የአሜሪካ ሴኔት የትራምፕን ውሳኔ ማስቀልበስ ሳይችል ቀረ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የአሜሪካው የሴኔት ምክርቤት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለሳዑዲ አረቢያ 8.1 ቢሊየን ዶላር የሚያወጣ የጦር መሳሪያ ለመሸጥ ያላቸውን እቅድ ማገድ ሳይችል ቀረ።
የኮንግረስ ምክር ቤት አባላት ሽያጩን ካገዱ በኋላ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያላቸውን ስልጣን ተጠቅመው ሽያጩ እንዲከናወን መመሪያ ከሰጡ በኋላ ነው ይህ ውሳኔ የተሰማው።
ሽያጩን የሚቃወሙ ወገኖች መሳሪያዎቹ ምናልባት በየመን ባለው ግጭት ላይ ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ ሲሉ ስጋታቸውን አስቀምጠዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ግን ሽያጩን ማስቆም አሜሪካ በዓለም ላይ ያላትን ፉክክር ያዳክመዋል ሲሉ ተሟግተዋል።
ፕሬዝዳንቱ አክለውም የሽያጩ መታገድ አሜሪካ ከአጋሮቿ ጋር ያላትን ግንኙነት ያበላሻልም ብለዋል።
ነገር ግን አንዳንድ የሕግ አዋቂዎች፣ ሪፐብሊካን የሴኔት አባላትን ጨምሮ፣ የኮንግረሱን ውሳኔ የሚያስጥስ ምንም ሕጋዊ መሰረት የለም ሲሉ ተናግረዋል።
ሰኞ ዕለት በነበረው ድምፅ አሰጣጥ ላይ አምስት ሪፐብሊካን የፕሬዝዳንቱን ውሳኔ ለመቀልበስ ከዲሞክራት አቻዎቻቸው ጋር ያበሩ ሲሆን አስራ አምስት ሴናተሮች ደግሞ ድምፅ ከመስጠት ታቅበዋል። በአጠቃላይ 45-40 በሆነ ድምፅ ውሳኔያቸውን ማገድ ሳይቻል ቀርቷል።
ሌሎች ሁለት ድምፅ አሰጣጦችም ተመሳሳይ በሆነ ድምፅ ነበር ያገኙት።
የትራምፕ አስተዳደር ግንቦት ወር ላይ ለሳዑዲ ዓረቢያና ለተባበሩት የአረብ ኢሜሬትስ መሳሪያ መሸጡን እንደሚገፋበት አስታውቆ ነበር።
ሽያጩን ለመግፋትም ፕሬዝዳንት ትራምፕ ብሔራዊ አስቸኳይ ጊዜ ወስነው ነበር።
ይህንን ውሳኔ የወሰኑትም ከኢራን ለተደቀነባቸው ስጋት መሆኑን መናገራቸው ይታወሳል።
በአሜሪካና በኢራን መካከል የነገሰው ውጥረት አሜሪካ ከስምምነቱ ከወጣች በኋላ እየተካረረ ሄዷል።














