በሱዳን ጦርነት ኢትዮጵያዊያንን ጨምሮ የተለያዩ አገራት ቅጥረኛ ተዋጊዎች እንዳሉ ተነገረ

በሱዳን እየተካሄደ ባለው የእርስ በርስ ጦርነት ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ አገራት የመጡ ቅጥረኛ ተዋጊዎች እንደሚሳተፉ የሱዳን ባለሥልጣናት ተናገሩ። የሱዳን ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግም የሱዳን ጦር ኃይልን በመቀናቀን ከሚዋጋው የፈጥኖ ደራሽ ኃይል ጋር ተሰልፈው ሲዋጉ ነበር ባላቸው ከ120 በላይ የውጭ አገር ቅጥረኛ ወታደሮች ላይ ክስ መሥርቷል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ቭላድሚር ፑቲን፡ “1 ቢሊዮን ዶላር የምታወጣው” ግሪንላንድን ማንም ቢወስዳት ሩሲያ አይጨንቃትም

    የሩሲያው ፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የሩሲያው ፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን የግሪንላንድ ባለቤትነት ጉዳይ የሩሲያ ጭንቀት እንዳልሆነ ተናገሩ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው ፑቲን የግሪንላንድን ጉዳይ ዩናይትድ ስቴትስ እና ዴንማርክ ሊፈቱት ይገባል ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የዴንማርክ ክፍል የሆነችው ራስ ገዟን ደሴት ለመቆጣጠር ያላቸውን ፍላጎት በአፅንዖት መግለፃቸው በዩኤስ እና በአውሮፓ መካከል ክፍተት ፈጥሯል።

    የግሪንላንድን ጉዳይ በተመለከተ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ሐሳባቸውን የገለፁት ቭላድሚር ፑቲን ሀገራቸው የትራምፕን ዕቅድ እንደማትቃወም ጠቁመዋል።

    “በግሪንላንድ የሚፈፀም ማንኛውም ጉዳይ የኛ ጭንቀት አይደለም” ሲሉ ፑቲን በሩሲያ የፀጥታ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ተናግረዋል።

    “ዴንማርክ ግሪንላንድን እንደ ቅኝ ግዛት ነበር የምትቆጥራት። ጭካኔ የተሞላበት ነበር ማለትም ይቻላል” ሲሉ አክለዋል።

    ዴንማርክ ለዩክሬን የጦር መሣሪያ እና የገንዘብ ድጋፍ ካደረጉ ሀገራት መካከል መሆኗ ሩሲያን አስቆጥቷል።

    ትራምፕ ረቡዕ በዳቮስ ባደረጉት ንግግር በሩሲያ እና ዩክሬን መካከል ሰላም ለማምጣት እየሞከሩ እንደሆነ ተናግረዋል።

    በአውሮፓው 1867 ሩሲያ አላስካን ለአሜሪካ በ7.2 ሚሊዮን ዶላር መሸጧን ያወሱት ፑቲን፤ ግሪንላንድ ብትሸጥ ዋጋዋ 1 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ቢሆን ነው ሲሉ ተደምጠዋል።

  2. እስራኤል በጋዛ ባደረሰችው ጥቃት ሦስት ጋዜጠኞች መገደላቸውን የእርዳታ ሠራተኞች አስታወቁ

    እስራኤል በጋዛ ባደረሰችው ጥቃት ልጁን ያጣ አባት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል በማዕከላዊ ጋዛ ባደረሰችው ጥቃት ሦስት ፍልስጤማዊያን ጋዜጠኞች መገደላቸውን የእርዳታ ሠራተኞች አስታወቁ።

    በሐማስ የሚመራው የጋዛው ሲቪል ዲፌንስ ኤጀንሲ እንዳለው የድርጅቱ መኪና አል-ዛህራ አካባቢ ጥቃት የደረሰበት ሲሆን ሞሐመድ ሳላህ ቃሽታ፣ አናስ ግናይም እና አብዱል ራውፍ ሻት የተባሉ ግለሰቦች መገደላቸውን ገልጿል።

    የእስራኤል ጦር ሠራዊት “ከሐማስ ጋር ግንኙነት ያለው ድሮን ያንቀሳቅሱ የነበሩ በርካታ ተጠርጣሪዎች” ላይ ጥቃት መፈፀሙን አስታውቆ ጉዳዩን እየመረመረ እንደሆነ ገልጿል።

    በሌሎች ረቡዕ ዕለት በጋዛ በደረሱ የእስራኤል ጥቃቶች ሁለት ሕፃናትን ጨምሮ ስምንት ሰዎች መገደላቸውን በሐማስ የሚመራው የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    በእስራኤል እና ሐማስ መካከል ባለፈው ጥቅምት ከተፈረመው የተኩስ አቁም ስምምነት በኋላ ቢያንስ 466 ፍልስጤማዊያን እንደተገደሉ የጤና ሚኒስቴር ይናገራል።

    የእስራኤል ጦር ደግሞ በተመሳሳይ ጊዜ ሦስት ወታደሮቹ በፍልስጤሙ ታጣቂ ቡድን እንደተገደሉበት አስታውቋል።

    ረቡዕ ዕለት የተገደሉት የፎቶ ጋዜጠኞች ለግብፅ ተራድዖ ኮሚቴ የሚሠሩ ሲሆን በጋዛ ሰርጥ የተፈናቀሉ ሰዎች ሁኔታ ለመቅረፅ እንደመጡ ተነግሯል።

    ሐማስ ጥቃቱ “የተኩስ አቁም ስምምነቱን የሚጥስ እና ሁኔታዎችን የሚያባብስ አደገኛ ሁኔታ” ሲል ገልፆታል።

    አብዱል ራውፍ ሻት ለፈረንሳዩ የዜና ወኪል ኤኤፍፒ ይሠራ ነበር። ኤኤፍፒ የተሰማውን “ጥልቅ ሀዘን” ገልጿል።

    የጋዜጠኞች መብት ተቋርቋሪው ሲፒጄ በበኩሉ በጋዜጠኞቹ ግድያ “መደናገጡን” ገልጿል።

  3. ኢትዮጵያዊው በእንግሊዝ የስደተኞች ሆቴል ፆታዊ ትንኮሳ ፈፅሟል መባሉን አስተባበለ

    ሳውዝአምፕተን የሚገኘው ሀይፊልድ ሀውስ ሆቴል

    የፎቶው ባለመብት, Google

    የምስሉ መግለጫ, ሳውዝአምፕተን የሚገኘው ሀይፊልድ ሀውስ ሆቴል

    በእንግሊዟ ሳውዝአምፕተን ከተማ አንድ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ባረፈበት ሆቴል ፆታዊ ትንኮሳ ፈፅሟል መባሉን አስተባበለ።

    ኤርትራ የተወለደው ኢትዮጵያዊ መላኩ ገብረሰንበት የተባለው የ23 ዓመት ወጣት በቁጥጥር ሥር ውሎ ረቡዕ ሳውዝአምፕተን ፍርድ ቤት እንደቀረበ ተዘግቧል።

    የዋስትና ጥያቄው ተቀባይነት ያላገኘው ተጠርጣሪ የስደተኝነት ጉዳዩ እንዲታይለት አምስት ዓመት ያክል መቆየቱ ታውቋል።

    ተጠርጣሪው አንዲት ሴትን ቀርቦ ይዟታል በሚል በቁጥጥር ሥር የዋለ ሲሆን ትንኮሳውን አልፈፀምኩም ሲል አስተባብሏል።

    የሀምፕሸር ፖሊስ ባለፈው ሳምንት አርብ በሀይፊልድ ሀውስ ሆቴል ተፈጠረ የተባለውን ክስተት እየመረመረ መሆኑን አስታውቋል።

    የተጠርጣሪው ጠበቃ ኻሊድ ሚዙሪ “ኤርትራ ነው የተወለደው። ጥገኝነት መጠየቅ ከሚችሉ ሀገራት መካከል ከአንዷ ነው የመጣው። በኤርትራ በርካታ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ተፈፅመዋል። ባልታወቀ ምክንያት አምስት ዓመት ሙሉ ሲጠብቅ ቆይቷል። እስካሁን ውሳኔ አላገኘም” ብለዋል።

    ሪፖርት ለፖሊስ ከቀረበ በኋላ መርማሪዎች ወደ ሆቴሉ በማቅናት መረጃ እንደተቀበሉና ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ሥር እንዳዋሉ የስካይ ኒውስ ዘገባ አስነብቧል።

    ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄውን ለማየት ቀጠሮ ሰጥቷል።

    ሀይፊልድ ሀውስ ሆቴል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የበርካታ ፀረ-ስደተኛ ተቃዋሚዎች ሰልፍ ማዕከል ሆኗል። ስታንድ አፕ ቱ ሬሲዝም የተባለው ሰልፍ ደግሞ በተቃራኒው የስደተኞች መብት እንዲከበር የሚጠይቅ ነው።

    ከጥቂት ወራት በፊት ሐዱሽ ቅባቱ የተባለው ኢትዮጵያዊ ስደተኛ በፆታዊ ትንኮሳ እስር ተፈርዶበት ከዩናይትድ ኪንግደም ተባሮ ወደ ኢትዮጵያ መላኩ ይታወሳል።

  4. “አደገኛ ሁኔታ ነው” - ትራምፕ በአባይ ጉዳይ በኢትዮጵያ እና ግብፅ መካከል ድርድር ሊኖር እንደሚችል ጠቆሙ

    ትራምፕ እና የግብፁ ፕሬዝደንት አብድል ፋታህ አል-ሲሲ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ በአባይ ጉዳይ ኢትዮጵያ እና ግብፅ ከስምምነት መድረስ እንደሚችሉ እንደሚያምኑ ተናገሩ።

    ትራምፕ በዳቮስ የምጣኔ ሀብት ፎረም ላይ ከግብፁ ፕሬዝደንት አብድል ፋታህ አል-ሲሲ ጋር በነበራቸው የጎንዮሽ ውይይት ወቅት ነው የተናገሩት።

    የዓባይ ግድብ “የናይል ወንዝ እንዳይፈስ” ያደርጋል ያሉት ትራምፕ ሁለቱን ሀገራት ወደ ድርድር ለማምጣት እንደሚፈልጉ መናገራቸውን አናዶሉ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    “አደገኛ ሁኔታ ነው። ግድቡን የሠሩት [ግብፆች] ለሚሊዮን ዓመታት ውሀ በሚያገኙበት መንገድ ላይ ነው። አሁን የውሀ ፍሰቱ በአንድ ትልቅ ግድብ ምክንያት ተገድቧል” ሲሉ ከሲሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ ተናግረዋል።

    “ግድቡን በተለመከተ የሆነ ነገር ማድረግ እንዳለብን አስባለሁ። ግድቡ ትልቅ ችግር ነው። የሆነ ነገር እናደርጋለን” ሲሉ ትራምፕ አክለዋል።

    ትራምፕ ባለፈው ሳምንት በካይሮ እና አዲስ አበባ መካከል ድርድር የማስጀመር ሐሳብ እንዳላቸው መናገራቸው ይታወሳል።

    “አንተ ጠንካራ ፕሬዘደንት ነህ” ሲሉ ሲሲን ያደነቁት ትራምፕ ከግብፅ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር እንደሚሠሩ በውይይታቸው ወቅት መግለፃቸውን ፎክስ ኒውስ ዘግቧል።

    “ኢትዮጵያም ጠንካራ መሪ እንዳላት ሰምቻለሁ። እርግጥ ነው እንዳንተ አላውቀውም ግን ጠንካራ ሰው ነው። ሁለታችሁን አቀራርበን ከስምምነት ለመድረስ እንሞክራለን።”

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ባለፈው ሳምንት ለግብፅ ፕሬዝዳንት አብደል ፈታህ አል ሲሲ በጻፉት ደብዳቤ "ባለን የግል ወዳጅነት መንፈስ እና አሜሪካ ለግብፅ ሕዝብ ሰላም እና ደኅንነት ባላት ቁርጠኝነት" የሕዳሴ ግድብን የተመለከተ ድርድርን ለመጀመር እንደሚፈልጉ መግለፃቸው ይታወሳል።

    የኢትዮጵያ መንግሥት ይህን ደብዳቤም ሆነ ትራምፕ በዳቮስ የሰጡትን አስተያየት በተመለከተ እስካሁን ያለው ነገር የለም።

  5. ቢቢሲ ለዩቲዩብ የሚሆን ዝግጅቶችን ለማቅረብ የሚያስችለውን ስምምነት ፈረመ

    ዩቲዩብ የሚል ፅሑፍ የሚታይበት ሞባይል ስክሪን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ቢቢሲ የቪድዮ ማሠራጫ መድረክ ለሆነው ዩቲዩብ ዝግጅቶችን ለማቅረብ የሚያስችለውን ስምምነት መፈራረሙን ይፋ አደረገ።

    ቢቢሲ ከዚህ ቀደም የጉግል ንብረት በሆነው በዩቲዩብ በኩል በዩናይትድ ኪንግደም የሚዘጋጁ ይዘቶቹን ያስተዋውቅ እና ያሠራጭ ነበር።

    በአዲሱ ስምምነት መሠረት ቢቢሲ ለዩቲዩብ ወጣት ተመልካቾች የተቀረፁ ይዘቶችን ማዘጋጀት ይጀምራል። እነዚህ ይዘቶች በዩኬ በቢቢሲ አይፕሌየር እና ሳውንድስ በኩል ሊታዩ ይችላሉ።

    አዳዲሶቹ ፕሮግራሞቹ ከዩኬ ውጭ በዩቲዩብ ሲታዩ ማስታወቂያ የሚኖራቸው ሲሆን፣ ይህም ለኮርፖሬሽኑ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ይሆናል ተብሏል።

    ይዘቶቹ መዝናኛ፣ ስፖርት እና ዜና ላይ የሚያተኩሩ ሲሆኑ፣ በሚመጣው የካቲት ከሚካሄደው የክረምት ኦሊምፒክ ጀምሮ መሠራጨት ይጀምራሉ።

    ቢቢሲ እና ዩቲዩብ ረቡዕ በወጡት መግለጫ አዲሱ ስምምነት “ከመላው ቢቢሲ የሚመጡ ታሪኮች እና ዜናዎች የሚሠራጩበት” ነው ይላል።

    15 ሚሊዮን የዩቲዩብ ተከታዮች ያሉት የቢቢሲ ገፅ የሚያሠራጫቸውን ፕሮግራሞች ማስታወቂያ እና ቅንጫቢ ከማስተላለፍ ውጭ ሙሉ ይዘቶችን አያስተላልፍም።

    በተናጠል የቢቢሲ ዜና የዩቲዩብ ገፅ 19 ሚሊዮን ተከታዮች አሉት።

  6. የትራምፕ አውሮፕላን በገጠመው ችግር ምክንያት ለመመለስ ተገዶ እንደነበር ተሰማ

    የፕሬዝዳንቱ አውሮፕላን ተመልሶ እንዲያርፍ በተደረገበት ጊዜ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የፕሬዝዳንቱ አውሮፕላን ተመልሶ እንዲያርፍ በተደረገበት ጊዜ

    በስዊትዘርላንድ ዳቮስ በሚካሄደው የዓለም ኢኮኖሚ ፎረም የመሪዎች ጉባኤ ላይ ለመካፈል ጉዞ የጀመረው ዶናልድ ትራምፕ የተሳፈረቡት አውሮፕላን በገጠመው የቴክኒክ ችግር ምክንያት ተመልሶ ለማረፍ ተገዶ እንደነበር ተሰማ።

    ይህንንም በተመለከተ የፕሬዝዳንቱ ኤይር ፎርስ ዋን አውሮፕላን ”በአነስተኛ የኤሌክትሪክ ችግር" ምክንያት ተመልሶ እንዲያርፍ ተደርጓል ሲል ዋይት ሐውስ አስታውቋል።

    ከፕሬዝዳንቱ ጋር ጉዞ ጀምረው የነበሩ ጋዜጠኞች የአውሮፕላኑ መብራቶቹ ለአጭር ጊዜ ጠፍተው እንደነበር ተናግረዋል።

    አውሮፕላኑ ሜሪላንድ ወደሚገኘው አንድሪውስ የአየር ኃይል ጦር ሰፈር ከተመለሰ በኋላ ትራምፕ በሌላ አውሮፕላን ወደ ስዊትዘርላንድ ማቅናታቸው ታውቋል።

    በዚህም ምክንያት ፕሬዝዳንቱ ከሦስት ሰዓታት በላይ ዘግይተው ጉዟቸውን ጀምረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ በዳቮስ በሚካሄደው በዓለም ኢኮኖሚክ ፎረም ላይ ንግግር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    ኤይር ፎርስ ዋን አውሮፕላን የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ሲሳፈርበት ለራዲዮ ግንኙነት የሚውል ስያሜ ሲሆን፣ ለየትኛውም የአየር ኃይል አውሮፕላን የሚሰጥ ስያሜ ነው።

    በአሁኑ ወቅት በአየር ኃይል ውስጥ ከ1990 ጀምሮ ጥቅም ላይ የዋሉ ሁለት የቦይንግ 747-200B አውሮፕላኖች አገልግሎት እየሰጡ ነው።

    አውሮፕላኖቹ በየጊዜው ማሻሻያ ቢደረግላቸውም ወጪያቸው እየጨመረ መሆኑ ተነግሯል።

    ትራምፕ በአውሮፕላኑ ላይ በተደጋጋሚ ቅሬታ ሲያቀርቡ ቆይተዋል። ቦይንግ ሁለት አዳዲስ አውሮፕላኖችን በጊዜ ማድረስ ባለመቻሉ ምክንያት አስተዳደራቸው ባለፈው ዓመት "አማራጮችን እየፈለገ" መሆኑን አስታውቆ ነበር።

  7. የአውሮፓ ህብረት በግሪንላድ ጉዳይ “አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በአስቸኳይ እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀቱን” አስታወቀ

    የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ኡርሱላ ቮን ደር ሌየን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ኡርሱላ ቮን ደር ሌየን፤ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ግሪንላድን የመጠቅለል ዕቅዳቸውን በተቃወሙ የአውሮፓ አገራት ላይ ለመጣል ለዛቱት የታሪፍ ጭማሪ"በአስቸኳይ" የአጸፋ ምላሽ ለመውሰድ “ዝግጁ” መሆኑን ተናገሩ።

    ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን ለመግዛት ካላቸው ፍላጎት ጋር ተያይዞ እየተባባሰ የመጣውን ውጥረት የጠቀሱት ቮን ደር ሌየን፤ "ለደኅንነት ሲባል ተጨማሪ የታሪፍ ዛቻ መሰንዘር ስህተት ነው" ብለዋል።

    "አውሮፓ ውይይቶችን እና መፍትሄዎችን ትመርጣለች፤ ነገር ግን አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በአንድነት፣ በአስቸኳይ እና በቁርጠኝነት እርምጃ ለመውሰድ ሙሉ በሙሉ ተዘጋጅተናል" ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቷ በዓለም አቀፍ ሥርዓት ላይ እየታየ ያለው "ድንገተኛ የሆነ ለውጥ ብቻ ሳይሆን ቋሚ" ሽግግር ጭምር እንደሆነ ገልጸዋል።

    "አሁን የምንኖረው ቀጥተኛ ጉልበት በሚገለጽ ዓለም ውስጥ ነው" ብለዋል። አውሮፓ "ነፃነቷን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረት እንድታፋጥን" የማድረግ ጉዳይ “ውሳኝ” እንደሆንም አስረግጠዋል።

    የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በበኩላቸው አውሮፓ ኅብረት የአሜሪካ የታሪፍ ዛቻን በተመለከተ የአጸፋ እርምጃ የመውሰድን ጉዳይ ሊያጤነው እንደሚገባ አሳስበዋል።

    ፕሬዝዳንት ማክሮን ማክሰኞ ዕለት በዓለም ኢኮኖሚ ፎረም ላይ ባደረጉት ንግግር “ከጉልበተኝነት ይልቅ መከባበርን” እንዲሁም “ከጭካኔ ይልቅ የሕግ የበላይነትን" እንደሚመርጡ ተናግረዋል።

    ማክሮን የአውሮፓ ኅብረት በአሜሪካ ታሪፎች ላይ የአጸፋዊ እርምጃዎችን እንዲወስድ እያሳሰቡ ካሉ መሪዎች መካከል ናቸው።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ግሪንላንድን ለመግዛት የሚያደርጉትን ጥረት እየገፉበት መሆኑን እና ይህንን ዕቅዳቸውን በተቃወሙ ስምንት የአውሮፓ አገራት ላይ የታሪፍ ዛቻ መሰንዘራቸውን ተከትሎ በአሜሪካ እና በአውሮፓ መካከል ያለው ውጥረት ተባብሷል።

    የአውሮፓ መሪዎች የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ለሰነዘሩትን የታሪፍ ዛቻ ስለሚሰጡት ምላሽ ለመወያየት ነገ ሐሙስ እንደሚገናኙ የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝዳንቷ ቮን ደር ሌየን ተናግረዋል።

  8. የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቦይንግ ተጨማሪ አውሮፕላኖችን አዘዘ

    787-9 ድሪምላይነር ጄት

    የፎቶው ባለመብት, Boeing

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለረጅም ርቀት ጉዞዎች የሚውሉ ዘጠኝ 787-9 ድሪምላይነር ጄት አውሮፕላኖችን ከአሜሪካው የአውሮፕላን አምራች ቦይግን ለመግዛት ትዕዛዝ ሰጠ።

    በአፍሪካ ቀዳሚው አየር ትራንስፖርት አቅራቢ ኩባንያ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ግዙፉ አውሮፕላን አምራች ቦይንግ ጥያቄው መቅረቡን አስታውቀዋል። አውሮፕላኖቹ ተገንብተው ከአውሮፓውያኑ 2034 አስከ 2033 ባለው ጊዜ ውስጥ የሚቀርቡ ይሆናል ተብሏል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ እነዚህ ዘመናዊ አውሮፕላኖች ለመግዛት ትዕዛዝ ያቀረበው በአሁኑ ጊዜ በመላው ዓለም ያሉትን 145 ዓለም አቀፍ መዳረሻዎቹን ለማስፋት ባለው ዕቅድ እንደሆነ ተነግሯል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው "ዘላቂ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን ለማስፋት ባለን ስትራቴጂያዊ ራዕይ ምክንያት ተጨማሪ አውሮፕላኖችን መግዛታችንን እና ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀማችንን እንቀጥላለን” ማለታቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    አየር መንገዱ ከወራት በፊት ዱባይ ላይ በተካሄደው ዓለም አቀፍ ትዕይንት ወቅት 11 ቦይንግ ማክስ 737 ጄት አውሮፕላኖች ግዢን መፈጸሙ ይታወሳል።

    በተከታታይ ዓመታት በአፍሪካ ቁጥር አንድ አየር መንገድ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ መዳረሻዎቹን በማስፋት በየጊዜው የአውሮፕላኖቹን ቁጥር እያሰፋ ነው።

    ከሳምንት በፊትም በአፍሪካ ትልቁ የተባለው አውሮፕላን ማረፊያ ለመገንባት ከአዲስ አበባ 40 ኪሎ ሜትር ያህል ርቀት ላይ ሥራውን ጀምሯል።

  9. ከአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጋር በተያያዘ የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትርን የገደለው ግለሰብ ተፈረደበት

    ሺንዞ አቤ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ

    ከአራት ዓመት በፊት የቀድሞው የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤን አደባባይ ላይ ተኩሶ የገደለው ግለሰብ የዕድሜ ልክ እስር ተፈረደበት።

    የ45 ዓመቱ ተከሳሽ ቴጹያ ያማጋሚ የግድያ ክስ ቀርቦበት የፍርድ ሂደቱ መታየት በጀመረበት ጊዜ ወንጀሉን መፈጸሙን አምኖ ቃሉን ሰጥቶ ነበር።

    በጦር መሳሪያ የሚፈጸም ወንጀል 'የለም' በሚባል ደረጃ በሚገኝባት ጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር አቤን ጎዳና ላይ ተኩሶ የገደላቸው ግለሰብ በዕድሜ ልክ እስር እንዲቀጣ ዐቃቤ ሕግ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት ፍርድ ቤት ብይን ሰጥቷል።

    እናቱ አባል በሆኑበት ‘ዩኒፊኬሽን ቸርች’ በተባለው የእምነት ተቋም ምክንያት ኪሳራ ስለገጠማቸው ከቤተ ክርስቲያኗ መሪዎች ጋር ግንኙነት አላቸው በተባሉት የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ላይ በያዘው ቂም ነበር ያማጋሚ ግድያውን የፈጸመው።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ሲያደርጉ በጠራራ ፀሐይ ለመገደላቸው ምክንያት በሆነው ቤተክርስቲያን ከተከታዮቹ ላይ የሚሰበስበውን ከፍተኛ የገንዘብ ልገሳን ጨምሮ በሌሎች አጠያያቂ ተግባራት ላይ ምርመራ እንዲካሄድበት ተደርጓል።

    ጉዳዩም የጃፓን ገዢ ፓርቲ ሊብራን ዲሞክራቲክ ፓርቲ ፖለቲከኞች ከቤተክርስቲያኑ ጋር ያላቸውን ትስስር ያጋለጠ ሲሆን፣ በርካታ የአገሪቱ ሚኒስትሮችም ሥልጣን እንዲለቁ ምክንያት ሆኗል።

  10. በጉጂ ዞን ታጣቂዎች ምግብ ቤት ላይ በፈጸሙት ጥቃት ሁለት ሰዎች ሲገደሉ፤ አምስት ቆሰሉ

    የአካባቢው ጽህፈት ቤት

    የፎቶው ባለመብት, sm

    በኦሮሚያ ክልል በጉጂ ዞን ሳባ ቦሩ ወረዳ ውስጥ በሚገኝ ምግብ ቤት ላይ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ሁለት ሰዎች ወዲያውኑ ሲገደሉ አምስት ሰዎች ከባድ የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው ነዋሪዎች እና የአካባቢው ባለሥልጣን ተናገሩ።

    በሰዎች ላይ ሞት እና የአካል ጉዳት ያስከተለው ጥቃት የደረሰው ሰባት የሚሆኑ ታጣቂዎች ወደ ምግብ ቤቱ በመግባት በከፈቱት ተኩስ እንደሆነ ተገልጿል። ጥቃቱ በተፈጸመበት ወቅት ወደ 20 የሚደርሱ ሰዎች በምግብ ቤቱ ውስጥ ነበሩ ተብሏል።

    ከጥቃቱ የተረፈው እና አሁን በአካባቢው ባለው አዱላ ዎዩ ሆስፒታል ሕክምና እየተደረገለት የሚገኝ አንድ ግለሰብ ለቢቢሲ አፋን ኦሮሞ እንደተናገረው ጥቃቱን የፈጸሙት የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት ታጣቂዎች ናቸው።

    ባለፈው ቅዳሜ ጥር 9/2018 ዓ.ም. ምሽት አራት ሰዓት አካባቢ ታጣቂዎቹ ወደ ወደ ምግብ ቤቱ ከገቡ በኋላ በፈጸሙት ጥቃት አንድ የ80 ዓመት አዛውንትን ጨምሮ ሁለት ሰዎች ወዲያውኑ መሞታቸውን፣ አምስት ሰዎች ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ከመካከላቸው ሁለቱ በአስጊ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ የአካባቢው ባለሥልጣን አረጋግጠዋል።

    የሳባ ቦሩ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ ዳምቦቢ ዋጩ እንደተናገሩት በጥቃቱ የተገደሉት እና ጉዳት የደረሰባቸው ሁሉም ሰላማዊ ሰዎች ናቸው። ጥቃቱ የተፈጸመውም በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አባላት ነው ብለዋል።

    "ጥቃቱ የተፈጸመው በሰባ ቦሩ ወረዳ ሳቢቹ ኤላ ዲማ በተባለ ስፍራ ላይ ሲሆን፣ በሰላማዊው ሰዎች ላይ ወንጀሉን የፈጸሙት የሸኔ ታጣቂዎች ናቸው። በጥቃቱ በአጠቃላይ ዘጠኝ ሰዎች ቆስለዋል።"

    መንግሥት ‘ሸኔ’ የሚለው እና በሽብር ቡድንነት የሰየመው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት በምዕራብ እና በደቡብ ኦሮሚያ አካባቢዎች በተለያዩ ጊዜያት ጥቃት ሲፈጽም ቆይቷል።

    ቡድኑ የአሁኑን ጥቃት በተመለከተ እስካሁን ያለው ነገር የለም።

    ጥቃቱ ከተፈጸመ በኋላ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ወደ ቦታው ደርሰው ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች ለሕክምና ወደ ጤና ተቋማት እንዲወሰዱ ማድረጋቸውን ምክትል አስተዳዳሪው ገልጸዋል።

    ለሰዎች ሕይወት ማለፍ እና ለአካል ጉዳት ምክንያት የሆነውን ጥቃት የፈጸሙት ታጣቂዎቹ በአቅራቢያ ወደሚገኝ ጫካ ሸሽተው በመግባታቸው የመንግሥት ኃይሎች እየተከታተሏቸው እንደሆነ አቶ ዳምቢቦ ተናግረዋል።

    ከዚህ ቀደምም ታጣቂዎች በሚንቀሳቀሱበት ሳባ ቦሩ ወረዳ ተመሳሳይ ጥቃት ይፈጸም የነበረ ሲሆን፣ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ የፀጥታው ሁኔታ ተሻሽሎ እንደነበር ባለሥልጣኑ አመልክተዋል።

  11. ቶጎ የቡርኪና ፋሶ ፕሬዝዳንት ትራኦሬን ለመግደል አሲረዋል የተባሉትን የቀድሞ መሪ አሳልፋ ሰጠች

    የቀድሞው የቡርኪና ፋሶ መሪ ፖል ሄንሪ ሳንዳኦጎ ዳሚባ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ቶጎ የቡርኪና ፋሶ ፕሬዝዳንት ኢብራሂም ትራኦሬን ለመግደል በማሴር የተወነጀሉትን የአገሪቱ የቀድሞ መሪን በቁጥጥር ስር በማዋል አሳልፋ ሰጠች።

    በአውሮፓውያኑ 2022 መፈንቅለ መንግሥት አድርገው ወደ ሥልጣን የወጡት የቀድሞው መሪ ፖል ሄንሪ ሳንዳኦጎ ዳሚባ፤ ከስምንት ወራት በኋላ ከሥልጣን የወረዱት በአሁኑ ፕሬዝዳንት በተፈጸመባቸው ግልበጣ ነበር።

    ኋላ ላይ ደግሞ ፕሬዝዳንት ትራኦሬ ላይ የግድያ ሙከራ በማቀነባበር ተከስሰዋል።

    የቀድሞው መሪ ዳሚባ ለቡርኪና ፋሶ ባለሥልጣናት ተላልፈው የተሰጡት ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ዕለት እንደሆነ ከቶጎ የፍትሕ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያሳያል።

    ተላልፈው ሲሰጡ በተደረሰው ስምምነት መሠረት ቡርኪና ፋሶ፤ “የፖል ሄንሪ ሳንዳኦጎ ዳሚባን አካላዊ ደኅንነት፣ ክብር እና ፍትሃዊ የፍርድ ሂደት መብቶችን ለማረጋገጥ እንዲሁም የሞት ቅጣት ላለመጣል" ቃል ገብታለች።

    የቶጎ ፍትሕ ሚኒስቴር መግለጫ እንደሚያስረዳው፤ ቀድሞው መሪ ላይ የቀረቡት ክሶች “የመንግሥት ገንዘብን ያለአግባብ ማባከን፣ በሕገ-ወጥ መንገድ መበልጸግ፣ ሙስና፣ የተሰረቁ ንብረቶችን መረከብ እና በሕገ ወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አድርጎ ማቅረብ” የሚሉት ናቸው።

    ዳሚባ የቀረቡባቸውን ክሶች በተመለከተ እስካሁን የሰጡት አስተያየት የለም፤ ቢቢሲ ያደረገው የስልክ ጥሪም ምላሽ አላገኘም።

    ከክሶቹ ውስጥ እጅግ ከባዱ የአሁኑን ፕሬዝዳንት ለመግደል አሲረዋል በሚል የቀረበው ውንጀላው ነው።

    ባለፈው ታኅሣሥ ወር ላይ ትራኦሬ ላይ ሊፈጸሙ የታቀዱ ተከታታይ የግድያ ሙከራዎች እና አገር የማተራመስ ሴራዎች በፀጥታ ኃይሎች መክሸፋቸውን የቡርኪና ፋሶ የደኅንነት ሚኒስትር ማሃማዱ ሳና ተናግረው ነበር።

    የቡርኪና ፋሶ መንግሥት ባለሥልጣናት ዳሚባ በስደት ባሉበት እነዚህን ድርጊቶች እያቀነባበሩ እንደሆነ በመግለጽ በተደጋጋሚ ከስሰዋል። በአውሮፓውያኑ 2024 መጨረሻ ላይም ባለሥልጣናት "ወታደራዊ ክንፍ" ብለው የጠሩት ሰፊ ሴራ ዋና መሪ ዳሚባ እንደሆኑ ተናግረው ነበር።

  12. ትራምፕ ግሪንላንድን የመቆጣጠር ጉዳይ ላይ “ወደ ኋላ መመለስ የለም” አሉ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Re

    ፕሬዳንት ትራምፕ ግሪንላንድን በአሜሪካ ቁጥጥር ስር ማስገባት “ወሳኝ ጉዳይ ነው” እንደሆነ እና ይህንን አቋማቸውን በተመለከተ "ወደ ኋላ መመለስ እንደሌለ” ለጋዜጠኞች ተናገሩ።

    ዋይት ሐውስ ውስጥ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ግሪንላንድን በተመለከተ ሥራዎች በጥሩ ሁኔታ እየተካሄዱ መሆናቸውን የገለጹት ትራምፕ፤ ውጤቱን “በቅርቡ ታዩታላችሁ” ብለዋል።

    በግሪንላንድ ምክንያት ከኔቶ ጋር ያላቸውን ግንኙነት የሚያቋርጡበት ሁኔታ ይኖር እንደሆነ በቢቢሲ የተጠየቁት ትራምፕ "በሁሉም መንገድ ለኔቶ የእኔን ያህል የሠራ የለም” በማለት ተናግረዋል። ግሪንላንድን የተመለከተው ውሳኔያቸው “ለዓለም ደኅንነት ስለሚፈለግ ኔቶም ሆነ እኔ ደስተኞች እንሆናለን” ሲሉም ገልጸዋል።

    ግሪንላንድን ለመጠቅለል ወታደራዊ ኃይል መጠቀምን በተመለከተ ትራምፕ ከምርጫቸው ወጪ አለመሆኑ የተነገረ ሲሆን፣ በኤንቢሲ ኒውስ ኃይል ይጠቀሙ እንደሆነ ላቀረበላቸው ጥያቄ “መልስ አልሰጥም” ብለዋል።

    የግሪንላንድ የኢንዱስትሪ እና የተፈጥሮ ሀብት ሚኒስትር ናጃ ናታኒየልሰን ለቢቢሲ እንደተናገሩት ግሪንላንዳውያን በትራምፕ ፍላጎት ግራ መገባታቸውን በመግለጽ “አሜሪካዊ መሆን እንደማንፈልግ በደንብ ግልጽ አድርገናል” ብለዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ስዊዘርላንድ ውስጥ እየተካሄደ ባለው የዓለም ኢኮኖሚ ፎረም ላይ የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ባደረጉት ንግግር ዓለም “ሕግ ወደሌለበት አቅጣጫ እያመራች ነው” በማለት አስጠንቅቀዋል። የካናዳው ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ካርኒ በኩላቸው “አሮጌው ሥርዓት ተመልሶ አይመጣም" ብለዋል።

  13. የሙሴቬኒ ልጅ በአባታቸው በምርጫ የተሸነፈው ተቃዋሚ ፖለቲከኛ እጁን እንዲሰጥ አዘዙ

    ጄነራል ሙሁዚ ካይኔሩጋባ
    የምስሉ መግለጫ, ጄነራል ሙሁዚ ካይኔሩጋባ

    አወዛጋቢው የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ልጅ እና የአገሪቱ ጦር ኃይሎች አዛዥ ጄነራል ሙሁዚ ካይኔሩጋባ አባታቸው ባሸነፉበት ምርጫ ዋነኛ ተፎካካሪ የነበረውን የተቃዋሚ ፓርቲ ፕሬዝዳንታዊ ዕጩ እጁን እንዲሰጥ አስጠነቀቁ።

    ጄነራሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ ከምርጫው በኋላ ለደኅንነቱ በመስጋት ተደብቆ የሚገኘው የቀድሞ ሙዚቀኛ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ቦቢ ዋይን በ48 ሰዓታት ውስጥ እጁን እንዲሰጥ አዘዋል።

    ቦቢ ዋይን ፕሬዝዳንት ሙሴቬኒ በ81 ዓመታቸው ለሰባተኛ ጊዜ ያሸነፉበት ምርጫ ውጤት ይፋ ከመሆኑ በፊት የመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች ከቤቱ ሊይዙት ሲመጡ ማምለጡን እና ተደብቆ እንደሚገኝ አሳውቋል።

    ዋይን በምርጫው በከፍተኛ የድምጽ ብልጫ በሙሴቬኒ ተበልጦ ሁለተኛ መሆኑ ከመገለጹ በፊት ምርጫው መጭበርበሩን የሚገልጹ ተደጋጋሚ መግለጫዎችን በማውጣት ሕዝቡን ለሰላማዊ ተቃውሞ ጠርቷል።

    ጄኔራሉ የአባታቸው ሥልጣን ይሆናሉ ተብሎ በስፋት የሚታመን ሲሆን፣ ለተቃዋሚው ፖለቲከኛ በማኅበራዊ ሚዲያ ጠንከራ ማስጠንቀቂያ አስተላልፈዋል።

    ቦቢ ዋይን "በ48 ሰዓታት ውስጥ እጁን ለፖሊስ የማይሰጥ ከሆነ እንደ ሕገወጥ/አመጸኛ ተቆጥሮ እርምጃ ይወሰድበታል" ሲሉ ኤክስ ላይ አስፍረዋል።

    ጄነራሉ በሌላ የማኅበራዊ ሚዲያ መልዕክታቸው "ካለፈው ሳምንት ወዲህ 22 የኤንዩፒ [የቦቢ ዋይን ፓርቲ] ሽብርተኞችን ገድለናል" ሲሉ እርምጃ መወሰዱንም ገልጸዋል።

    ከምርጫው ጋር በተያያዘ በርካታ አንዳንድ ሪፖርቶችም በመቶዎች የሚቆጠሩ የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎች ተገድለዋል ብለው ያመለክታሉ።

    ቦቢ ዋይን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የተቃዋሚ ፓርቲው መሪ ቦቢ ዋይን
  14. የአውሮፓ ኅብረት ከዴንማርክ እና ከግሪንላንድ ጎን እንደሚቆም አስታወቀ

    የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽነር ኧርሰላ ቮን ደር ላይን

    የፎቶው ባለመብት, EBU

    የምስሉ መግለጫ, የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽነር ኧርሰላ ቮን ደር ላይን

    የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽነር ኡርሱላ ቮን ደር ላይን፤ ኅብረቱ ለግሪንላንድ እና ለዴንማርክ “ሙሉ ድጋፍ” እንደሚሰጥ አስታወቁ። ሉዓላዊነት “ለድርድር አይቀርብም” ሲሉም ተናግረዋል።

    በዳቮስ የቡድን ስምንት ላይ ንግግር ያደረጉት ኮሚሽነሯ፤ የአውሮፓ ኅብረት ከዴንማርክ እና ከግሪንላንድ ጋር “እጅ ለእጅ ተያይዞ” እንደሚሠራ ገልጸዋል። በምጣኔ ሃብት እና በመሠረተ ልማት ዘርፍ ድጋፍ መስጠት እንደሚቀጥሉም አክለዋል።

    የአውሮፓ ኅብረት “የአርክቲክን ደኅንነት ለመጠበቅ” ከአሜሪካ እና ከሌሎችም አጋሮች ጋር “በጋራ ፍላጎቶች ላይ በማተኮር” እንደሚሠራ ገልጸዋል።

    ካናዳ፣ ኖርዌይ እና ዩናይትድ ኪንግደምን ጨምሮ በአውሮፓ ያሉ አገራት “የጋራ ደኅንነት” ትኩረት እንደሚሰጠው የገለጹት ኮሚሽነሯ “አውሮፓ አዲስ የደኅንነት መዋቅርን መላመድ አለባት” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን የመጠቅለል ዕቅዳቸውን በማይደግፉ የአውሮፓ አገራት ላይ ታሪፍ ለመጣል መዛታቸውን “ስህተት” መሆኑንም ገልጸዋል።

    ያለፈው ነሐሴ የአውሮፓ ኅብረት እና አሜሪካ የንግድ ስምምነት መፈራረማቸውን በማስታወስ “ስምምነት፣ ስምምነት ነው። ወዳጆች ሲጨባበጡ ትርጉም ሊኖረው ይገባል” ብለዋል።

    ትራምፕ ታሪፍ የሚጥሉ ከሆነ ግን የአውሮፓ ምላሽ “የጋራ፣ ቆራጥ እና የማያዳግም” እንደሚሆን ኮሚሽነሯ አስረግጠው ተናግረዋል።

  15. ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ በኩል የከፈቱት ዘመቻ እና የገጠማቸው ውዝግብ

    ትራምፕ ግሪንላንድ ላይ የአሜሪካን ሰንደቅ ዓላማ ሲያቆሙ የሚያሳይ የፈጠራ ምሥል

    የፎቶው ባለመብት, Truth Social/ Donald Trump

    ትራምፕ የዴንማርክ አንድ አካል በሆነችው ግሪንላንድ ላይ የይገባኛል ጥያቄ አንስተው ግዛቲቱን የመጠቅለል ፍላጎታቸው በተጠናከረበት በአሁኑ ወቅት ከአውሮፓ ኅብረት አጋሮቻቸው ጋር እሰጣገባ ውስጥ ገብተዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት የአውሮፓ ኅብረት አባል በሆነችው ዴንማርክ ግዛት ላይ የይገባኛል ጥያቄ በማንሳታቸው ከሌሎች አባል አገራት ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።

    በዚህም የተነሳ ትራምፕ በተቃወሟቸው አገራት ላይ ከፍተኛ ታሪፍ ለመጣል መዛታቸው ሌላ ውዝግብ ፈጥሯል። ትራምፕ ግን በየትኛውም መንገድ ግሪንላንድን በእጃቸው ለማስገባት የቆረጡ ይመስላሉ።

    ፍሎሪዳ ውስጥ ግሪንላንድን በተመለከተ ምን ዕቅድ እንዳላቸው ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ “[ግሪንላንድ] የእኛ መሆን አለባት” ሲሉ አጭር ምላሽ ሰጥተዋል።

    የራሳቸው በሆነው ትሩዝ ሶሻል በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ መድረክ ላይ ደግሞ እሳቸው የአሜሪካንን ሰንደቅ ዓላማ ግሪንላንድ ላይ ሲተክሉ የሚያሳይ የፈጠራ ምሥል አጋርተዋል።

    ትራምፕ ከአውሮፓ መሪዎች ጋር

    የፎቶው ባለመብት, Truth Social/ Donald Trump

    የምስሉ መግለጫ, ካርታው የተለወጠበት ፎቶ

    በተጨማሪም ከዚህ በፊት ከአውሮፓ አገራት መሪዎች ጋር ባደረጉት ውይይት ወቅት የተነሳ ፎቶ ላይ የነበረ ካርታን በመለወጥ ካናዳን እና ግሪንላንድን የአሜሪካ አድርገው በማስተካከል ፎቶውን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አውጥተዋል።

    በተጨማሪም የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን መወያየት እንደሚፈልጉ እና ግሪንላንድን በተመለከተ ምን እያደረጉ መሆናቸውን በመጠየቅ የላኩላቸውን የጽሁፍ መልዕክት አጋርተዋል።

    እንዲሁም የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን አገራት ማኅበር ኔቶ ዋና ፀሐፊ ማርክ ሩተ ግሪንላንድን በተመለከተ “መፍትሄ ለመፈለግ ቁርጠኛ” መሆናቸውን የሚያመለክት የጽሁፍ መልዕክትም አጋርተዋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ረዳት ዳረን ጆንስ ትራምፕ በግሪንላንድ ላይ በያዙት አቋም ምክንያት በአውሮፓው አጋሮቻቸው ላይ ታሪፍ ለመጣል ማቀዳቸውን “አዋጪ አይደለም” ሲሉ ተችተዋል።

    ትራምፕ ከአውሮፓ መሪዎች ጋር

    የፎቶው ባለመብት, Truth Social/ Donald Trump

    የምስሉ መግለጫ, ትክክለኛው ካርታ ያለበት ፎቶ
  16. ትራምፕ፤ ዩኬ ቼጎስ ደሴቶችን አሳልፋ መስጠቷ “ታላቅ ድድብና” ነው አሉ

    ትራምፕና ሰር ኪር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ “ዩናይትድ ኪንግደም ቼጎስ ደሴቶችን አሳልፋ መስጠቷ ታላቅ ድድብና ነው” ሲሉ ተቹ።

    ፕሬዝደንቱ በማኅበራዊ ሚድያ ገፃቸው ላይ ባሰፈሩት ሐሳብ “የኔቶ ‘ድንቅ’ አጋራችን የሆነችው ዩኬ ዲየጎ ጋርሲያ ደሴትን ያለምንም ምክንያት ለሞሪሺየስ አሳልፋ እየሰጠች ነው” ብለዋል።

    “ዩኬ ይህን በጣም ጠቃሚ ደሴት አሳልፋ መስጠቷ ታላቅ ድድብና ነው። ለዚህ ነው ለብሔራዊ ደኅንነታችን ግሪንላንድን መቆጣጠር አለብን የምንለው።”

    ባለፈው የአውሮፓውያኑ ዓመት ትራምፕ ዩኬ ቼጎስ ደሴትን ለሞሪሺየስ መልሳ መስጥቷን መደገፋቸው ተዘግቦ ነበር።

    ደሴቶቹ ሞሪሺየስ የብሪታኒያ ቅኝ ግዛት ሳለች በአውሮፓውያኑ 1965 ተገንጥለው ነበር። ብሪታኒያ ደሴቶቹን በ3 ሚሊዮን ፓውንድ ነበር የገዛችው።

    ነገር ግን ሞሪሺየስ ደሴቶቹ ከብሪታኒያ ነፃ ለመውጣት ሲባል በግድ ተላልፈው የተሰጡ ናቸው ስትል ተከራክራለች።

    ዩናይትድ ኪንግደም እና ዩናይትድ ስቴትስ ከደሴቶቹ መካከል አንዱ በሆነው ዲየጎ ጋርሲያ ወታደራዊ ካምፕ አላቸው። በካምፑ ግንባታ ወቅት በርካታ ሺህ ሰዎች ከመኖሪያቸው ተፈናቅለዋል።

    ባለፈው ዓመት ብሪታኒያ ደሴቶቹን መልሳ ለመስጠት በወሰነች ወቅት የዩኬው ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር የአሜሪካው ፕሬዝደንት “ውሳኔውን ደግፈዋል” ብለው ተናግረው ነበር።

  17. የአፍሪካ ቀንድ ውጥረት፡ ሶማሊያ እና ኳታር ወታደራዊ ስምምነት ተፈራረሙ

    የሶማሊያው መከላከያ ሚኒስትር አሕመድ ማሊን ፊቂ እና የኳታር አቻቸው ሳውድ ቢን አብዲራህማን ቢን ሐሰን አል-ታኒ

    የፎቶው ባለመብት, Sonna

    የምስሉ መግለጫ, የሶማሊያው መከላከያ ሚኒስትር አሕመድ ማሊን ፊቂ እና የኳታር አቻቸው ሳውድ ቢን አብዲራህማን ቢን ሐሰን አል-ታኒ

    ሶማሊያ እና ኳታር ወታደራዊ ትብብራቸውን ለማጠናከር ስምምነት መፈራማቸው ተሰማ።

    ስምምነቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ወታደራዊ ጥምረት ለማጠናከር የፀጥታ ትብብር ለማስፋፋት ያቀደ እንደሆነ ተዘግቧል።

    ስምምነቱን የሶማሊያው መከላከያ ሚኒስትር አሕመድ ማሊን ፊቂ እና የኳታር አቻቸው ሳውድ ቢን አብዲራህማን ቢን ሐሰን አል-ታኒ እንደተፈራረሙት የሶማሊያ መንግሥት የዜና ወኪል የሆነው ሶና ዘግቧል።

    ሚኒስትሮቹ ዶሀ እየተካሄደ በሚገኘው ዓለም አቀፍ የማሪታይም ወታደራዊ ኤግዚቢሽን ላይ ስምምነቱን እንደተፈራረሙ ተነግሯል።

    ሶና እንደዘገበው የሁለቱ ሀገራት ስምምነት በቀጣናዊ ሰላም እና መረጋጋት ላይ ለመሥራት ያለመ ነው።

    በቅርቡ ከዩናይትድ አረብ ኤሜሬቶች ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ሙሉ በሙሉ ያቋረጠችው ሶማሊያ ከሳዑዲ አረቢያ ከቱርክ፣ ከግብፅ እና ከሌሎች ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት እያጠናከረች ትገኛለች።

    ከሳምንታት በፊት እስራኤል ከሶማሊያ በመነጠል ነጻ ሀገርነቷን ላወጀችው ሶማሊላንድ የሀገርነት እውቅና መስጠቷን ተከትሎ በአቡ ዳቢ እና ሞቃዲሹ መካከል ያለው ግንኙነት ከምን ጊዜውም በላይ ሻክሯል።

    ተንታኞች እንደሚሉት የሶማሊያ መንግሥት የሶማሊላንድን ነጻነት ከሚደግፉ ሀገራት መካከል አንዷ ዩናይትድ አረብ ኤምሬቶች ናት ብሎ ያስባል።

  18. ከ100 በላይ የዩጋንዳው ተቃዋሚ ፓርቲ አባላት የምርጫ ብጥብጥ ክስ ቀረበባቸው

    ፍርድ ቤት የቀረቡ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ከዩጋንዳ ምርጫ ብጥብጥ ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር የዋሉ ከ100 በላይ የአገሪቱ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በሕገ ወጥ መንገድ መሰብሰብ ጨምሮ የተለያዩ ክሶች ቀረቡባቸው።

    የ81 ዓመቱ ዩዌሪ ሙሴቬኒ ባለፈው ሳምንት በተካሄደው ምርጫ 71.6 በመቶ ያህሉን በማግኘት በሰፊ ብልጫ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫውን አሸንፈዋል። ተቀናቃኛቸው ቦቢ ዋይን ደግሞ 24 በመቶ ድምጽ እንዳገኘ ተገልጿል።

    የቀድሞው የሙዚቀኛ ቦቢ ዋይን እና ፓርቲው ‘ናሽናል ዩኒቲ ፕላትፎርም’ የምርጫ ውጤቱን እንደማይቀበሉት ገልጸዋል። ኮሮጆ መሙላት፣ የምርጫ ወኪሎች የግዳጅ ስወራ እና የጸጥታ ኃይሎች ጫናን ጨምሮ የምርጫ ሂደቱ ላይ ሰፊ መዛባት ነበረ ሲሉ ወንጅለዋል።

    ወደ ቤቱ ካመሩ ወታደራዊ ኃይሎች ያመለጠው ዋይን፤ እስካሁን ድረስ የት እንዳለ አልታወቀም።

    ሰኞ በ‘ኤንቲቪ ዩጋንዳ’ ቴሌቪዥን ጣቢያ በተላለፈ አንድ ቪዲዮ ላይ ፖሊስ ቤቱን እንደዘረፈ በመግለጽ ከስሷል። ቤቱን ለቅቆ መውጣቱ በነጻነት “ለዓለም እንዲናገር” እንደሚያስችለውም ገልጿል። በአሁኑ ሰዓት የት እንደሚገኝ ግን አልገለጸም።

    አገሪቱ መንግሥት በአንጻሩ የቦቢ ዋይን ፓርቲ አባላት የሆኑ ቢያንስ 118 ሰዎችን በከተማዋ ካምፓላ በሚገኙ የተለያዩ ፍርድ ቤቶች አቅርቧል። በህገ ወጥ መንገድ መሰብሰብ፣ ማሴር እንዲሁም ህገ ወጥ በሆነ መልኩ የምርጫ ቁሳ ቁሶችን በመያዝ ወንጀሎች እንደተከሰሱ የፓርቲው ጠበቃ ለሮይተርስ ተናግረዋል። የፍርድ ቤት ሰነዶችም ይህንኑ ማሳየታቸውን የዜና ወኪሉ ዘግቧል።

    የፓርቲው ዋና ፀሐፊ ዴቪድ ሩቦንጎያ በበኩላቸው ደጋፊዎቻቸው የአመጻ ድርጊት ውስጥ ተሳትፈዋል መባሉን አስተባብለዋል።

    “አብዛኛዎቹ የምርጫ ወኪሎች ናቸው፤ የፓርቲው የምርጫ ወኪል መሆናቸውን የሚያረጋግጡ ደብዳቤዎችን ጭምር ይዘዋል። ዒላማ ተደርገዋል፣ በኃይል ታስረዋል” ሲሉ ሰኞ ዕለት ኤንቲቪ ዩጋንዳ ተናግረዋል።

  19. ቻትጂፒት ማስታወቂያ ማሳየት ሊጀምር እንደሆነ አስታወቀ

    ቻትጂፒቲ የሚታይበት የሞባይል ስክሪን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ የሆነው ቻትጂፒቲ ለአንዳንድ ተጠቃሚዎች ማስታወቂያ ማሳየት ሊጀምር እንደሆነ አስታውቋል።

    የቻትጂፒቲ እናት ኩባንያ የሆነው ኦፕንኤአይ እንዳስታወቀው የመጀመሪያ ሙከራውን በአሜሪካ ባሉ በነፃ በሚጠቀሙ ሰዎች ላይ ያደርጋል።

    ቻትጂፒቲን ከፍለው የሚጠቀሙ ሰዎች ያሉ ሲሆን ዝቅተኛ ዋጋው በወር 8 ዶላር ነው።

    ኦፕንኤአይ እንዳለው ሰዎች ቻትጂፒቲን በሚጠቀሙ ጊዜ አስፈላጊ የሚባሉ ማስታወቂያዎች ይመጡላቸዋል። ለምሳሌ ሜክሲኮ ውስጥ የሚጎበኝ ቦታ ጠቁመን ብለው የሚጠይቁ ሰዎች የሽርሽር ቦታዎች ማስታወቂያ ሊያዩ ይችላሉ።

    ኩባንያው ተጠቃሚዎች ከቻትጂፒቲ ጋር የሚያወሩትን ነገር ማስታወቂያ ለሚያስነግሩ ድርጅቶች አሳልፎ እንደማይሰጥ ቃል ገብቷል።

    አክሎ ማስታወቂያ ያስፈለገው “በሚገኘው ገቢ ተጠቃሚዎቹን የበለጠ ለማገልገል” እንደሆነ ገልጿል።

    ፋይናንሻል ታይምስ በአውሮፓውያኑ 2025 የመጀመሪያው 6 ወር ብቻ ኦፕንኤአይ 8 ቢሊዮን ዶላር ከስሯል ሲል ፅፏል። ቻትጂፒቲን ከሚጠቀሙት 800 ሚሊዮን ሰዎች መካከል 5 በመቶው ብቻ ናቸው ከፍለው የሚጠቀሙት።

  20. የሶሪያ መንግሥት እና የኩርድ ኃይሎች ስምምነት በፈጸሙ ማግሥት ግጭት ውስጥ ገቡ

    የሶሪያ ባንዲራ የተለጠፈበት መኪና ላይ የተቀመጡ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እሁድ ዕለት የሰላም ስምምነት ተፈራርመው የነበሩት የሶሪያ መንግሥት እና ‘ሲሪያን ዴሞክራቲክ ፎርስስ’ የተባሉት በኩርድ የሚመሩ ታጣቂዎች በድጋሚ ግጭት ውስጥ መግባታቸው ተዘገበ።

    ከሁለት ቀናት በፊት የተፈረመው የ14 ነጥቦች የሰላም ስምምነት ለ10 ዓመት ገደማ በኩርዶች ሲመራ የነበረው ራስ ገዝ ግዛት በሶሪያ መንግሥት ቁጥጥር ስር እንዲሆን የሚያደርግ ነበር።

    የአማጺያኑ ኃይሎች ራቃ እና ዴር አል ዞህር የተባሉትን ክልሎች ለቅቀው እንደሚወጡ እና ታጣቂዎቻቸው የመንግሥት ተቋማት ውስጥ እንደሚዋሃዱም ተገልጾ ነበር። የዚህ ስምምነት መፈረም ለሁለት ሳምንታት ሲካሄድ ለነበረው ውጊያ መቋጫ እንደሚሆንም ተገምቷል።

    ሰኞ ዕለት ግን የሶሪያ መንግሥት ኃይሎች ከዚህ ቀደም በታጣቂዎቹ ቁጥጥር ስር ወደነበሩት የአገሪቱ ሰሜናዊ እና ምስራቃዊ ግዛቶች ገብተዋል።

    ከሰዓት ላይ የአገሪቱ ሠራዊት በሃሳካ ግዛት ወደምትገኘው ሻዳዲ መግባቱን አስታውቋል። ሠራዊቱ ኃይሎቹን ያሰማራው የ‘ሲሪያን ዴሞክራቲክ ፎርስስ’ ታጣቂዎች በከተማዋ እስር ቤት የነበሩ በርካታ የኢስላሚክ ስቴት (አይኤስ) አባላትን ለቅቀዋል የሚል ውንጀላ በማቅረብ እንደሆነ ‘ሳና’ የተሰኘው የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘገባ እንደሚያመልክተው፤ የሶሪያ አገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስቴር 120 ታሳሪ የአይኤስ አባላት ማምለጣቸውን ገልጿል።

    እስር ቤቱ ወደ መንግሥት የሚተላለፍበትን ሁኔታ ለማመቻቸው አደራዳሪዎችን እና አማጺያኑን ማነጋገሩን ሠራዊቱ ገልጿል። ይሁን እንጂ የኩርድ ኃይሎች አመራር ለንግግር የቀረበውን ጥያቄ “ውደቅ” ማድረጋቸውን ተናግሯል።

    የመከላከያ ሠራዊቱ ወታደሮች ደህንነትን ለማስፈን እና ከእስር ያመለጡትን ሰዎች ለመያዝ አስፈላጊውን እርምጃ እንደማይወስዱም አክሏል።

    ‘ሲሪያን ዴሞክራቲክ ፎርስስ’ በበኩሉ “ከደማስቆ ጋር ግንኙነት ባላቸው ኃይሎች” በተፈጸመበት ተደጋጋሚ ጥቃት ምክንያትሻዳዲ እስር ቤት “ከኃይሎቹ ቁጥጥር ውጪ መውደቁን” ገልጿል። “ከባድ የጸጥታ አደጋን ለመከላከል ሲሞክሩ” የነበሩ በርካታ ተዋጊዎቹ መገደላቸውንም አክሏል።