ሰበር, ፓይለቱ ችግር ገጥሞት ነበር
የአውሮፕላኑ አብራሪ ችግር ስላጋጠመው ወደ አዲስ አበባ ለመመለስ ጠይቆ እንዲመለስ ተነግሮት እንደነበር የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማሪያም ተናግረዋል። አውሮፕላኑ ከጆሃንስበርግ በረራው ሲመለስ ምንም አይነት የበረራ ችግርን የሚመለከት መረጃ እንዳልነበርና ከሶስት ሰዓት በላይም መሬት ላይ ቆይቶ እንደነበር አቶ ተወልደ ገልፀዋል።
ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በትናንትናው ዕለት 149 መንገደኞችንና 8 የበረራ ሰራተኞችን አሳፍሮ ወደ ናይሮቢ ሲበር የነበረው አውሮፕላን ቢሾፍቱ አቅራቢያ ነው የተከሰከሰው። በአደጋውም 157 ተሳፋሪዎች ህይወታቸውን አጥተዋል
የአውሮፕላኑ አብራሪ ችግር ስላጋጠመው ወደ አዲስ አበባ ለመመለስ ጠይቆ እንዲመለስ ተነግሮት እንደነበር የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማሪያም ተናግረዋል። አውሮፕላኑ ከጆሃንስበርግ በረራው ሲመለስ ምንም አይነት የበረራ ችግርን የሚመለከት መረጃ እንዳልነበርና ከሶስት ሰዓት በላይም መሬት ላይ ቆይቶ እንደነበር አቶ ተወልደ ገልፀዋል።
ቦይንግ በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው ቦይንግ 737 በቢሾፍቱ ተከስክሶ ከ 100 በላይ ግለሰቦች በሞቱበት አደጋ የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን አስተላልፏል።
ድርጅቱ ባወጣው መግለጫ በዚህ አደጋ ቤተሰቦቻቸውንና ወዳጆቻቸውን ላጡ ግለሰቦች ከፍተኛ መፅናናትን ተመኝቶ የኢትዮጵያ አየር መንገድን በሚያስፈልገው መንገድ ለመርዳት ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል።
የቦይንግ የቴክኒካል ቡድንም እርዳታን ለመለገስም ከኢትዮጵያ የሚመጣውን ጥያቄ እየጠበቁ እንደሆነ አስታውቀዋል።
ከET 302 መንገደኞች 32 ኬንያዊያን፣ 18 ካናዳዊያን፣ 9 ኢትዮጵያዊያን ሲሆኑ የሌሎች አገር ዜጎችም ይገኛሉ። አውሮፕላኑ ቦይንግ 737 ከተገዛ አራት ወር የሆነው ሲሆን ዛሬ ጠዋት ደግሞ ከጆሃንስበርግ እንደመጣ ታውቋል።
የአውሮፕላኑ አብራሪ የነበረው ያሬድ ሙልጌታ ኢትዮጵያ ኬንያዊ ነው ተብሏል።
ከ149ኙ መንገደኞች 8ቱ ቻይናዊያን መሆናቸው ታውቋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ የሆኑት አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም አደጋው ከደረሰበት ቦታ ተገኝተዋል። ቦታው ላይ ሲደርሱ ጭስ ብቻ እንደነበር አቶ ተወልደ ተናግረዋል።
ET302 ከጠዋቱ 4፡30 ጆሞ ኬንያታ አውሮፕላን ማረፊያ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቅ የነበረ ሲሆን የዘመድ ወዳጆቻቸውን መድረስ ሲጠባበቁ የነበሩ የመንገደኛ ዘመዶች በአሁኑ ሰዓት በከፍተኛ ሃዘን ላይ ይገኛሉ።
የኬንያ ትራንስፖርት ሚኒስቴር አጋጣሚው እጅግ ከባድ ቢሆንም አደጋውን በሚመለከት በቀዳሚነት መረጃ መስጠት ያለበት የኢትዮጵያ አየር መንገድ በመሆኑ እነዚህ ሰዎች በትእግስት እንዲጠባበቁ አስታውቋል።
የትራንስፖርት ሚኒስትሩ ጄምስ ዋይናና የኬንያ መንግስት አደጋውን ተከትሎ ለሚመለከታቸው የኢትዮጵያ አካላት ድጋፍ እያደረገ እንደሆነና ለዚሁም ጆሞ ኬንያታ አውሮፕላን ማረፊያ አቅራቢያ ማእከል ማቋቋሙን ገልፀዋል።
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ዘመዶቻቸው የአውሮፕላኑ መንገደኛ ለነበሩ ሰዎች ቤተሰብና ወዳጅ መረጃ ይሰጡ ዘንድ የነፃ ስልክ መስመር (+254)733666066 አድርጓል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድም ተሳፋሪዎችን የሚመለከት መረጃ መስጠት የሚቻልባቸውን የስልክ መስመሮች ቀደም ብሎ ይፋ አድርጎ ነበር
የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በአደጋው ማዘናቸውን ገልፀዋል።
አደጋው በደረሰበት ስፍራ የሚኖሩት አቶ በቀለ ጉተማ ለቢቢሲ እሳቱና ፍንዳታው ከፍተኛ እንደነበረ ገልፀዋል። ‘‘በጣም ነው የሚያሳዝነው። እሳቱ በጣም ከፍተኛ ነው’’ ብለዋል።ከእሳቱ ከፍተኛነት የተነሳ የአካባቢው ሰው እርዳታ ለማድረግ ቢፈልግም ስላልቻለ የእርዳታ ሰራተኞች እስኪመጡ ድረስ ይመለከቱ እንደነበር ጨምረው አስረድተዋል። ቢቢሲ ከቢሾፍቱ ከተማ ነዋሪዎች እንደሰማው ከሆነ ከቢሾፍቱ ከተማ አደጋው ወደ አጋጠመበት ሮብ ገበያ ጊምቢቹ ጋራ ቀበሌ የሚያቀኑ በርካታ አምቡላንሶች እና የእሳት አደጋ መኪኖች ተመልክተዋል። ጨምረውም በቢሾፍቱ ከተማ የሚገኘው የአየር ኃይል ወደ ስፍራው እንደተንቀሳቀሰ መስማታቸውን ተናግረዋል።
‘‘አራት ሄሊኮፍተር በቦታው ደርሰው ነበር። ፍንዳታው እና እሳቱ አያስጠጋም ነበረ። አሁን ነዶ አልቋል።’’ . . . ''የእሳት አደጋ ሰራተኞች በቦታው የደረሱት እሳቱ ነዶ ካለቀ በኋላ ነው'' ብለዋል አቶ በቀለ።
የአውሮፕላኑ ተሳፋሪዎች ፤ የ33 አገር ዜጎች በሙሉ መሞታቸውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቃል አቀባይ ለኢቢሲ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው ቦይንግ 737 ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ በመጓዝ ላይ እያለ መብረር ከጀመረ ከስድስት ደቂቃዎች በኋላ ግንኙነት የጠፋ ሲሆን ቢሾፍቱ አካባቢ ላይ ተከስክሷል።
አውሮፕላኑ ከአራት ወራት በፊት ነው የተገዛው።
ET 302 አውሮፕላን 149 መንገደኞችንና 8 የበረራ ሰራተኞችን አሳፍሮ ነበር።
አውሮፕላኑ ከቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የተነሳው ጠዋት 2፡38 ሲሆን ከ6 ደቂቃ በኋላ ከአብራሪዎቹ ጋር ይደረግ የነበረው ግንኙነት ተቋርጧል።
አውሮፕላኑ የተከሰከሰው ቢሾፍቱ አቅራቢያ ነው።
ከአደጋው የተረፈ መንገደኛ ስለመኖር አለመኖሩ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቦታው ሰራተኞቹን መላኩን ረፋዱ አምስት ሰዓት ላይ ባወጣው የአደጋ ሪፖርት አስታውቋል።