በኮሮናቫይረስ ስጋት ምክንያት የ2012 ምርጫ መራዘሙ ተገለፀ

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ከተከሰተ ወዲህ አገራት የተለያየ እርምጃ እየወሰዱ ነው። የአየርም ሆነ የብስ ድንበሮቻቸው የዘጉ፣ ከተሞቻቸውን ከእንቅስቃሴ ያቀቡ እንዲሁም ሰዓት እላፊ የጣሉ አገራት በርካቶች ናቸው። ሁሉም ቢሆኑ በአንድ ድምጽ ስለ ወረርሽኙ መከላከያ ሲናገሩ የሚደመጠው አካላዊ ርቀትንና፣ የግል ንጽህናን መጠበቅ እንዲሁም የበሽታው ምልክት የሚታይባቸው ሰዎች ራሳቸውን ለይተው እንዲያቆዩ ነው። ዓለም በአሁኑ ሰዓት 33 ሺህ ያህል ዜጎቿን በኮቪድ-19 ምክንያት አጥታለች። ከዚህ ሰዓት ጀምሮ ከዓለም ዙሪያ የምናሰባስባቸውን ዘገባዎች በቀጥታ እናቀርብላችኋለን።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኮሮናቫይረስን ለመዋጋት የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች ሳኒታይዘር እያመረቱ ነው

    የኮሮናቫይረስ ሥርጭትን ለመግታት በሚደረገው ጥረት በአገሪቱ የሚገኙ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ሳኒታይዘር ማምረት ጀምረዋል።

    ከእነዚህም መካከል ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ እና ወለጋ ዩኒቨርሲቲ ተጠቃሽ ናቸው።

    ከእነዚህም መካከል ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ፣ ወለጋ ዩኒቨርሲቲ፣ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ተጠቃሽ ናቸው።

    ከዚህም በተጨማሪ ባህርዳርና ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከእጅ ንክኪ ነጻ የሆነ የእጅ መታጠቢያ እያመረቱ እንደሆነም ገልጸዋል።

    በቅርቡ ደግሞ ሳኒታይዘር የማምረት እንቅስቃሴውን መቀላቀሉን ያስታወቀው መቀሌ ዩኒቨርሲቲ ነው።

    የዩኒቨርሲተው ፕሬዝደንት ፕሮፌሰር ክንደያ ገ/ሕይወት በትዊተር ገጻቸው ላይ እንዳጋሩት የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የኬሚስትሪ ትምህርት ክፍል ሳኒታይዘር ማምረቱን ይቀጥላል።

  2. ደቡብ አፍሪካ የቤት ለቤት የኮሮናቫይረስ ምርመራ ልትጀምር ነው

    የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚደንት ሲሪል ራማፎሳ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት ሰፊ የምርመራ ፕሮግራም መጀመራቸውን አስታወቁ።

    ፕሬዚደንቱ 10 ሺህ የሚሆኑ የመስክ ሰራተኞች ቤት ለቤት እየዞሩ ምርመራ ማድረግ እንደሚጀምሩ ተናግረው፤ በዚህ የምርመራ ሂደት ምልክት ያሳዩ ሰዎች በቤታቸው አሊያም በሆስፒታል ራሳቸውን ለይተው እንዲቆዩ ይደረጋል ብለዋል።

    ከዚህም በተጨማሪ መንግሥት በቫይረሱ ከተያዙ ሰዎች ጋር ንክኪ ያላቸው ሰዎችን ለመከታተል የሚረዳ ቴክኖሎጂ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል።

    በደቡብ አፍሪካ 1 ሺህ 326 ሰዎች በኮሮናቫይረስ የሚመጣው ኮቪድ -19 በሽታ ተጠቂ ሆነዋል።

    እስካሁን አገሪቷ 3 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መሞታቸው አስታውቃለች።

    ደቡብ አፍሪካ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት የ21 ቀናት የእንቅስቃሴ ገደብ ከጣለች 5ኛ ቀኗን ይዛለች።

  3. ደቡብ ኮሪያ የመንግሥት ትዕዛዝን የሚተላለፉትን በእስር ልትቀጣ ነው

    የደቡብ ኮሪያ መንግሥት የኮሮናቫይረስን ለመከላከል የተላለፈውን ውሳኔ ጥሰው የሚገኙ ሰዎችን በእስር እቀጣለሁ አለ።

    ከወረርሽኙ ጋር በተያያዘ በለይቶ ማቆያ እንዲቆዩ የተላለፈን ውሳኔ ሳያከብሩ የሚገኙ ሰዎች የአንድ ዓመት እስራት ወይም የገንዘብ መቀጮ ይጣልባቸዋል ተብሏል።

    ከአምስት ቀናት በኋላ ተግባራዊ በሚደረገው ሕግ ከለይቶ ማቆያ ያለ ፍቃድ የሚወጣ ግለሰብ ከ8 ሺህ የአሜሪካ ዶላር በላይ ይቀጣል።

  4. ሦስት ጊዜ ተመርምረው ነጻ የሆኑት ሜርከል አሁንም ራሳቸውን እንደለዩ ናቸው ተባለ

    የጀርመኗ ቻንስለር አንጌላ ሜርከል አሁንም ራሳቸውን ለይተው እንደተቀመጡ ናቸው።

    ቻንስለሯ ለሦስተኛ ጊዜ ተመርምረው ሦስቴም ከኮቪድ-19 ነጻ እንደሆኑ ቢረጋገጥም እርሳቸው ግን ራሳቸውን ነጥለው መቀመጥ መምረጣቸውን የመንግሥት ቃል አቀባይ ገልጿል።

    መረሄተ መንግሥት አንጌላ ሜርከል የግል ሐኪም ቫይረሱ ከተገኘበት በኋላ ከቤታቸው ሆነው መስራት መጀመራቸው ተገልጾ ነበር።

    በወቅቱ የግል ሐኪማቸው ለ65 ዓመቷ ሜርከል የኒሞኒያ ክትባት ሰጥቷቸው ነበር ተብሏል።

    የመንግሥት ቃል አቀባይ ሜርከል ከቤት መስራታቸውን ለተወሰነ ቀን እንደሚቀጥሉበት አስታውቋል።

    የዩናይትድ ኪንግደሙን ጠቅላይ ሚንስትር፣ ቦሪስ ጆንሰንን ጨምሮ ሌሎች ቫይረሱ የተገኘባቸው ከፍተኛ ባለስልጣናት ራሳቸውን ለይተው መቀመጣቸው ይታወሳል።

  5. አፍሪካ ውስጥ ኮሮናቫይረስ የለም ያሉት ፓስተር የ7 ዓመት እስር ይጠብቃቸዋል ተባለ

    የኡጋንዳ ባለስልጣናት ትምህርቱን ለሚከታተሉ ምዕመናን አፍሪካ ውስጥ ኮሮናቫይረስ የለም ብለው ያስተማሩ አንድ አወዛጋቢ ፓስተርን ከሰሱ።

    ኦጉስቲን ይጋ የተባሉት ፓስተር አርብ ዕለት ሪቫይቫል ክርስቲያን በተባለ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተካሄደ ጉባኤ ላይ እንደተናገሩትና አገር ውስጥ ባሉ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ላይ በቀረበ ንግግራቸው ምክንያት ነው የአገሪቱ አቃቤ ሕግ ፓስተሩን የከሰሳቸው።

    ነገር ግን ፓስተሩ የቀረበባቸውን ክስ አስተባብለዋል።

    የኡጋንዳ ፖሊስ ቃል አቀባይ ፓትሪክ ኦንያንጎ ለኤኤፍፒ ዜና ወኪል እንዳሉት “ኮቪድ-19 አፍሪካ ውስጥም ሆነ ኡጋንዳ ውስጥ የለም ማለት መንግሥት በሽታውን ለመዋጋት የሚያደርገውን ጥረት ከማደናቀፍ በተጨማሪ፤ ሕዝቡ በሽታውን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ማድግ ካለበት ጥንቃቄ እንዲዘናጋ ያደርገዋል” ሲሉ የፖስተሩ ንግግር ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት ገልጸዋል።

    ፓስተር ኦጉስቲን ይጋ የኮሮናቫይረስ አፍሪካ ውስጥ የለም ማለታቸው በፍርድ ቤት ከተረጋገጠ እስከ ሰባት ዓመት የሚደርስ የእስር ቅጣት ሊጠብቃቸው እንደሚችል ተነግሯል።

    ኡጋንዳ እስካሁን ድረስ በግዛቷ ውስጥ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው የተረጋገጠ 33 ሰዎች አግኝታለች።

  6. የኮንጎ የቀድሞ ፕሬዚደንት ዮምቢ ኦፓንጎ በኮሮናቫይረስ መሞታቸው ተነገረ

    የሪፐብሊክ ኦፍ ኮንጎ የቀድሞ ፕሬዚደንት ዮምቢ ኦፓንጎ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ ባጋጠማቸው የጤና እክል በፓሪስ በ81 ዓመታቸው መሞታቸው ተነገረ።

    የቀድሞ ፕሬዝደንቱ በቫይረሱ ከመያዛቸው አስቀድሞ ታመው እንደነበር ቤተሰቦቻቸው አስታውቀዋል።

    ዮምቢ ኦፓንጎ ኮንጎ ብራዛቪልን ከአውሮፓዊያኑ 1977 ከሥልጣን እስከወረዱበት 1979 ድረስ አስተዳድረዋል።

    በአገሪቷ የመድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲ ሥርዓት እስከሚተዋወቅበት የአውሮፓዊያኑ 1991 ድረስም በርካታ ዓመታትን በእስር አሳልፈዋል።

    በ1997 በአገሪቷ የእርስ በርስ ጦርነት ከመነሳቱ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው አገልግለዋል።

    ከዚያም ከአስር ዓመታት በኋላ ወደ አገራቸው እንዲገቡ ከመፈቀዱ በፊት ወደ ፈረንሳይ ተሰደው ይኖሩ ነበር።

  7. ዩኒቨርስቲዎች የኮሮናቫይረስ ህሙማን ማገገሚያ ስፍራ ሊሆኑ ነው

    ዩኒቨርስቲዎች በኮሮናቫይረስ የተጠረጠሩና በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ ሰዎች ማቆያና ማገገሚያ ስፍራ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ እንደሆነ ተገለጸ።

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚንስቴር እንደገለጸው፤ ዩኒቨርስቲዎቹ በጀት መድበው ከሚገኙባቸው አካባቢዎች የጤና ቢሮዎች ጋር በመቀናጀት እየሰሩ መሆናቸውንም ተገልጾ ዝግጁ የማድረጉ ሥራ ያለበት ደረጃም ግምገማ ተካሂዷል።

    ሚኒስትሯ ፕሮፌሰር ሂሩት እንዳሉት ዩኒቨርስቲዎቹ አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ጠቁመው፤ ያለውን የመኝታ ክፍሎቹ አቀማመጥን መቀየር፣ በቂ መፀዳጃና መታጠቢያ ቤቶችን እንደሚገባና እንዲሁም የምግብ አቅርቦት በዩኒቨርስቲዎቹ እንደሚሸፈን ገልጸዋል።

  8. በፓናማ ወንዶችና ሴቶች ተለያይተው ከቤት እንዲወጡ ተደረገ

    የማዕከላዊ አሜሪካ አገር ፓናማ ጥብቅ የሆነ የኮሮናቫይረስ የመከላከል እርምጃ መውሰዷን የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የፓናማ ዜጎች ከቤት ያለመውጣ ገደብ የተጣለባቸው ከአንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ሲሆን አሁን ደግሞ ወንዶችና ሴቶች ለየብቻቸው ብቻ ከቤት መውጣት እንደሚችሉ አስቀምጧል።

    የእንቅስቃሴ ገደቡ ለቀጣዮቹ 15 ቀናት የሚቀጥል ሲሆን ከዛሬ ጀምሮ ሴቶች፣ ሰኞ፣ ረብዑና አርብ ለሁለት ሰዓት ብቻ አስፈላጊ ነገሮችን ለመሸማመት መውጣት ተፈቅዶላቸዋል።

    ወንዶች ደግሞ ማክሰኞ፣ ሐሙስ እና ቅዳሜ የሚወጡ ሲሆን እሁድ ዕለት አንድም ሰው ከቤቱ መውጣት እንደማይችል ተደንግጓል።

    “ይህ በቤት የመቀመጥ ትዕዛዝ ለሌላ ሳይሆን ሕይወታችንን ለመታደግ ነው” ብለዋል የደህንነት ሚኒስትሩ ጁዋን ፒኖ።

    ፓናማ የመጀመሪያውን በኮቪድ-19 የተያዘ ሰው ያገኘችው ከሶስት ሳምንት በፊት ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ከአንድ ሺህ በላይ ሰዎች ቫይረሱ እንዳለባቸው ተረጋግጧል።

    በፓናማ እስካሁን ድረስ በኮቪድ-19 ምክንያት 29 ሰዎች መሞታቸው ታውቋል።

  9. ፕሬዝዳንቱ የተዛባ መረጃ ያሰራጫሉ ተባሉ

    የብራዚሉ ፕሬዝዳንት ዢየር ቦልሶናሮ በፌስቡክ ገጻቸው ላይ ያሰፈሯቸው ተንቀሳቃሽ ምስሎች፣ ኮሮናቫይረስን በሚመለከት ስለ ራስን ለይቶ ማቆየት የተዛባ መረጃን ያሰራጫሉ በሚል ፌስቡክ ከአካውንታቸው ላይ ሰረዛቸው።

    የማህበራዊ ሚዲያ ኃላፊዎቹ የፌስቡክንም ሆነ የኢናስታግራምን ደረጃዎች ይጥሳሉ ሲሉ የፕሬዝዳንቱን መልዕክቶች አብጠልጥለዋል።

    በዚህ በተሰረዘው የፕሬዝዳንቱ መልዕክት ላይ ቦልሶናሮ ሰዎች የአገራቸውን ኢኮኖሚ ለመርዳት ሥራ መግባት እንዳለባቸው ይናገሩ ነበር ተብሏል።

    በሳምንቱ መጨረሻ ላይም ትዊተር የፕሬዝዳንቱን በርካታ መልዕክቶች መሰረዙ ታውቋል።

    ትዊተርም እንደ ሌሎቹ የማህበራዊ መገናኛ ብዙኀን ሁሉ የፕሬዝዳንቱ መልዕክት የማህበረሰብ ጤና መመሪያዎቹን የሚጥሱና በዚህ ወቅት ሰዎችን ለበለጠ የኮቪድ-19 ስርጭት የሚያጋልጡ ናቸው ሲል ተችቷቸዋል።

    ፕሬዝዳንቱ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ከተከሰተ ጀምሮ ስለቫይረሱ ባላቸው የተዛባ አመለካከት የተነሳ ትችት ሲቀርብባቸው ነበር።

    በብራዚል የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመግታት በሚል የሚያስተዳድሯቸውን ክልሎችና ከተሞችን በመዝጋት ከእንቅስቃሴ ውጪ ያደረጉና ተጨማሪ የመከላከል ርምጃዎችን የወሰዱ ባለስልጣናቶቻቸውን በነገር ሲሸነቁጡ ተሰምቷል።

    የመገናኛ ብዙኀንንም “ፍርሃት ነዢዎች” ሲሉ ኮንነዋል።

  10. ጃፓን የውጪ አገር ዜጎች ወደ ግዛቷ እንዳይገቡ ልትከለክል ነው

    የጃፓን መንግሥት ከአሜሪካ፣ ከቻይና፣ ከደቡብ ኮሪያ እንዲሁም ከዩናይትድ ኪንግደምን ጨምሮ ከበርካታ የአውሮፓ አገራት የሚመጡ መንገደኞች ወደ ጃፓን እንዳይገቡ ሊያግድ መሆኑ ተሰምቷል።

    ጃፓን በውጪ ጉዳይ ሚኒስትሯ ቶሺሚትሱ ሞቴጊ በኩል ዜጎቿ ወደ 73 አገራት እንዳይጓዙ የጠየቀች ሲሆን፣ የውጪ አገራት ዜጎች ወደ ጃፓን እንዳይገቡ የተከለከለው ከመቼ ጀምሮ መሆኑን ግን ያሉት ነገር የለም።

    በጃፓን 1ሺህ 953 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ሲረጋገጥ 56 ሰዎች ደግሞ በዚሁ ምክንያት መሞታቸው ተገልጿል።

    የጃፓኑ ፕሬዝዳንት ሺንዞ አቤና ምክትላቸው ታሮ አሶ ለጥንቃቄ ሲባል ተመሳሳይ ስብሰባ አንድ ላይ እንዳይካፈሉ መወሰኑም ተሰምቷል።

  11. እንደምን አደራችሁ የቢቢሲ አማርኛ ቤተሰቦች!

    ኢትዮጵያ ውስጥ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ከተከሰተ ጊዜ አንስቶ የፌደራል መንግሥቱ እና የክልል መንግሥታት የተለያዩ እርምጃዎችን እየወሰዱ ነው።

    ትናንትና በስፋት እንዳስተዋልነው የሰዎችን ከቦታ ቦታ እንቅስቃሴ በመግታት የቫይረሱን ስርጭት ለመቆጣጠር በማሰብ ክልሎች የሕዝብ ማመላሻ ተሽከርካሪዎች እንቅስቀሴዎችን ገድበዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይም ትናንት በሰጡት መግለጫ ላይ በተለያየ አካባቢ የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመከላከል ተግባራዊ እንዲሆኑ የተላለፉ መልዕክቶች በአግባቡ ተግባራዊ እየሆኑ አይደሉም ብለዋል።

    ከሌላ አገራት ልምድ መረዳት እንደሚቻለው በጤና ባለሙያዎች የሚነገሩ መልዕክቶችን አለመተግበር የሚያስከፍለው ዋጋ ውድ ነው።

    ስለዚህ እናንት ቤተሰቦቻችን ራሳችሁንና የምትወዷቸውን ከቫይረሱ ለመከላከል የሚሰጡ መልዕክቶችን በአግባቡ መተግበር አትርሱ።

    አትዘናጉ!

    እኛ ከዚህ ሰዓት ጀምሮ አሁናዊ የሆኑ የአገር ውስጥ እና የውጪ መረጃዎችን በቀጥታ ማቅረብ እንጀምራለን።

    አብረን እንሁን!