በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 4 ሺህ ተጠጋ

በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር አስር እጥፍ ጭማሬ እያሳየ ባለበት በዚህ ወር በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርም ወደ አራት ሺህ ተጠግቷል። በዛሬው ዕለት 195 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን ተከትሎም ቁጥሩንም 3ሺህ 954 አድርሶታል። በዛሬው ዕለትም ሁለት በህክምና ማዕከል የነበሩ ሰዎች ህይወት ማለፉንም የጤና ሚኒስትርና የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዕለታዊ መግለጫ አስታውቋል።ሃገሪቱ በቫይረሱ ያጣቻቸው ዜጎች ቁጥርም 65 ደርሷል።በትናንትናው ዕለትም 85 ሰዎች ያገገሙ ሲሆን በአጠቃላይ በሃገሪቱ ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ቁጥርም 934 ደርሷል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በፔሩ በኮሮናቫይረስ የተጠቁት ሰዎች ቁጥር ከጣሊያን በለጠ

    Peru

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    በአሁኑ ወቅት የላቲን አሜሪካ አገራት የኮሮናቫይስ ማዕከል ሆነዋል። ብራዚል እና ፔሩ ደግሞ ቫይረሱ ጠንካራ ክንዱን ያሳረፈባቸው አገራት ናቸው።

    በፔሩ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 240 ሺህ 908 ሆኗል። ይህም አሃዝ በቫይረሱ ተጠቂዎች ብዛት ፔሩን ከጣሊያን በላይ አድርጓታል። የሟቾች ቁጥር ደግሞ 7ሺህ 257 መሆኑ ተጠቁሟል።

    በብራዚል ግን በቫይረሱ የተያዙ እና የሞሩ ሰዎች ቁጥር ከፔሩ በብዙ እጥፍ ይበልጣል። የተጠቂዎች ቁጥር ወደ አንድ ሚሊዮን የተቃረበ ሲሆን በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች ደግሞ ከ45 ሺህ በላይ ነው።

    ፔሩ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት የእቅስቃሴ ገደብ ጥላለች።

  2. በርካታ ናይጄሪያውያን በአንድ ቦታ ታጨቀው ፕሪሚየር ሊጉን ሲመለከቱ ነበር

    Man City vs Arsenal

    የፎቶው ባለመብት, POOL

    ለወራት በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሰበብ ተቋርጦ የነበረው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ትናንት ምሽት ተጀምሯል። ቢሆንም አሁንም ባለው የበሽታው ስጋት ምክንያት የመጀመሪያው ጨዋታ ያለ ተመልካች በዝግ ስታዲየም ተደርጓል።

    ቀሪ ውድድሮችም በተመሳሳይ ደጋፊዎች በማይገኙባቸው ጭር ባሉ በዝግ ስታዲየም መደረጋቸውን ይቀጥላሉ።

    በአፍሪካ ያሉ ተመልካቾች ግን በአንድ ላይ ተሰባስበው ከመመልከት ያገዳቸው የለም።

    ትናንት ምሽት ማንችስተር ሲቲ እና አርሰናል ያደረጉትን ጨዋታ በመቶዎች የሚቆጠሩ ናይጄሪያዊያን ተጠጋግተውን እና በአንድ ቦታ ላይ ታጭቀው ጨዋታውን ሲመለከቱ ተስተውለዋል።

    ኳስ እና ሲኒማ የሚያሳዩ ንግድ ቤቶች በቫይረሱ ስጋት እንዲዘጉ ቢደረጉም፤ እግር ኳስ አፍቃሪ ናይረጄሪያውያን ግን ወደ ሆቴል ሄዶ በአንድ ላይ ተሰባስቦ ከመመልከት ያገዳቸው የለም።

    ኮሮናቫይረስ በናይጄሪያ በስፋት መሰራጨቱን እንደቀጠለ ነው። ትናንት ብቻ በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ 490 ተጨማሪ ሰዎች ተገኝተዋል።

    እስካሁን በአገሪቱ ከ17 ሺህ በላይ በቫይረሱ የተጠቁ ሰዎች የተገኙ ሲሆን 455 ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

    ኳስ የሚመለከቱ ናይጄሪያውያን
  3. ካንታስ እስከ ጥቅምት ያሉ በርካታ ዓለም አቀፍ በረራዎችን ሰረዘ

    Qantas

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአውስትራሊያው ካንታስ አየር መንገድ ወደ ኒው ዚላንድ ከሚደረጉ በረራዎች ውጪ እስከ ጥቅምት ወር ድረስ ያሉትን ዓለም አቀፍ በረራዎቹን ሰረዘ።

    ይህ የተሰማው የአውስትራሊያ መንግሥት ይህ የፈረንጆቹ ዓመት እስኪጠናቀቅ ድረስ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት የአውስትራሊያ ድንበር ለዓለም አቀፍ ተጓዦች ዝግ ሆኖ እንደሚቀጥል ማስታወቁን ተከትሎ ነው።

    የአየር መንገዱ እህት ኩባንያ የሆነው ጄትስታር በአገሪቱ ተጥሎ የነበረው የእንቅስቃሴ ገደብ እየላላ መምጣቱን ተከትሎ የአገር ውስጥ በረራን አጠናክሮ ለመቀጠል በዝግጅት ላይ ይገኛል።

    ካንታስ በዚህ ሳምንት የአገር ውስጥ በረራ በእጥፍ እድገት አሳይቷል ብሏል። ባለፍነው ሳምንት 32 ሺህ ተጓዞችን ከአንድ የአውስትራሊያ ጫፍ ወደ ሌላ አጓጉዟል። በዚህ ሳምንት ደግሞ የተጓዞች ቁጥር 64 ሺህን ተሻግሯል ብሏል አየር መንገዱ።

  4. 'ዴክሳሜታሶን' እንዴት ያለ መድሃኒት ነው? በኢትዮጵያስ በስፋት ይገኛል?

    ዴክሳሜታሶን

    የፎቶው ባለመብት, NURPHOTO

    በአሁኑ ጊዜ ዴክሳሜታሶን የሁሉን ቀልብ የገዛ መድኃት ሆኗል። ምክንያቱ ደግሞ የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች በኮቪድ-19 ተይዘው በጽኑ የታመሙ ሰዎችን ለማከም ሊውል ይችላል ማለታቸውን ተከትሎ ነው።

    'ዴክሳሜታሶን' እንዴት ያለ መድኃኒት ነው? በበአገራችንስ ይገኛል? ሊያስከትል የሚችለው የጎንዮሽ ችግርስ አለ?

    ለእነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ይዘናል።

  5. ዚምባብዌ ለመንግሥት ሠራተኞች 50 በመቶ ደመወዝ ጭማሪ ልታደርግ ነው

    Zimbabwe

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ዚምባብዌ በግሽበቱ ምክንያት ለሁሉም የመንግሥት ሠራተኛ 50 በመቶ ደመወዝ ጭማሪ ልታደርግ ነው።

    ወትሮም ቢሆን በከፍተኛ ግሽበት ችግር ውስጥ የነበረው የዜምባብዌ የምጣኔ ሀብት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እያንከባለለው ይገኛል።

    የዚምባብዌ የገንዘብ ሚኒስትር በአስቸኳይ ደመወዝ ለሁሉም ሰው እንጨምራለን ብለዋል። ጭማሪውም 50 በመቶ እንደሆነ ተነግሯል።

    ይህ ጭማሪ ጡረተኞችንም የሚመለከት ነው። የደመወዝ ጭማሪው ባለፈው ዓመት ለሕዝብ በተዋወቀው የአገሬው ገንዘብ ኖት ይሆናል።

    ዚምባብዌ የራሷን የመገበያያ ገንዘብ እየተወች በሌሎች አገሮች መገበያያ ገንዘብ መገበያየትን ለምዳለች። ከዚህ የደመወዝ ጭማሪ ሌላ ለሁሉም የመንግሥት ሠራተኞች "የኮቪድ ማገገሚያ ጉርሻ" በሚል 75 ዶላር በወር እንዲከፈላቸው ተወስኗል። ጡረተኞችም በወረርሽኙ ምክንያት በወር 30 ዶላር ያገኛሉ።

    ይህ ድጎማ ከሰኔ ጀምሮ ለ3 ወራት ተግባራዊ ይሆናል።

    የዚምባብዌ ገንዘብ የግሽበት መጠን ገደቡን ጥሶ 785 % ሆኗል።

  6. በጀርመን በመቶዎች የሚቆጠሩ የሥጋ ማቀነባበሪያ ሠራተኞች በቫይረሱ መያዛቸው ተነገረ

    ጀርመን ሥጋ ማቀነባባሪያ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    በመቶዎች የሚቆጠሩ ጀርመናውያን የቄራ ሠራተኞች በቫይረሱ መያዛቸውን ተከትሎ በሺዎቹ የሚቆጠሩ ሰዎች ወደ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ መደረጉ ተነገረ።

    በሰሜን-ምዕራብ በሚገኘው የጀርመን ግዛት ውስጥ በሥጋ ማቀነባበሪያ ውስጥ የሚሰሩ 650 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    በማቀነባበሪያው የሚሰሩ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሠራተኞች ላይ ምርመራ ገና አልተካሄደም። በዚህም በቫይረሱ መያዛቸው የሚረጋገጡ ሰዎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተሰግቷል።

    በዚህም የአካባቢው ባለስልጣናት ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ የህጻናት ማዕከላትን ዝግ አድርገዋል።

    ምንም እንኳ ጀመርን ከአውሮፓ ሕብረት አገራት ከፍተኛው የሕዝብ ቁጥር ቢኖራትም በቫይረሱ ሳቢያ በሞት የተነጠቀቻቸው ሰዎች ቁጥር ከ9 ሺህ በታች ነው።

  7. ሐሙስ የሰኔ 11/2012 ዓ.ም የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ

    ኤርታሌ አፋር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቀጥታ ዘገባችን ገጽ ተጀምሯል። ከአገር ውስጥ እና ከመላው ዓለም የተሰባሰቡ በኮሮናቫይረስ ዙሪያ የሚገኙ መረጃዎችን እናቀርባለን።

    አብራችሁን ሁኑ።

    መልካም ቀን!

    ምስል፡ በምድራችን ላይ ከሚገኙት እጅግ ሞቃታማ አካባቢዎች አንዱ የሆነውን በአፋር ክልል የሚገኘውን ኤርታሌን ያሳያል።

  8. መልካም ምሽት

    ውድ ተከታታዮቻችን የዛሬው በዚሁ ቋጨን።

    ነገ ጠዋት በቀጥታ ዘገባችን እንመለሳለን።

    መልካም ምሽት!

  9. “ዴክሳሜታሶን መውሰድ ያለባቸው በጠና የታመሙ ብቻ ናቸው” የዓለም ጤና ድርጅት

    ዴክሳሜታሶን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ዴክሳሜታሶን

    የዓለም ጤና ድርጅት ዴክሳሜታሶን መውሰድ ያለባቸው በጠና የታመሙ ሰዎች፣ በሀኪም ትዕዛዝ ብቻ ነው ሲል ዛሬ ማስጠንቀቂያ ሰጠ።

    በስፋትና በርካሽ የሚገኘው ዴክሳሜታሶን በኮቪድ-19 በጠና የታመሙ ሰዎችን ሕይወት እንደሚታደግ ትላንት ይፋ መደረጉ ይታወሳል

    የዓለም ጤና ድርጅት እንዳለው፤ መድኃኒቱ በሽታውን ስለመከላከሉ እንዲሁም የበሽታውን መጠነኛ ምልክት በሚያሳዩ ሰዎች ላይ ስለመሥራቱ ማስረጃ የለም።

    የድርጅቱ የድንገተኛ ክፍል ኃላፊ ማይክ ራየን፤ “መድኃኒቱ በጠና ለታመሙ ሰዎች መሰጠት እንዳለበት ሊታወቅ ይገባል” ብለዋል።

    አንዳንድ የጤና ባለሙያዎች፤ የመድኃኒቱን የጎንዮሽ ጉዳት በማጣቀስ፤ ስለ ውጤታማነቱ የበለጠ መረጃ እንፈልጋለን እያሉ ነው።

    በዩናይትድ ኪንግደም የተደረገ ሙከራ፤ ዴክሳሜታሶን በቬንትሌተር እርዳታ ያሉ የኮቪድ-19 ታማሚዎችን የመሞት እድል በአንድ ሦስተኛ እንደሚቀንሰው ታይቷል። መድኃኒቱ ኦክስጅን የተሰጣቸውን ህሙማን የመሞት እድል በአንድ አምስተኛ መቀነሱም ተገልጿል።

  10. በፌስቡክ ገጿ ስለ ኮቪድ-19 ሐሰተኛ መረጃ ያሰራጨችው ተቀጣች

    ሐሰተኛ መረጃ የተሰራጨበት ከተማ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ሐሰተኛ መረጃ የተሰራጨበት ከተማ

    ራሺያዊቷ ኮቪድ-19 በተመለከተ በፌስቡክ ገጿ ላይ ሐሰተኛ መረጃ በማሰራጨቷ የገንዘብ ቅጣት ተላለፈባት።

    የካቴሪንበርግ ከተማ ነዋሪ የሆነችው ኖቫያ ጋዜታ በፌስቡክ ገጿ ላይ በጻፈችው ሐሰተኛ ዜና ነው በአካባቢው ፍርድ ቤት 200 ዶላር ገደማ የገንዘብ መቀጮ የተላለፈባት።

    "ሆስፒታሉ ተጨናንቋል። ሰዎች በከፍተኛ ቁጥር እየሞቱ ነው። በሁሉም ሰዎች ላይ የሳምባ ምች እየተገኘ ነው" በማለት ነበር በፌስቡክ ገጿ ላይ የጻፈችው።

    ፍርድ ቤቱ ግን ኖቫያ ጋዜታ የጻፈችው ሐሰትኛ ዜና ስለመሆኑ በማረገገጡ ነው ቅጣቱን ያስተላለፈባት።

    ሩሲያ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ይገኙባታል። ከ7ሺህ በላይ ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸውን አጥተዋል።

  11. በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው ፕሪሚየር ሊግ ተጀምሯል

    አስቶን ቪላ እና ሼፊልድ ዩናይትድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አስቶን ቪላ እና ሼፊልድ ዩናይትድ እያደረጉ ባሉት ጨዋታ ከደቂቃዎች በፊት ተጀምሯል።

    በጨወታው ጅማሬ ላይ የሁለቱ ክለብ ተጫዋጮች እና ዳኞች የ “ብላክ ላይቭስ ማተር” እንቅስቃሴን በመደገፍ ተንበርክከው ታይተዋል።

    በመለያ ልብሶች ላይም በተጫዋቾች ስም ፈንታ “ብላክ ላይቭስ ማተር” የሚል ጽሑፍ ታትሟል።

    ጨዋታው ከተጀመረ 20 ደቂቃዎች ያለፉ ሲሆን እስካሁን ጎል አልተቆጠረም።

  12. ሊቢያ የሰዓት እላፊዋን በአስር ቀናት አራዘመች

    የተባበሩት መንግሥታት እውቅና የሰጠው የሊቢያ መንግሥት በሚቆጣጠራቸው ቦታዎች የሰዓት እላፊ ገደብን ለአስር ቀን አራዝሟል።

    መቀመጫው ትሪፖሊ የሆነው የሊቢያ መንግሥት እንዳለው፤ ከምሽት 2 ሰዓት እስከ ንጋት 12 ሰዓት መንቀሳቀስ አይቻልም። አርብና ቅዳሜ ደግሞ የ24 ሰዓት ገደብ ተጥሏል።

    በምሥራቅ ሊቢያ ያለው ተቀናቃኝ አመራር በቤንጋዚ ተመሳሳይ የሰዓት እላፊ ገደብ ጥሏል።

    ኦፌሴላዊ አሃዝ ወደ 500 ሰዎች በበሽታው መያዛቸውንና አስር ሰዎች መሞታቸውን ይጠቁማል። ትክክለኛ ቁጥሩ ከዚህም በላይ ሊሆን ይችላል።

    ትሪፖሊ

    የፎቶው ባለመብት, af

  13. የቫይረሱ ስርጭት በቀነሰባት ከተማ ምክትል ከንቲባው በኮቪድ-19 ተያዙ

    ፕሬግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬግ

    የቼክ ሪፐብሊክ መዲና የሆነችው የፕሬግ ምክትል ከንቲባ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተነገረ።

    የቫይረሱ ስርጭት በአውሮፓ አገራት እየቀነሰ መምጣቱ ይታወቃል።

    የከተማዋ ምክር ቤት አባላት በኢንተርኔት አማካኝነት ስብሰባ ሲያካሂዱ ቢቆዩም በቅርቡ በአካል ለመገናኘት በድምጽ ብልጫ ተወስኖ በአንድ አዳራሽ ተገናኝተዋል።

    ምክትል ከንቲባው በቫይረሱ መያዛቸው መረጋገጡን ተከትሎ 11 የፕሬግ ከተማ ምክር ቤት አባላት ወደ ለይቶ ማቆያ ለመግባት ተገደዋል።

    ከእነዚህም በተጨማሪ በርካታ የምክር ቤቱ አባላት እና ሠራተኞች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ይደረግላቸዋል ተብሏል።

    ቼክ ሪፐብሊክ እስካሁን በቫይረሱ የተያዙ 10ሺህ 112 ሰዎችን ሪፖርት ያደረገች ሲሆን 332 ሞቶችን መዝግባለች።

  14. “ወጣቶች ለበሽታው ሥርጭት ምክንያት ሆነዋል”

    ቴክሳስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቴክሳስ አገረ ገዢ ግሬግ አቦት፤ ባርና ሬስቶራንት የሚሄዱ ወጣቶች በሽታው እንደ አዲስ እንዲሰራጭ ምክንያት ሆነዋል ሲሉ ወቀሱ።

    “ሰኔ ከገባ ጀምሮ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ከ30 ዓመት በታች ናቸው” ብለዋል።

    ቴክሳስ በአንድ ቀን በሽታው የተያዙ ሰዎች ከፍተኛውን ቁጥር አስመዝግባለች።

    ባርና ሬስቶራንቶች በ75 በመቶ ሥራ እንዲጀምሩ የተወሰነው ባለፈው አርብ ነበር። ሌሎች የንግድ አይነቶች የተከፈቱት 50 በመቶ ብቻ ነው።

    በቴክሳስ የሚገኙ ዘጠኝ ከተሞች ከንቲባዎች፤ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ግዴታ ይሁን ሲሉ ለአገረ ገዢው ደብዳቤ ጽፈዋል።

  15. በቤጂንግ በቅርብ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች የተለየ ምልክት አሳይተዋል ተባለ

    ቤጂንግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በቤጂንግ በቅርቡ በበሽታው የተያዙ ሰዎችን የሚያክሙ ባለሙያዎች፤ ህሙማኑ ለየት ያለ ምልክት እየሳዩ መሆኑን ገለጹ።

    የጤና ባለሙያዎቹ እንዳሉት፤ ህሙማኑ የመገጣጠሚያ እና የሆድ ህመም አሳይተዋል።

    ግሎባል ታይምስ የተባለው ጋዜጣ እንደዘገበው፤ በተለያየ የአየር ሁኔታ፣ የአኗኗር ዘዬ ውስጥ ያሉ እንዲሁም የተለያየ የደም አይነት ያላቸው ሰዎች የሚያሳዩት ምልክት የተለያየ መሆኑን አስተውለዋል።

    ከዚህ ቀደምም በቻይና ሰሜን ምዕራብ አካባቢ የሚሠሩ ባለሙያዎች ለየት ያለ ምልክት ማየታቸውን ተናግረው ነበር። ህሙማን ትኩሳትና የማያቋርጥ ሳል ሳያሳዩ ይደክማቸው፣ ጉሮሯቸውን ይከረክራቸው ነበር።

    በቻይና መዲና ቤጂንግ በቅርቡ በበሽታው የተያዙ ሰዎች መኖራቸው፤ ወረርሽኙ ዳግም ሊያገረሽ ይችላል የሚል ስጋት ፈጥሯል።

    ከሰኔ 11 ጀምሮ 137 ሰዎች በኮቪድ-19 ተይዘዋል። የቻይና መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት፤ በቅርቡ በበሽታው ከተያዙ ሰዎች አብዛኞቹ ከ 30 እስከ 39 ዓመት የሆናቸው ወጣቶች ናቸው። የበሽታውን ምልክትም አያሳዩም።

  16. በፖርቹጋላዊው ከንቲባ ሕገ ወጥ ድግስ ያዘጋጁት ይከሰሱ አሉ

    ፖርቹጋል

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በፖርቹጋል፣ አልጋርቬ በምትባል ግዛት፣ ላጎስ የተባለች ከተማ ውስጥ በተካሄደ ድግስ ላይ ተገኝተው ከነበሩ ሰዎች 16ቱ ኮሮናቫይረስ ተገኝቶባቸዋል።

    የከተማው ከንቲባ ሕገ ወጥ የሆነውን ድግስ ያዘጋጁት ሰዎች ይከሰሱ ብለዋል።

    በድግሱ ላይ ከ100 በላይ ሰዎች መገኘታቸው ተዘግቧል። ከ20 ሰዎች በላይ መሰብሰብ ደግሞ ሕጉ አይፈቅድም።

    በድግሱ የተገኙና ከነሱ ጋር ንክኪ ያላቸው ወደ 100 የሚሆኑ ሰዎች ተመርምረዋል።

    የቱሪስቶች መዳረሻ በሆነችው ላጎስ ከተማ ውስጥ ያሉ ሠራተኞች ቫይረሱ ከተገኘባቸው በኋላ፤ በርካታ የንግድ ማዕከሎች ጸረ ተዋህሲ ለመርጨት ሲባል ተዘግተዋል።

    በፖርቹጋል በወረርሽኙ የተያዙ ሰዎች 37,336 ሲሆኑ 1,522 ሰዎች ሞተዋል።

  17. በኢትዮጵያ ኮቪድ-19 የተገኘባቸው ሰዎች 3759 ሲደርስ 849 ሰዎች አገግመዋል

    አሃዝ

    ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረገ 5274 የላብራቶሪ ምርመራ 129 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ተረጋገጠ።

    የጤና ሚንስትር እና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ባወጡት እለታዊ መግለጫ መሠረት፤ በአጠቃላይ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች 3759 ደርሰዋል።

    ከእነዚህ መካከል 79 ወንዶች፣ 50 ደግሞ ሴቶች ናቸው። የእድሜ ክልላቸውም ከአንድ ዓመት እስከ 70 ነው። ቫይረሱ የተገኘባቸው ሁሉም ኢትዮጵያውያን ናቸው ተብሏል።

    እስካሁን ቫይረሱ እንዳለባቸው ተረጋግጦ ህክምና ሲደረግላቸው ከነበሩ ሰዎች መካከል 111 ሰዎች ከበሽታው ሲያገግሙ፤ ሁለት በህክምና ማዕከል ውስጥ የነበሩ ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል፤ ይህም የሟቾች ቁጥርን ወደ 63 አድርሶታል።

  18. የእስራኤል ተመራማሪዎች ራሱን የሚያጸዳ ጭንብል ሠሩ

    የእስራኤል ተመራማሪዎች በሙቀት ራሱን የሚያጸዳና ከአንድ ጊዜ በላይ ጥቅም ላይ የሚውል የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል መሥራታቸውን ተናገሩ።

    ጭምብሉ የተሠራው ራሱን ከኃይል አመንጪ ጋር አገናኝቶ 70 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ እንዲሞቅ ነው። ይህም ኮሮናቫይረስን ለመግደል ያስችለዋል።

    ይህ ጽዳት በ30 ደቂቃ ውስጥ ሲከናወን ሰዎች ጭምብሉን ማድረግ የለባቸውም።

    ጥናቱን የመራው ያሂር ኢንሊ ለሮይተርስ እንደተናገረው፤ የጭንብል እጥረት ነው ለፈጠራው ያነሳሳቸው።

    ፈጠራው በአሜሪካ እንዲመዘገብም ጠይቀዋል።

  19. በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 4 ሺህ ተጠጋ

  20. በስዊድን የሟቾች ቁጥር ከአምስት ሺህ በላይ ሆነ

    በስዊድን በኮሮናቫይረስ ሳቢያ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 5,041 መድረሱን የጤናው ዘርፍ ኃላፊዎች አስታወቁ።

    ከአስር ሚሊዮን በላይ ነዋሪ ያላት ስዊድን ከጎረቤት አገሮች በላቀ በበሽታው ጉዳት ደርሶባታል።

    ጥብቅ የእንቅስቃሴ ገደብ አለመጣሏም እያወዛገበ ነው።

    ከውሳኔው ጀርባ ያለው አንደርስ ተግነል፤ ውሳኔው ብዙ ሞት ማስከተሉን አምኗል።