ዩክሬን በሩሲያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ 13 ሰዎች ተገደሉ
ዩክሬን በሩሲያዋ ግዛት ታታርስታን ሪፐብሊክ ውስጥ በፈጸመችው የድሮን ጥቃት አንድ ሕጻንን ጨምሮ 13 ሰዎች መገደላቸውን የሞስኮ ባለሥልጣናት ተናገሩ።
ከትናንት እሁድ ምሽት ጀምሮ የተፈጸመው ድብደባ ሞስኮ ዩክሬን ላይ ሙሉ ጦርነት ከከፈተች ወዲህ ሩሲያ ላይ ተሰንዝረው በርካታ ሰዎችን ከገደሉ ጥቃቶች አንዱ ሆኗል።
ዩክሬን ከድንበሯ ከ1,100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው ኒዝኔካምስክ ከተማ ላይ ፈጽማዋለች ስለተባለው ጥቃት እስካሁን አስተያየት አልሰጠችም።
የዩክሬን ጦር ኒዝኔካምስክ ከተማ ውስጥ የሚገኘው ‘ታኔቮ’ የነዳጅ ማጣሪያን መምታቱን ገልጿል። የዩክሬኑ የመከላከያ ቴክኖሎጂ አምራች ‘ፋየርፖይንት’ በበኩሉ ጥቃቱ የተፈጸመው በኩባንያው የተመረቱ ‘ኤፍፒ-1’ ድሮኖች መሆኑን አስታውቋል።
ጥቃቱ ከሌሊት እስከ ጠዋት ድረስ ለሰዓታት የቆየ እንደነበር የአካባቢው ምንጮች ተናግረዋል።
ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለቀቁ እና ትክክለኛነታቸው የተረጋገጠ ቪዲዮዎች ጭስ እና እሳት ወደ ሰማይ ሲወጣ አሳይተዋል። የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደውል ድምፅም ቪዲዮው ላይ ይሰማል።
ሩሲያ የኢንዱስትሩ ተቋማት እና የመኖሪያ አካባቢዎች ዒላማ መደረጋቸውን አረጋግጣለች። የሩሲያ የምርመራ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ፤ “በማንኛውም ወታደራዊ ኦፕሬሽን ውስጥ ተሳትፎ የሌላቸው ሰላማዊ ሰዎች ቦታው ላይ ነበሩ” ብሏል። ቢቢሲ ይህንን መረጃ በራሱ አላረጋገጠም።
ትናንት ሌሊት ከዩክሬን የተላኩ 450 ድሮኖች በሩሲያ አየር መከላከያዎች ተመትተው መውደቃቸው ተገልጿል።
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ዩክሬን ከድንበሯ ረጅም ርቀት ላይ የሚገኙ የሩሲያ ዒላማዎች ላይ የተሳኩ ጥቃቶችን ማድረስ ጀምራለች።
እነዚህ ጥቃቶች ብዙውን ጊዜ ዒላማ የሚያደርጉት መጋዘኖች እና የኃይል መሠረተ ልማቶችን ሲሆን፣ በዚህ ምክንያት የሚገደሉ ሰላማዊ ሰዎች ቁጥርም ጨምሯል።
ዩክሬን እነዚህ መሠረተ ልማቶች ሩሲያ ለምታካሂደው ጦርነት የገቢ እና የሎጂስቲክ አስተዋጾ ያደርጋሉ የሚል ክስ ታቀርባለች።