ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉና ስብሰባዎች እንዳይካሄዱ ተወሰነ

በኢትዮጵያ ውስጥ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ቁጥር አምስት መድረሱን ተከትሎ በመላ አገሪቱ ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉና ስብሰባዎች እንዳይካሄዱ መወሰኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ አስታወቁ። ቢቢሲ አማርኛ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ዙሪያ የሚወጡ ትኩስ ዘገባዎችን በቀጥታ ያቀርባል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኮሮናቫይረስ ጥርጣሬ የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ እራሳቸውን ለይተው ተቀመጡ

    የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ የሆኑት ዶክትር ቶላ በሪሶ በኮሮናቫይረስ ስጋት ምክንያት እራሳቸውን ለይተው በአንድ ክፍል ለብቻቸው መቀመጣቸውን ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው ተብሎ ይፋ ከተደረገውና ጃይካ የሚባለው በትምህርት ላይ ከሚሰራው የተራድኦ ድርጀት ባልደረባ ከሆነው ጃፓናዊ ጋር በሥራ ምክንያት በመገናኘታቸው እራሳቸውን ለተወሰኑ ቀናት ለይተው እንዲያቆዩ ያደረጋቸው ምክንያት እንደሆነ ኃላፊው ገልጸዋል።

    ጃፓናዊው ከዶክትር ቶላ ጋር በተገናኘበት በዚያን ጊዜ "ገና ከውጪ አገር መምጣቱ ስለነበር ምንም አይነት የበሽታው ምልክት አይታይበትም ነበር" በማለት ከእርሱ ጋርም አንድ ኢትዮጵያዊ አብሮት እንደነበረ ለቢቢሲ ገልጸዋል።

    ይህ ጃፓናዊ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኋላ በአርሲ ዞን ሁለት ትምርት ቤቶችን ጎብኝቶ እንደነበረ የሚናገሩት ኃላፊው እሱ በሄደባቸው ቦታዎች አብረተውት የነበሩ ሰዎችም እራሳቸውን ለይተው ክትትል እተደረገላቸው መሆኑን ለቢቢሲ ተናግረዋል።

  2. በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች አራት ደረሰ

    በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ተጨማሪ ሦስት ሰዎች መገኘታቸውን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ባለፈው ሳምንት አርብ በሽታው ከተገኘበት የውጪ አገር ዜጋ ጋር አራት ሰዎች በበሽታው መያዛቸው መረጋገጡ ተገልጿል።

    ቀደም ሲል በበሽታው መያዙ የተረጋገጠው ግለሰብ ጃፓናዊ ሲሆን አሁን ከተገኙት ሦስት ሰዎች መካክል ሁለቱ ጃፓናዊያን ሲሆኑ አንዱ ኢትዮጵያዊ ነው።

    አሁን በበሽታው መያዛቸው የተረጋገጠው ሦስቱ ሰዎች መጀመሪያ ላይ መያዙ ከተነገረው ግለሰብ ጋር ግንኙነት እንደነበራቸው ታውቋል።

    በተጨማሪም በበሽታው የተጠረጠሩ 117 ሰዎች ተለይተው ክትትል እየተደረገባቸው ሲሆን ተጨማሪሰዎችን የመለየት ሥራም እየተከናወነ መሆኑ ተገልጿል።