በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኘውን ኃይሏን እያጠናከረች ካለችው አሜሪካ ጋር የተፋጠጡት የኢራን የጠቅላይ መሪ አያቶላህ
አሊ ኻሜኒ፤ ዋሽንግተን ቴህራን ላይ የምትፈጽመው ማንኛውም ጥቃት ቀጣናዊ ጦርነት እንደሚያስነሳ አስጠነቀቁ።
ኻሜኒ፤ “አሜሪካውያኖቹ ጦርነት ከጀመሩ በዚህ ጊዜ [የሚነሳው] ቀጣናዊ ጦርነት እንደሚሆን ማወቅ አለባቸው"
ሲሉ መናገራቸውን ከአገሪቱ መንግሥት ጋር ግንኙት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን "ቁም ነገር ያለው ውይይት" ላይ
እንደሆነች እና ይህ ውይይት "ተቀባይነት ያለው" ውጤት ላይ እንደሚያደርስ ተስፋ ማድረጋቸውን ገልጸው ነበር።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በበኩላቸው፤ በቴህራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ላይ "ስምምነት
ላይ መድረስ እንደምንችል እርግጠኛ ነኝ" ሲሉ ለሲኤንኤን ተናግረዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራንን ኒውክሌር የማበልጸግ ፍላጎት እና ጸረ መንግሥት ተቃዋሚዎች ላይ በወሰደችው በሺህዎች የሚቆጠሩ
ሰዎች የገደለ እርምጃ ምክንያት በማድረግ ጣልቃ እንደሚገቡ ዝተዋል።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ፤ "እንደ አለመታደል ሆኖ አሜሪካን እንደ ተደራዳሪ አጋር ለማየት ያለን
እምነት አጥተናል" ብለዋል።
ሆኖም በቀጣናው ባሉ ወዳጅ አገራት በኩል የሚደረገው የመልዕክት ልውውጥ ከዋሽንግተን ጋር "ፍሬያማ"
ንግግር እንዲኖር እያመቻቸ መሆኑን አክለዋል።
የኢራን ከፍተኛ የደኅንነት ባለሥልጣን አሊ ላሪጃኒ የድርድር ማዕቀፍ የማዘጋጀት ሂደት ለውጥ እየታየበት እንደሆነ ገልጸው
ነበር።
በቀጣናው የሚገኘው ኃይሏን እያጠናከረች ያለችው አሜሪካ፤ ‘የዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን’ የተሰኘውን የአውሮፕላን
ተሸካሚ መርከብ ወደ አካባቢው ልካለች። ባለፈው ሳምንት ደግሞ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በአረቢያን ባሕር ላይ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን
አስታውቋል።
የኢራኑ ጠቅላይ መሪ ኻሜኒ፤ "[ትራምፕ] በየጊዜው መርከቦችን አመጣሁ ይላል... የኢራን ሕዝብ እነዚህን
ነገሮች አይፈራም" ብለዋል።
ኢራን ከዓለም ወሳኝ የመርከብ መተላለፊያዎች አንዱ በሆነው ሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ከእሑድ ዕለት አንስቶ ለሁለት ቀናት
የሚቆይ እና ተኩስን የሚያካትት የባሕር ኃይል ልምምድ ማድረግ እንደምትጀምር ሲጠበቅ ነበር።
ይሁን እንጂ የዜና ወኪሉ ሮይተርስ
ያነጋገራቸው አንድ የኢራን ባለሥልጣን፤ የኢራን አብዮታዊ ዘብ የባሕር ኃይል እንዲህ ዓይነት ልምምድ የማድረግ ዕቅድ እንደሌለው
መግለጻቸውን እሑድ ዕለት ዘግቧል።
የዓለም ገበያ ላይ ከሚቀርበው ነዳጅ ውስጥ አንድ አምስተኛው የሚሆነው የሚተላለፈው ኢራን በምትቆጣጠረው የሆርሙዝ
ወሽመጥ በኩል ነው። ቴህራን ከዚህ ቀደም ጥቃት የሚሰነዘርባት ከሆነ ወሽመጡን እንደምትዘጋ ዝታ ነበር።