የሶሪያ ሃኪሞች በኮቪድ-19 ቁስ እጥረት ህይወታቸው እያለፈ ነው ተባለ
ሂዩማን ራይትስ ዎች የተሰኘው የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ድርጅት በሶሪያ መንግሥት ይዞታ ስር በሚገኙ አከባቢዎች የሚያገለግሉ የጤና ባለሙያዎች በኮቪድ-19 በሽታ መከላከያ አቅርቦት እጥረት ለበሽታው እየተጋለጡ መሆኑን አስታወቀ።
ሂዩማን ራይትስ ዎች ጨምሮ እንዳለው በበሽታው ምክንያት ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ የጤና ባለሙያዎች ህይወታቸው አልፏል።
ድርጅቱ ያነጋገራቸው የጤና ባለሙያዎች እንዳሉት ከሆነ የሆስፒታል አልጋዎች በኮቪድ-19 በተያዙ ታማሚዎች ተጨናንቀዋል።
የሶሪያ መንግሥት በአገሪቱ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 2800፣ በበሽታው የሞቱ ሰዎች አሃዝ ደግሞ 116 ነው ይላል።
ሂዩማን ራይትስ ዎች ግን በሶሪያ በቫይረሱ የተያዙ እና የሞቱ ሰዎች ቁጥር መንግሥት ከሚለው በብዙ እጥፍ እንደሚበልጥ ይናገራል።
ድርጅቱ ባለፉት 4 ወራት ብቻ 33 ዶክተሮች የኮቪድ-19 ምልክት ባለው ሕመም ህይወታቸው አልፏል ብሏል።