀ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የብራዚል ኮንግረስ የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጃየር ቦልሶናሮ ባለፈው ምርጫ ከተሸነፉ በኋላ የመፈንቅለ መንግሥት አሲረው ነበር በሚል የተላለፈባቸውን የእስር ቅጣትን በእጅጉ የሚቀንስ ረቂቅ ሕግ ውድቅ አደረገ።
ቦልሶናሮ በ2022 ምርጫ ከሉዊዝ ኢናሲዮ ሉላ ዳ ሲልቫ ከተሸነፉ በኋላ በሥልጣን ለመቆየት ባደረጉት ሙከራ 27 ዓመታት እስራት ተፈርዶባቸዋል።
የቦልሶናሮን እስር ዘመን ከሁለት ዓመት ትንሽ ከፍ ያለ ለማድረግ የቀረበውን ሃሳብ ሉላ ድምጽን በድምጽ የመሻር መብታቸውን ተጠቅመው ሽረውት ነበር። ሕግ አውጪዎች ሐሙስ ዕለት የእስር ቅጣቱ እንዴት ይሰላል የሚለውን የፕሬዝዳንቱን ሃሳብ ውድቅ አድርገዋል።
ሕጉ በጠቅላይ ፍርድ ቤት ክርክር ሊደረግበት ይችላል።
የ71 ዓመቱ ቦልሶናሮ በመጋቢት ወር በጤና እክል ምክንያት ለጊዜው በቤታቸው እንዲታሰሩ ተፈቅዶላቸዋል።
ከ2019 እስከ 2022 በፕሬዝዳንትነት ያገለገሉት የቀድሞው የጦር ካፒቴን፣ ሉላን እና በምክትል ፕሬዝዳንትነት የተወዳደሩትን ጄራልዶ አልክሚንን ለመግደል ዕቅድ ነበራቸው በሚል ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛ ብሏቸዋል።
የአገሪቱ የጦር ኃይል ከፍተኛ አመራሮች ድጋፍ ሳይደረግላቸው በመቅረቱ ሴራው ባለመሳካቱ ሉላ በጥር 2023 ቃለ መሃላ ፈጸመዋል።
የሉላ ሃሳብ ውድቅ ከተደረገ በኋላ በርካታ የሕግ አውጪዎች 'ነፃነት' እያሉ መፈክር ያሰሙ ሲሆን፣ ፕሬዝዳንት ለመሆን ፍላጎት ያለውን የቀድሞ መሪው የበኩር ልጅ ፍላቪዮ ቦልሶናሮን ስም ደጋግመው ጠርተዋል።
ሁለት ሦስተኛ የሚሆኑ የኮንግረሱ አባላት የቀድሞውን ፕሬዚዳንትን የእስር ጊዜ ለመቀነስ የቀረበውን ዕቅድ በመደገፍ ድምጽ ሰጥተዋል።



















