በኢትዮጵያ የተደረገው የላብራቶሪ ምርመራ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሆነ

በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ የማህበረሰብ ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ሲሆን በቫይረሱም የተያዙም ሰዎች ከ57 ሺህ በልጧል። በትናንትናው ዕለት ለ24 ሺህ 544 ሰዎች በተደረገው ምርመራ 950 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል። በዚህም መሰረት በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 57 ሺህ 466 ደርሷል። ከነዚህም ውስጥ 20 ሺህ 776 ያገገሙ ሲሆን 897ቱ ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል። አገሪቷ በአጠቃላይ ያከናወነችው ላብራቶሪም ከአንድ ሚሊዮን በልጧል። የቫይረሱን ስርጭት አካሄድ የሚከታተሉ ባለሙያዎች እንደሚሉት የወረርሽኙ ስርጭት ከመረጋጋት ይልቅ እየጨመረ በመሆኑ፣ አሁንም ጥንቃቄ መልዕክቶቹ በአግባቡ ተግባራዊ መሆን አለባቸው። አካላዊ ርቀትን መጠበቅ፣ አፍና አፍንጫን መሸፈን እንዲሁም እጅን በሚገባ በሳሙናና በውሃ መታጠብ ከጥንቃቄ መልዕክቶቹ መካከል ይገኙበታል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኢትዮጵያ በአንድ ቀን 24 ሰዎች በኮቪድ-19 ሳቢያ ሞቱ

    ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረገ 23 ሺህ 712 የናሙና ምርመራ፤ 1303 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ተረጋገጠ።

    የጤና ሚንስትር እና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ባወጡት ዕለታዊ መግለጫ እንደተመለከተው፤ በአንድ ቀን 24 ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል።

    ባጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 56 ሺህ 516 የደረሰ ሲሆን፤ 880 ሰዎች ደግሞ ሞተዋል።

    ባለፉት 24 ሰዓታት 329 ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል። ይህም በቫይረሱ ያገገሙ ሰዎችን ቁጥር 20 ሺህ 612 አድርሶታል።

    እስካሁን 994 ሺህ 303 የናሙና ምርመራ ተደርጓል።

  2. በሩስያ የክትባት ሙከራ ህሙማን ‘አንቲቦዲስ’ ማምረት መቻላቸው ተገለጸ

    በሩስያ የመጀመሪያ ዙር የክትባት ሙከራ የተሳተፉ ህሙማን አንቲቦዲስ (ጸረ እንግዳ አካላት) ማምረት እንደቻሉ ተገለጸ።

    ህሙማኑ የጎላ የጎንዮሽ ጉዳት እንዳልገጠማቸው ላንሴንት የተባለው የጤና መጽሔት የሩስያ ሳይንቲስቶችን ጠቅሶ ዘግቧል።

    ተመራማሪዎች እንደሚሉት፤ ስፑቲክ ቪ ክትባት አስተማማኝ መሆኑ እንዲረጋገጥ ሰፊና ዘለግ ያለ ምርምር ያስፈልጋል።

    አንዳንድ አገሮች ጥርጣሬ ቢያሳዩም፤ ባለፈው ወር ክትባቱ በሩስያ የጤና ተቆጣጣሪ አካል ይሁንታ እንዳገኘ መገለጹ ይታወሳል።

    በተለይ የምዕራቡ ዓለም ባለሙያዎች፤ ሩስያ ቁልፍ የምርምር ደረጃዎችን አልፋ ለክትባቱ ፍቃድ እንደሰጠች ሲናገሩ ተደምጠዋል።

    ሩስያ ትችቶቹን መሠረተ ቢስ ብላቸዋለች።

    ፕሬዘዳንት ቭላድሚር ፑቲን ልጃቸው ክትባቱን እየወሰደች እንደምትገኝ ይፋ አድርገዋል።

    ባለፈው አርብ ደግሞ የመከላከያ ሚንስትሩ ሰርጌ ሺጉ ክትባቱ ሲሰጣቸው በብሔራዊ ቴሌቭዥን ታይቷል።

  3. የጋምቤላ ዕለታዊ የኮቪድ-19 ሪፖርት ለምን ተቋረጠ?

  4. ናይጄሪያ ዓሥር አየር መንገዶች ወደ አገሯ እንዳይገቡ አገደች

    በናይጄሪያ ዓለም አቀፍ በረራ ቢጀመርም፤ ዓሥር አየር መንገዶች ላይ እገዳ ተጥሏል።

    ኤር ፍራንስ (ፈረንሳይ)፣ ኬኤልኤም (ኔዘርላንድስ)፣ ሉፍታንዛ (ጀርመን)፣ ኢቲሀድ (ዩኤኢ) ከታገዱት አየር መንገዶች መካከል ናቸው።

    የቱሪስት ቪዛ ያላቸው ናይጄሪያውያን ከላይ ወደተጠቀሱት አገሮች እንዳይገቡ ስለተከለከሉ፤ ናይጄሪያ አየር መንገዶቹን አግዳለች።

    በሌላ በኩል የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ብሪትሽ ኤርዌይስ፣ ቨርጅን አትላንቲክ፣ ተርኪሽ ኤርላየንስ እና ካታር ኤርዌይስ ወደ ናይጄሪያ በረራ እንዲያደርጉ ከተፈቀደላቸው 14 አየር መንገዶች መካከል ይገኙበታል።

    በናይጄሪያ 54,000 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ፤ከ1,000 በላይ ሰዎች ሞተዋል።

  5. ኮሮናቫይረስን ለማከም ምን ያህል ተቃርበናል?

  6. የቀድሞው የጣልያን ጠቅላይ ሚኒስትር በርሎስኮኒ ሆስፒታል ገቡ

  7. በኦሮሚያና በአፋር ክልሎች በአዋሽ ወንዝ ሙላት የተነሳ 92 ሺህ ያህል ሰዎች መፈናቀላቸው ተገለፀ

  8. አፍሪካ 220 ሚሊየን የክትባት ብልቃጦችን ልታገኝ ትችላለች

    የኮቪድ-19 ክትባቶች ፈቃድ አግኝተው የሚመረቱ ከሆነ አፍሪካ ቢያንስ 220 ሚሊየን የመጀመሪያ ዙር የክትባት ብልቃጦችን እንደምታገኝ የዓለም ጤና ድርጅት አስተውቋል።

    የመጀመሪያ ዙር ክትባቱ የጤና ባለሙያዎችን እና ተጋላጭ የማህበረሰብ ክፍሎች ላይ ትኩረት የሚያደርግ እንደሆነ የድርጅቱ የአፍሪካ ፕሮግራም የክልል ኃላፊ የሆኑት ሪቻርድ ሚሂጎ ተናግረዋል።

    አክለውም ''እደላው የሚከናወነው የየአገራቱን የህዝብ ብዛት መሰረት በማድረግ ነው'' ብለዋል።

    ኃላፊው እንደገለጹት 54 የአፍሪካ አገራት ክትባቱ ሲገኝ መጠቀም እንደሚፈልጉ ፍላጎት አሳይተዋል። አፍሪካ በአጠቃላይ ከ1.3 ቢሊየን በላይ ሰዎች ይገኛሉ።

    'ኮቫክስ' የተባለው ዓለማቀፍ የክትባት ጥምረት እንዳስታወቀው በሚቀጥው የፈረንጆቹ ዓመት 2 ቢሊየን የክትባት ብልቃጦችን ፍትሀዊ በሆነ መልኩ በመላው ዓለም የማሰራጨት እቅድ እንዳለው አስታውቋል።

    ጥምረቱም አስካሁን ተስፋ ሰጪ ያላቸውን ዘጠኝ የክትባት አይነቶች መለየቱ ተገልጿል።

    ከነዚህ መካከል ደግሞ ሁለቱ በሰዎች ላይ እየተሞከሩ የሚገኙት አፍሪካ ውስጥ ነው።

  9. ኒውዚላንድ በኮሮናቫይረስ የመጀመሪያ ሞት መዘገበች

    የኮሮናቫይረስ ስርጭት በግንቦት ወር ተገትቷል በተባለባት ኒውዚላንድ በዛሬው ዕለት የመጀመሪያ ሞቷን መዝግባለች።

    በአምሳዎቹ እድሜ ይገኛል የተባለው ግለሰብ በኦክላንድ ሆስፒታል በፅኑ ህሙማን ማቆያ ለቀናት ሲረዳ ቆይቶ በዛሬው እለት ህይወቱ ማለፉን የአገሪቱ የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    የኒውዚላንድ ትልቋ ከተማ ኦክላንድ በቅርብ ሳምንታት ውስጥ የወረርሽኙ ማዕከል መሆኗ የተገለፀ ሲሆን 100 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጦ ነበር። በዛሬው ዕለትም አምስት ሰዎች በቫይረሱ ተይዘዋል።

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት ፈጣን እርምጃ በመውሰዷ በአለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ ምስጋና የተቸራት ኒወዚላንድ ለመቶ ቀናት ያህልም ያለምንም የማህበረሰብ ስርጭት ቆይታ ነበር። በአሁኑ ሰዓትም አዲሱን ዙር ወረርሽኝ ለመቆጣጠር መመሪያዎቹ እንደገና እንዲጠብቁ ተደርገዋል።

  10. የቅዱስ ጴጥሮስ ሆስፒታል ነርስ በኮሮናቫይረስ ህይወታቸው አለፈ

    በቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በነርስነት እያገለገሉ የነበሩት አንበሳአውድም ዮሃንስ በትናንትናው ዕለት በኮሮናቫይረስ ህይወታቸው ማለፉን ሆስፒታሉ አስታውቋል።

    ነርስ አንበሳአውድም የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሞያቸው ህዝቡን በማገልገል ላይ እያሉ በኮሮናቫይረስ መያዛቸውንም ከሆስፒታሉ ፌስቡክ ገፅ መረዳት ተችሏል።

    ነርሱ የህክምና እርዳታ ሲደረግላቸው ከቆዩ በኋላም በትናንትናው ዕለት ህይወታቸው ማለፉ ተገልጿል።

  11. በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ከ55 ሺህ በላይ ሆነ

    ባለፉት 24 ሰዓታት ለ 20 ሺህ 778 ሰዎች በተደረገው ምርመራ 804 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተረጋግጧል።

    በዚህም መሰረት በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 55 ሺህ 213 አድርሶታል።

    የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ በሚያወጡት ዕለታዊ መግለጫ መሰረት 10 ሰዎች በዛሬው ዕለት መሞታቸው ተገልጿል። አገሪቱ በኮሮናቫይረስ ያጣቻቸው ዜጎች ቁጥርም 856 ሆኗል።

    ከዚህም በተጨማሪ 380 ሰዎች ማገገማቸው የተገለፀ ሲሆን ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 20 ሺህ 283 ደርሷል።

    ኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ያከናወነቻቸው የላብራቶሪ ምርመራዎችም 970 ሺህ 591 ሆኗል።

  12. በኮቪድ-19 ምክንያት 7000 የጤና ባለሙያዎችን ዓለም አጥታለች- አምነስቲ

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ቢያንስ እስከ 7 ሺህ የሚደርሱ የጤና ባለሙያዎች በመላው ዓለም መሞታቸውን አለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አምነስቲ አስታወቀ።

    ከፍተኛው ሞት የተመዘገበው ደግሞ በሜክሲኮ እንደሆነ ድርጅቱ ገልጿል።

    ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ድርጅት እንደገለጸው በሜክሲኮ ብቻ ቢያንስ 1 ሺህ 320 የሚሆኑ የጤና ባለሙያዎች ሕይወታቸውን ሲያጡ በአሜሪካ ደግሞ 1 ሺህ77 የጤና ባለሙያዎች፣በዩኬ 649 እንዲሁም 634 ደግሞ በብራዚል ሞተዋል።

    ''በደቡብ አፍሪካ ደግሞ በአሳሳቢ ሁኔታ የሚሞቱ የጤና ባለሙያዎች ቁጥር እየጨመረ ነው'' ያለው አምነስቲ እስካሁን 240 የጤና ባለሙያዎች በአገሪቱ መሞታቸውን ጠቅሷል።

    ሕንድ ደግሞ 573 የጤና ባለሙያዎቿን አጥታለች።

    '' የዓለምን ህዝብ ለማዳን ስራቸውን ሲሰሩ 7 ሺህ የጤና ባለሙያዎች መሞት ማለት በጣም ትልቅ ነገር ነው። ሁሉም የጤና ባለሙያዎች ስራ ቦታቸው ደህንነት እንዲጠበቅላቸው ግዴታ ነው'' ብለዋል የድርጅቱ የማህበራዊ ፍትህ ኃላፊው ስቲቭ ኮክበርን።

  13. ትልልቆቹ መድሀኒት አምራቾች በቅርቡ የክትባት ሙከራ ሊጀምሩ ነው

    ትልልቆቹ 'ጂኤስኬ' እና 'ሳኖፊ' የተባሉት መድሀኒት አምራች ግዙፍ ኩባንያዎች በሚቀጥሉት ሳምንታት ውስጥ ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የሚሆን ክትባት ላይ ሙከራ እንደሚጀምሩ አስታውቀዋል።

    ድርጅቶቹ እንዳስታወቁት በአሜሪካ በሚገኙ 11 ቦታዎች በተመረጡ 440 አዋቂዎች ላይ ክትባቱን የሚሞክሩ ሲሆን ታህሳስ ላይ ደግሞ ውጤቱን በማየት ተጨማሪ ሙከራ ይደረጋል።

    ውጤቱ አመርቂ ከሆነ ደግሞ እስከ ዓመቱ መጨረሻ ድረስ ተጨማሪ ሙከራዎች እንደሚደረጉም ተገልጿል።

    እስካሁን ድረስ 20 የሚሆኑ መድሀኒት አምራች ኩባንያዎች ለኮሮናቫይረስ የሚሆን ክትባት ለማግኘት ሙከራ በማድረግ ላይ ይገኛሉ።

    የአሜሪካ መንግሥት ደግሞ በመጪው ሕዳር ወር ላይ አንድ ክትባት ተመርቶ መሰራጨት እንደሚጀመር አስታውቋል።

  14. የኮቪድ-19 የላብራቶሪ ምርመራ ኔጋቲቭ ውጤት በተመርማሪዎች የእጅ ስልክ ላይ መላክ ተጀመረ

    የኢትዮጵያ የሕብረተስብ ጤና ኢንስቲትዩት የኮቪድ-19 ምርመራ ኔጋቲቭ ውጤቶች በ8335 በእጅ ስልካቸው የጽሑፍ መልዕክት እንዲደርሳቸው የሚያስችል ስራ መጀመሩን ገለፀ።

    ኢንስቲትዩቱ በፌስቡክ ገፁ ላይ ባሰፈረው መረጃ መሰረት የኮሮናቫይረስ ምርመራ አድርገው ከቫይረሱ ነጻ ለሆኑ የላቦራቶሪ ውጤቱን በእጅ ስልካቸው እንዲደርሳቸው እየተደረገ መሆኑን ገለጿል።

    ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር የላብራቶሪ ናሙና የተወሰደላቸው ሰዎች የኮሮና ቫይረስ የላቦራቶሪ የናሙና ምርመራ ውጤት ከተረጋገጠ በኋላ ከሶስት ሰዓት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ በ8335 በመጠቀም ተመርማሪዎች ውጤቱን በአጭር የጽሁፍ መልዕክት (SMS) እንዲደርሳቸው እየተደረገ መሆኑን ጨምሮ አስታውቋል።

    ተመርማሪዎች ትክክለኛ የስልክ ቁጥራቸውን ማስመዝገብ እንደሚጠበቅባቸው ያስታወቀው ኢንስቲትዩቱ ሌሎች ከኮሮናቫይረስ መከላከል ጋር የተያያዙ ስራዎችንም በኤሌክትሮኒክስ ለማካሄድ እየሰራ መሆኑን በፌስ ቡክ ሰሌዳው ላይ አስፍሯል።

  15. በአሜሪካ በኮቪድ-19 ምክንያት የተቸገሩ ኢትዮጵያውያንን እየረዱ የሚገኙ ወገኖች

  16. ሲዲሲ የኮቪድ-19 ክትባት የሚሰራጭበት መንገድ ላይ የአሜሪካ ግዛቶች ቀድመው እንዲዘጋጁ አሳሰበ

  17. 1105 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ተይዘዋል

    ባለፉት 24 ሰዓታት ለ21ሺህ 360 ሰዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ተደርጎ በ1ሺህ105 ሰዎች ላይ ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል።

    ይህም በአገሪቱ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርን ወደ 54ሺህ 409 ከፍ አድርጎታል።

    ከዚህ በተጨማሪም ባለፉት 24 ሰዓታት 18 ሰዎች በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ ሲሆን በጠቅላላው ከበሽታው ጋር በተያያዘ ህይወታቸው ያለፉ ሰዎች ቁጥር 846 ደርሷል።

    በሌላ በኩል በ24 ሰዓታት ውስጥ 416 ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል።

  18. የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የፕላስቲክ ብክለትን ጨምሮታል ተባለ

  19. 7 ቤተሰቡን በኮቪድ-19 የተነጠቀው ለኮቪድ-19 ክትባት ሙከራ ፍቃደኛ ሆነ

    7 የቤተሰብ አባላቱን በኮቪድ-19 ምክንያት የተነጠቀው ጃኮብ ሴራኖ የኮቪድ-19 ክትባት ሙከራ እንዲደረግበት ፍቃደኛ ሆኗል።

    የ23 ዓመቱ ወጣት አሜሪካዊ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ እና አስትራዜኔካ በጋራ የሚያበለጽጉት የኮሮናቫይረስ ክትባት እንዲሞከርበት ነው ፍቃደኛ የሆነው።

    "ሙከራ እንደመሆኑ መጠን የተጓዳኝ ችግር ሊያስከትል እንደሚችል ይገባኛል። ምንም ቢሆን ግን ለበሽታው መፍትሄ እንዲገኝ አንድ እርምጃ ወደፊት መራመድ እንዳለብን አስባለሁ" ሲል ለሲቢኤስ ኒውስ ተናግሯል።

    እየተሞከረ ያለው ክትባት ውጤታማ እና የተጓዳኝ ጉዳት የማያስከትል የአሜሪካው የምግብ እና መድሃኒት አስተዳደር ባለስልጣንን ይሁንታ ሲያገኝ ለሕዝብ ጥቅም ገብያ ላይ እንዲውል ይደረጋል።

    ክትባቱን እያበለጸጉ ከሚገኙ ባለሙያዎች መካከል ክትባቱ ውጤታማ ሊሆን እንደሚችል ተስፋቸውን እየገለጹ ይገኛሉ።

  20. አርሰናል ከ ሼፊልድ በሚያደርጉት ግጥሚያ ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም ሊመለሱ ይችላሉ

    በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መስከረም 3 2013 አርሰናል ከ ሼፊልድ ዩናይትድ በሚያደርጉት ግጥሚያ ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም ሊመለሱ ይችላሉ ተባለ።

    የመድፈኞቹ ደጋፊዎች በኢሚሬትስ ስታዲየም ለቡድናቸው ድጋፍ ለመስጠት በተስፋ እየተጠባበቁ ነው።

    ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም የሚመለሱት መንግሥት የሚያስተላልፈውን መመሪያ በመከተል ይሆናል።

    በዚህም ምናልባት በቁጥር አነስተኛ የሆኑ ደጋፊዎች ወደ ስታዲየም እንዲገቡ ሊፈቀድ ይችላል።

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ከተቋረጠ ወዲህ ስታዲየሞች እና ደጋፊዎች ተራርቀው ቆይተዋል።

    የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መስከረም መስከረም 2 2013 ይጀመራል።