ክትባት፡ በዘጠኝ የአፍሪካ አገራት 450 ሺህ የኮሮናቫይረስ ክትባቶችን አስወገዱ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
በዘጠኝ የአፍሪካ አገራት 450,000 የኮሮናቫይረስ ክትባቶች ጥቅም ላይ ሳይውሉ መወገዳቸውን የዓለም ጤና ድርጅት አስታወቀ።
የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ የበሽታ መከላከል ፕሮግራም ኃላፊ ዶ/ር ሪቻርድ ሚሂጎ እንዳሉት፤ ወደ አፍሪካ የተላኩ የአስትራዜኒካ ክትባቶች ቶሎ አለመድረሳቸው ጥቅም ላይ ሳይውሉ ለመወገዳቸው ዋናው ምክንያት ነው።
አስትራዜኒካ በአፍሪካ በስፋት ጥቅም ላይ እየዋለ የሚገኘው ክትባት ነው።
ዶ/ር ሪቻርድ እንደሚሉት፤ ክትባቶቹ ወደ አፍሪካ ከደረሱ በኋላ ለመበላሸት የቀሯቸው ጥቂት ቀናት ብቻ ነበሩ።
"እነዚህ ክትባቶች ባክነዋል ማለት አይደለም። ወደ አፍሪካ ለመላክ አስቸጋሪ ስለነበረ እዚህ ከደረሱ በኋላ እስኪበላሹ የቀራቸው ጥቂት ቀን ነበር" ብለዋል።
ክትባቶቹን ያስወገዱት አገራት ማላዊ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ላይቤሪያ፣ ሞሪታንያ፣ ጋምቢያ፣ ሴራ ሊዮን፣ ጊኒ፣ ኮሞሮስ እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ናቸው።
ክትባት በይፋ ያስወገደችው አገር ማላዊ ስትሆን፤ የአገሪቱ የጤና ሚንስትር እንዳሉት ክትባቱ በሕዝብ ፊት እንዲወደድ የተወሰነው መተማመን ለመፍጠር ነው።
ክትባቶቹ የሚበላሹበት ቀን ደርሶ ከመጣላቸው በፊት ጥቅም ላይ ለማዋል ሲባል ወደ አገራት ከደረሱበት ቀን አንስቶ በፍጥነት ለማከፋፈል ተሞክሯል።
"ክትባቱን ያለ አሳማኝ ምክንያት ያስወገደ አገር የለም" ብለዋል ዶ/ር ሪቻርድ።
ማኅበረሰቡ ክትባት የመውሰድን ጥቅም ጠንቅቆ እንዲገነዘብ ንቅናቄዎች እንደሚያስፈልጉም አክለዋል።
1.2 ቢሊዮን ከሚሆኑ የአህጉሪቱ ነዋሪዎች መካከል አስካሁን ክትባት ያገኙት ስምንት ሚሊዮኑ ብቻ ናቸው።












