የብሪታኒያው ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን የኮሮናቫይረስ መስፋፋትን ለመግታት ያስችላል ያሉትን የዜጎችን አኗኗር የሚቀይሩ
ጥብቅ እርምጃዎች ይፋ አደረጉ።
በዚህም መሰረት ሰዎች ከቤታቸው እንዳይወጡ የተከለከሉ ሲሆን፤ መውጣት የሚቻለው የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ለማድረግ በቀን
አንድ ጊዜ ብቻ፣ “የግድ አስፈላጊ” ለሆኑ ሥራዎችና ጉዞዎች፣ መሰረታዊ ነገሮችን ለመግዛትና የህክምና ክትትልና ድጋፍ ለማግኘት
ብቻ ይሆናል።
መሰረታዊ የሆኑ ነገሮችን የሚሸጡ መደብሮች እንዲዘጉ የተነገራቸው ሲሆን አብረው ከሚኖሩ ሰዎች ውጪ በሕዝብ መሰብሰቢያ ስፍራዎች
ከሁለት በላይ ሆኖ መገኘትም ተከልክሏል።
በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ እስካሁን በኮሮናቫይረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 335 ደርሷል።
ዜጎች በመንግሥት የወጣውን ግዴታ ተግባራዊ የማያደርጉ ከሆነ የመቅጣትና የተሰበሰቡ ሰዎችን የመበትን ስልጣን ፖሊስ ተሰጥቶታል
ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆንሰን ከጽህፈት ቤታቸው በቴሌቪዥን ቀርበው አስታውቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት አገራቸው “ብሔራዊ የአደጋ ጊዜ” እንደተጋረጠባትና ዜጎች ከቤት ባለመውጣት ጤናቸውንና የወገኖቻቸውን
ህይወት እንዲጠብቁ ጥሪ አቅርበዋል።
የተጣለው እገዳም በመላዋ አገሪቱ ቢያንስ ለሦስት ሳምንታት የሚቆይ ሲሆን በየጊዜውም እየታየ ክለሳ ይደረግበታል ብለዋል።
የብሪታኒያ መንግሥት እንዳስጠነቀቀው ከቤት መውጣት የሚቻልባቸው ሁኔታዎች እንደተጠበቁ ሆነው ሰዎች ከቤታቸው ውጪ በሚሆኑባቸው
ወቅት ቆይታቸውን በጣም አጭር ማድረግና ከሰዎች ጋር ያላቸው ቅርበትም ከሁለት ሜትሮች ያነሰ እንዳይሆን መጠንቀቅ እንዳለባቸው ተመክሯል።
በተጨማሪም መንግሥት ሠርግን፣ ክርስትናንና ሌሎች ማኅበራዊ ሥነ ሥርዓቶች እንዳይካሄዱ የከለከለ ሲሆን፤ የቀብር ሥነ ሥርዓቶች
ግን እንደሚፈቀዱ ገልጿል።