የብሪታንያው ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን በኮሮናቫይረስ መያዛቸውን ጽህፈት ቤታቸው አስታወቀ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀላል የሚባል ምልክት እንደታየባቸው የገለፀው መግለጫው መንግሥታዊ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ይቆያሉ ተብሏል።
የጽ/ቤታቸው ቃል አቀባይ አክለውም ራሳቸውን አግልለው እንደሚቆዩ አስታውቀዋል።
"ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምርመራ እንዲያደርጉ ከሐኪም በተሰጣቸው የግል ምክር መሰረት ነው የተመረመሩት" ሲል ከጽህፈት ቤታቸው የወጣው መግለጫ አመልክቷል።
በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግሥታቸው የኮሮናቫይረስ የፈጠረውን ቀውስ ለመቆጣጠር የሚያደርገውን ጥረት በመምራት ላይ እንደሚገኙም ተገልጿል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ጆንሰን በትዊተር ሰሌዳቸው ላይ "ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ቀለል ያሉ ምልክቶችን በማየቴ ባደረኩት ምርመራ ቫይረሱ ተገኝቶብኛል። አሁን እራሴን አግልዬ የምገኝ ቢሆንም ነገር ግን መንግሥት በሽታውን ለመዋጋት የሚያደርገውን ጥረት በቪዲዮ ኮንፈረንስ አማካይነት እየመራሁ እቀጥላለሁ።
"በጋራ ይህንን በሽታ እናሸንፈዋለን" ብለዋል።
በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ እስካሁን ከ11,600 በላይ በበሽታው መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ሲኖሩ 578 ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀደም ብሎ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የዌልሱ ልዑል ቻርለስ ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ተረጋግጧል።
በአሁኑ ወቅት የ71 ዓመቱ ልዑል ቻርልስ ቀለል ያሉ የበሽታው ምልክቶች እየታዩባቸው ቢሆንም "በጥሩ የጤንነት ሁኔታ ላይ ይገኛሉ" ሲል ቃል አቀባያቸው አሳውቋል።