አሜሪካ በሆርሙዝ በኩል ለማለፍ ለኢራን ቀረጥ የሚከፍሉ የመርከብ ድርጅቶች ላይ ማዕቀብ እንደምትጥል አስጠነቀቀች

አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ለማለፍ ለኢራን ተጨማሪ ክፍያ የሚከፍሉ የመርከብ ድርጅቶች ማዕቀብ እንደሚጣልባቸው አስጠነቀቀች። አርብ ዕለት በአሜሪካ የውጭ አገራት ንብረት ቁጥጥር ቢሮ ያወጣው ማስጠንቀቂያ አሜሪካውያን ግለሰቦችም ሆኑ ኩባንያዎች ለኢራን የመንግሥት ተቋማት ምንም ዓይነት ቀረጥ እንዳይከፍሉ ያግዳል። አሜሪካዊ ያልሆኑ ግለሰቦች እና ኩባንያዎች ደግሞ በወሽመጡ በኩል ለማለፍ ለቴህራን ቀረጥ የሚከፍሉ ከሆነ ማዕቀብ እንደሚጣልባቸው አስታውቋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. እስራኤል ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 14 ሰዎች ተገደሉ

    እስራኤል እሁድ ዕለት ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 14 ሰዎች ሲገደሉ፤ ሁለት ሕጻናት እና ሁለት ሴቶችን ጨምሮ 37 ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ገለጸ።

    የደረሰው ጉዳት ከመገለጹ አስቀድሞ የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ በተለያዩ የደቡባዊ ሊባኖስ መንደሮች የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲጡ አስጠንቅቀው ነበር።

    ነዋሪዎች በአፋጣኝ “መውጣት እንዳለባቸው” የሚያስጠነቅቅ መልዕክት የጻፈው ጦሩ፤ እዚያው መቆየት “ሕይወታቸውን አደጋ ላይ እንደሚጥለው” ገልጿል።

    የእስራኤል ጦር ከቆይታ በኋላ የሄዝቦላህ ወታደሮች እና “የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ወታደሮች ላይ ጥቃት ለመፈጸም” ይውላሉ ያላቸው የደቡባዊ ሊባኖስ ስፍራዎችን “በከባድ መሣሪያ እና የአየር ጥቃት” መምታቱን አስታውቋል።

    ሄዝቦላህ በፈጸመው ጥቃት የ19 ዓመት የእስራኤል ወታደር መገደሉን እና ስድስት ሰዎች መቁሰላቸውንም ገልጿል።

    እስራኤል እና ሊባኖስ ለሦስት ሳምንት የሚቆይ ተኩስ አቁም ተግባራዊ እንዲሆን ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ዕለት መስማማታቸው ይታወሳል።

    ይህ ስምምነት “በየትኛውም ጊዜ ራሷን ከታቀደ፣ አይቀሬ እና ቀጣይነት ያለው ጥቃት ለመከላከል አስፈላጊውን እርምጃ በሙሉ የመውሰድ መብትን” ለእስራኤል ሰጥቷል።

    ተኩስ አቁሙ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ አንስቶ እስራኤል እና ሄዝቦላህ አንዳቸው ሌላኛቸውን ስምምነቱን በመጣስ ከስሰዋል።

    14 ሰዎችን ከገደለውን ጥቃት አስቀድሞ ቅዳሜ ዕለትም የእስራኤል ጦር የሄዝቦላህ “ወታደራዊ ይዞታዎች” ባላቸው ስፍራዎች ላይ ጥቃት ፈጽሟል።

    ጦሩ ይህንን ጥቃት የፈጸመው በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ሁለት ፈንጂ የተሸከሙ ድሮኖችን ወደ እስራኤል አስወንጭፏል በሚል ነው።

    ቅዳሜ ዕለት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ የአገሪቱ ጦር ሊባኖስ ውስጥ የሚገኙ “የሄዝቦላህ ዒላማዎችን በኃይለኛው እንዲያጠቁ” ትዕዛዝ ሰጥተዋል። በዚሁ ዕለት ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በተፈጸሙ ጥቃቶች ስድስት ሰዎች ተገድለዋል።

  2. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር በስልክ መነጋገር እንደሚመርጡ እና ተደራዳሪዎቻቸውን እንደማይልኩ ተናገሩ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ሁለት ወር ሊደፍን የተቃረበውን ጦርነት የሚቋጭ ድርድር ማድረግ የምትፈልግ ከሆነ በስልክ መነጋገር እንችላን አሉ።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት ለፎክስ ኒውስ በሰጡት ቃለ መጠይቅ “መነጋገር ከፈለጉ፤ ማውራት እንችላለን። ሰዎችን ግን አንልክም” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ይህንን የተናገሩት አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞ ላይ እንደጣለችው ገደብ ያሉ የስምምነት እንቅፋቶች እንዲወገዱ ከጠየቀች በኋላ ነው።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቅዳሜ ዕለት ተደራዳሪዎቻቸው ስቲቭ ዋትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነርን ወደ ፓኪስታን ዋና ከተማ ኢስላማባድ እንደሚልኩ ከተናገሩ በኋላ ሁለቱ አገራት በድጋሚ ድርድር ይጀምራሉ የሚል ተስፋ ጭሮ ነበር።

    አርብ ዕለት ፓኪስታን ገብተው የነበሩት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ ግን የአሜሪካኑ ልዑካን ከመድረሳቸው አስቀድሞ ወደ ኦማን ተጉዘዋል።

    ትናንት እሁድ ለአጭር ቆይታ ተመልሰው ወደ ፓኪስታን ተጉዘው የነበረ ቢሆንም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ተደራዳሪዎቻቸውን የመላክ እቅዳቸውን አስቀድመው ሰርዘዋል።

    አራግቺ ከፓኪስታን ወጥተው ወደ ሩሲያ አምርተዋል። በዚያም ከፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር እንደሚገናኙ ይጠበቃል።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከዚህ ቀደም ኢራን እና አሜሪካን ስታደራድር ወደ ነበረችው ኦማን ባደረጉት ቆይታ ስለ ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ እንደተነጋገሩ ተገልጿል።

    ትራምፕ በፎክስ ቃለ መጠይቃቸው “መነጋገር ከፈለጉ ወደ እኛ መምጣት ወይም ሊደውሉልን ይችላሉ። ታውቃለህ፤ ቴሌፎን አለ። ጥሩ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ መስመር አለን” ሲሉ በድጋሚ ልዑካን እንደማይልኩ ጠቁመዋል።

    አክለውም፤ “ስምምነቱ ውስጥ ምን መኖር እንዳለበት ያውቃሉ። በጣም ቀላል ነው፤ የኒውክሌር መሣሪያ ሊኖራቸው አይችልም። ይህ ካልሆነ የምንገናኝበት ምክንያት አይኖርም” ማለታቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ከቆይታ በኋላ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “ማድረግ ያለባቸው መደወል ነው” በማለት ጽፈዋል።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት የፓኪስታን የፖለቲካ እና ወታደራዊ አመራሮች በቴህራን እና ዋሽንግተን መካከል የተኩስ አቁም እንዲፈረም እየጣሩ ባሉበት ወቅት ነው።

    የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ ፕሬስ ያነጋገራቸው አንድ የፓኪስታን ባለሥልጣን ቀጥተኛ ያልሆኑ ንግግሮች መቀጠላቸውን ገልጸዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት እንዲቆይ የተስማሙት ተኩስ አቁም ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ቢጠናቀቀም፤ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ላልተወሰነ ጊዜ አራዝመውታል። ይህም የካቲት ላይ የተጀመረው ውጊያ እንዲገታ አድርጓል።

    በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የተገደሉበት እና የዓለምን ኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ የከተተውን ጦርነት በዘላቂነት የሚቋጭ መፍትሔ ላይ ግን እስካሁን አልተደረሰም።