ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ትራምፕ የምርጫ ውጤትን ለመቀልበስ ማሴር በሚል ለቀረበባቸው ክስ ጥፋተኛ አይደለሁም አሉ
የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የ2020 ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ውጤትን ለመቀልበስ ማሴር በሚል ለቀረበባቸውን ክስ ጥፋተኛ አይደለሁም ሲሉ ለፍርድ ቤት መልስ ሰጡ።
ትራምፕ ዋሽንግተን ባለ ፍርድ ቤት ለጥቂት ደቂቃዎች በቆየው ችሎት ፊት ቀርበው ስም እና ዕድሜያቸውን እንዲሁም በምንም አይነት አደንዛዥ እጽ ተጽእኖ ስር እንዳልሆኑ እና የቀረቡባቸውን ክሶች እንዳልፈፀሙ ቃላቸውን ሰጥተዋል።
ከችሎቱ በኋላ ትራምፕ ለጋዜጠኞች ክሶቹ የቀረቡባቸው በፖለቲካ ተቀናቃኞቻቸው መሆኑን ተናግረዋል።
ትራምፕ በፍርድ ቤት ውሎ አሜሪካን ማጭበርበር፣ ምስክር ላይ ጫና ማሳደር፣ ይፋዊ የሥራ ሂደትን ለማወክ ማሴር እና በዜጎች መብት ላይ ማሴር በሚል ለቀረቡባቸው ክሶች ጥፋተኛ አይደለሁም ብለዋል።
የቀድሞ ፕሬዝዳንት ክስ ተመስርቶባቸው ፍርድ ቤት ሲቀርቡ በአራት ወራት ውስጥ ይህ ለሦስተኛ ግዜ ነው።
ከዚህ ቀደም የአገር ምስጢር የያዙ ሰነዶችን አግባብ ባልሆነ ሁኔታ ይዘዋል በሚል እንዲሁም አንዲት የልቅ ወሲብ ተዋናይን ዝም ለማሰኘት የከፈሉት ገንዘብ እንዳይታወቅ ወጪው ለንግድ ሥራ የተከፈለ አስመስለዋል የሚሉ ክሶች ቀርበውባቸው ነበር።
ትራምፕ ላይ የቀረበው ሦስተኛው ክስ የቀድሞው ፕሬዝዳንት 2020 ምርጫ ከተሸነፉ በኋላ ባሉት ሁለት ወራት ውስጥ የተከናወኑትን እንዲሁም የትራምፕ ደጋፊዎች በካፒቶል ሂል ላይ ያደረጉትን ወረራን ተመልክቷል።
በትናንቱ የፍርድ ቤት ውሎ ዳኛዋ ተከሳሹ ስለ ክስ ሂደቱ በይፋ ከመናገር እንዲቆጠቡ አሳስበዋል። ዳኛዋ ትራምፕ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ የማያከብሩ ከሆነ የእስር ማዘዣ ሊወጣባቸው እንደሚችል እና ችሎት በመዳፈር ሊከሰሱ እንደሚችሉ አስጠንቅቀዋል።
ትራምፕ እአአ 2020 ላይ የተካሄደውን ምርጫ ቢሸነፉም ምርጫው ተጭበርብሯል በማለት የፕሬዝዳንት ባይደን አሸናፊነት ሳይቀበሉ አሉ።
ሪፓብሊካኑ ትራምፕ በ2024 ላይ በሚደረገው ምርጫ ፓርቲያቸውን ወክለው እንደሚወዳደሩ ይፋ አድርገዋል።
ከፍርድ ቤቱ ውሎ በኋላ ትራምፕ ክስ ተመስርቶባቸው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ መደረጋቸው “ለአሜሪካ አሳዛኝ ቀን ነው” ብለዋል።
በዚህ ክስ ላይ ከቀድሞው ፕሬዝዳንት ጋር ያበሩ ናቸው የተባሉ በስም ያልተጠቀሱ ስድስት ግለሰቦች ተካተዋል። አራት ጠበቆች፣ አንድ የፍትሕ ቢሮ ከፍተኛ ኃላፊ እንዲሁም የፖለቲካ አማካሪ ከትራምፕ ጋር አብረዋል ተብሏል።