በናይጄሪያ የአሜሪካ ጦር መሰማራቱ ሲገለጽ ታጣቂዎች ከ100 በላይ ሰዎችን ገደሉ
በናይጄሪያ ምዕራባዊ ግዛት ክዋራ ውስጥ በሁለት መንደሮች ላይ በተፈጸመ አሰቃቂ ጥቃት በርካታ ሰዎች መገደላቸውን ባለሥልጣናት እና የመብት ተሟጋቾች ተናገሩ።
አጥቂዎቹ ሱቆችንና ቤቶችን እንዲሁም የባህል መሪውን መኖሪያ ቤት አቃጥለው የኑኩ እና የዎሮ ማኅበረሰቦችን ለቅቀው እንዲወጡ ማስገደዳቸውን የአካባቢው ባለሥልጣን ሳይዱ ባባ አህመድ ለቢቢሲ ሃውሳ ተናግረዋል።
ባለሥልጣናት ለጥቃቱ አክራሪ ቡድኖችን ተጠያቂ አድርገው ወታደሮችን ወደ ኳራ ካይማ አሰማርተዋል።
ማክሰኞ ዕለት የተፈፀመው ጥቃት፣ ባለፉት ጥቂት ቀናት ውስጥ በናይጄሪያ ከተከሰቱት በርካታ ጥቃቶች መካከል አንዱ ነው።
የአገሪቱ የመከላከያ ሚኒስትር ለቢቢሲ እንዳረጋገጡት፣ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው የአሜሪካ ወታደሮች ቡድን በስለላ እና በስልጠና ለመርዳት ወደ ናይጄሪያ ገብተዋል።
የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ቦላ ቲኑቢ ለጥቃቱ የጂሃዲስት ቡድኑን ቦኮ ሃራምን ተጠያቂ አድርገዋል። የአካባቢው ሕግ አውጪ መሐመድ ኦማር ባዮ በበኩላቸው ለጥቃቱ ከኢስላሚክ ስቴት ጋር ግንኙነት ያለው የታጠቀ ቡድን፣ ላኩራዋ ተጠያቂ ነው ብለዋል።
የክዋራ ግዛት አስተዳዳሪ አብዱልራህማን አብዱልራዛቅ 75 ሰዎች "በጭካኔ ተገድለዋል" ብለዋል።
አህመድ መጀመሪያ ላይ ለቢቢሲ ሃውሳ ቢያንስ 35 ሰዎች መገደላቸውን የተናገሩ ቢሆንም ነገር ግን የሰብአዊ መብት ተሟጋች የሟቾች ቁጥር አራት እጥፍ እንደሚበልጥ ተናግረዋል።
በክዋራ የሚገኙ የቀይ መስቀል ኃላፊ የሆኑት ባባኦሞ አዮዴጂ ለኤኤፍፒ እንደተናገሩት "ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት የሟቾች ቁጥር አሁን 162 ደርሷል፤ ተጨማሪ አስከሬኖችን ለማግኘት የሚደረገው ፍለጋ ቀጥሏል" ብለዋል።
አምነስቲ ኢንተርናሽናል በበኩሉ ከ170 ሰዎች በላይ መገደላቸውን ገልጾ አብዛኞቹ የሞቱት ከቅርብ በተተኮሰባቸው ጥይት መሆኑን አስታውቋል።