ቻይና ወደ ጨረቃ የላከችው መንኩራኩር የአፈር እና ድንጋይ ናሙና ይዞ ተመለሰ

የቻይና መንኩራኩር

የፎቶው ባለመብት, SHUTTERSTOCK

ታትሟል

ቻይና ከጨረቃ ላይ የአለትና የአፈር ናሙናዎችን እንዲያመጣ ወደ ጨረቃ ያለከችው መንኩራኩር ተልዕኮውን በስኬት ጨርሶ ወደ ምድር መመለሱ ተነገረ።

'ቻንግ ኢ-5' የሚል መጠሪያ የተሰጠው መንኩራኩር ሕዳር 24 ነበር ወደ ጨረቃ ጉዞውን ያደረገው።

ለመጨረሻ ጊዜ ሶቪየት ሕብረት ነበረች ከጨረቃ ላይ የአለት ስብርባሪ ለማምጣት መንኩራኩር ከ40 ዓመታት በፊት ወደ ጨረቃ የላከችው።

ስኬታማውን ተልዕኮ ተከትሎም ቻይና ከአሜሪካ እና ሶቪየት ሕብረት በመቀጠል ከጨረቃ ላይ የአለት ስብርባሪ ማምጣት የቻለች ሶስተኛዋ አገር መሆን ችላለች።

ቻይና ይህ ጉዞ በድል መጠናቀቁ ከሚያስገኝላት ሳይንሳዊ ጥቅም በተጨማሪ በሕዋ ሳይንስ ምርምር የደረሰችበትን ምጥቀት ለተቀረው ዓለም ለማሳየት ከፍተኛ ዕድል የሚፈጥርላት እንደሆነ ተገልጿል።

ከሕዋ የተመለሰው መንኩራኩር ምድር ሲደርስ በርካታ ባለሙያዎች ተቀብለውታል።

ወደ ጨረቃ ተልኮ የነበረው መሳሪያ ከጨረቃ ላይ የአለት ስብርባሪና የአፈር ቅንጣት ይዞ እንደሚመለስ የሚጠበቅ ሲሆን ምን ያክል ናሙና ይዞ ስለመመለሱ ግን የተባለ ነገር የለም። ነገር ግን ከ2 እስከ 4 ኪሎግራም ሊመዝን እንደሚችል ተጠቁሟል።

ወደ ጨረቃ የተላከው ቻንግ-5 የተባለው መንኩራኩር በጥንታዊ የቻይና ጨረቃ አማልክት የተሰየመ ነው።

ከጨረቃ የሚመጣው አለትና አፈር እስካሁን በሰው ልጅ ተጎብኝቶ ከማያውቅ የጨረቃ ክፍል እንደሆነም ተገልጿል።

በ1976ቱ የሶቪየት ህበረት ተልዕኮ 170 ግራም የአለት ስብርባሪ ነበር ወደ ምድር ተይዞ መመለስ የተቻለው። በአሜሪካው አፖሎ ሚሽን ደግሞ 382 ኪሎ ግራም የአለት ስብርባሪና አፈር ጭምር ለማምጣት ተችሏል።

የቻይና የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚሉት በዚህ ተልዕኮ የሚመጣው የአለት ስብርባሪ ድንጋይ ጨረቃን በተሻለ መልኩ ለመረዳትና ወደፊት የሚደረጉ ጉዞዎችን ቀላል ለማድረግ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል።

ከጨረቃ ላይ የተወሰዱት ናሙናዎች እድሜ ከሶስት ቢሊየን ዓመታት በላይ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል።