ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ለኤቨረስት ተራራ ወጪዎች አዲስ ደንብ ሊወጣ ነው
የዓለማችን ትልቁን ተራራ፤ ኤቨረስትን መውጣት የሚፈልጉ ተራራ ወጭዎች ተራራውን ከመውጣታቸው አስቀድሞ ተራራ የመውጣት ልምድ እንዳላቸው ማሳየት እንደሚጠበቅባቸው የኔፓል መንግሥት አማካሪ ቦርድ አሳሰበ።
በዚህም ኤቨረስትን ለመውጣት የሚያመለክቱ ተራራ ወጭዎች ቢያንስ 6500 ሜትር ከፍታ ያለውን የኔፓልን ተራራ መውጣት ይጠበቅባቸዋል።
ከዚህም ባሻገር የአካል ጤንነትና ብቃትን የሚያሳይ ማስረጃ ማቅረብ እና ልምድ ያለው የተራራ መሪ መቅጠርም ይኖርባቸዋል።
በያዝነው ዓመት መጀመሪያ ላይ በኤቨረስት ተራራ ላይ 11 ሰዎች ሳይሞቱ አሊያም ሳይጠፉ እንዳልቀረ ተገልጿል።
ከተፈጠሩ የሞት አደጋዎች ዘጠኙ በኔፓል በኩል ያጋጠሙ ሲሆን ሁለቱ ደግሞ በቲቤታን በኩል የተፈጠሩ ናቸው። ከእነዚህ መካከል አራቱ በተፈጠረ የመንገድ መጨናነቅ ሳቢያ እንደሞቱ ተነግሯል።
በቦርዱ ሪፖርት እንደተገለፀው ተራራውን ለመውጣት በትንሹ 35 ሺህ ዶላር እንዲከፍሉ እና ከ 8 ሺህ ሜትር ከፍታ በላይ ያላቸው ሌሎች ተራራዎችን ለመውጣት ደግሞ 20 ሺህ ዶላር እንዲከፍሉ ሃሳብ ቀርቧል።
"ሕጉንና ደንቡን እናሻሽላለን፤ በዚህም ተራራው ደህንነቱ የተሟላ፣ ክትትል የሚደረግበት እንዲሆን እናደርጋለን " ሲሉ የኔፓል ቱሪዝም ሚኒስቴር ዮገሽ ባታሪ ተናግረዋል።
ኔፓል ለ14 የዓለማችን ከፍተኛ ተራራዎች መገኛ ስትሆን የውጭ አገር ተራራ ወጭዎች ለአገሪቷ ዋነኛ የገቢ ምንጭም ናቸው።
የኔፓል ቦርድ የመንግሥት ባለሥልጣናትን፣ የተራራ ባለሙያዎችን እንዲሁም የተራራ ወጭዎችን የማህበረሰብ ኤጀንሲ የተካተቱበት ነው።
ቦርዱ የተዋቀረው ከዚህ ቀደም 11 ሺህ ዶላር መክፈል የቻለ ሁሉ ተራራውን እንዲወጣ መፈቀዱን በተመለከተ ከአንዳንድ ልምድ ያላቸው ተራራ ወጭዎች ትችት በመቅረቡ ነው።
የኔፓል መንግሥት በዚህ ወቅት ብቻ ለ381 ተራራ ወጭዎች ፈቃድ ሰጥቷል።