እስራኤል ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 14 ሰዎች ተገደሉ
እስራኤል እሁድ ዕለት ሊባኖስ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 14 ሰዎች ሲገደሉ፤ ሁለት ሕጻናት እና ሁለት ሴቶችን ጨምሮ 37 ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ገለጸ።
የደረሰው ጉዳት ከመገለጹ አስቀድሞ የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ በተለያዩ የደቡባዊ ሊባኖስ መንደሮች የሚገኙ ነዋሪዎች ለቅቀው እንዲጡ አስጠንቅቀው ነበር።
ነዋሪዎች በአፋጣኝ “መውጣት እንዳለባቸው” የሚያስጠነቅቅ መልዕክት የጻፈው ጦሩ፤ እዚያው መቆየት “ሕይወታቸውን አደጋ ላይ እንደሚጥለው” ገልጿል።
የእስራኤል ጦር ከቆይታ በኋላ የሄዝቦላህ ወታደሮች እና “የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት ወታደሮች ላይ ጥቃት ለመፈጸም” ይውላሉ ያላቸው የደቡባዊ ሊባኖስ ስፍራዎችን “በከባድ መሣሪያ እና የአየር ጥቃት” መምታቱን አስታውቋል።
ሄዝቦላህ በፈጸመው ጥቃት የ19 ዓመት የእስራኤል ወታደር መገደሉን እና ስድስት ሰዎች መቁሰላቸውንም ገልጿል።
እስራኤል እና ሊባኖስ ለሦስት ሳምንት የሚቆይ ተኩስ አቁም ተግባራዊ እንዲሆን ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ዕለት መስማማታቸው ይታወሳል።
ይህ ስምምነት “በየትኛውም ጊዜ ራሷን ከታቀደ፣ አይቀሬ እና ቀጣይነት ያለው ጥቃት ለመከላከል አስፈላጊውን እርምጃ በሙሉ የመውሰድ መብትን” ለእስራኤል ሰጥቷል።
ተኩስ አቁሙ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ አንስቶ እስራኤል እና ሄዝቦላህ አንዳቸው ሌላኛቸውን ስምምነቱን በመጣስ ከስሰዋል።
14 ሰዎችን ከገደለውን ጥቃት አስቀድሞ ቅዳሜ ዕለትም የእስራኤል ጦር የሄዝቦላህ “ወታደራዊ ይዞታዎች” ባላቸው ስፍራዎች ላይ ጥቃት ፈጽሟል።
ጦሩ ይህንን ጥቃት የፈጸመው በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ሁለት ፈንጂ የተሸከሙ ድሮኖችን ወደ እስራኤል አስወንጭፏል በሚል ነው።
ቅዳሜ ዕለት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ የአገሪቱ ጦር ሊባኖስ ውስጥ የሚገኙ “የሄዝቦላህ ዒላማዎችን በኃይለኛው እንዲያጠቁ” ትዕዛዝ ሰጥተዋል። በዚሁ ዕለት ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በተፈጸሙ ጥቃቶች ስድስት ሰዎች ተገድለዋል።