የሳዑዲው ልዑል አሜሪካ በሁቲዎች ላይ ጥቃት እንድትፈጽም ጠይቀው ተቀባይነት አለማግኘታቸው ተዘገበ

የሳዑዲ አረቢያው ልዑል ሞሐመድ ቢን ሳልማን ሐሙስ ዕለት ሁለት ጊዜ ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ስልክ ደውለው በየመን በሚገኙት የሁቲ ታጣቂዎች ላይ አሜሪካ የአየር ጥቃት እንድትፈጽም መጠየቃቸው ተዘገበ።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በየመን የሚካሄደው ጦርነት ዋነኛ ተዋናዮች እነማን ናቸው?

    በፈራረሱ ሕንፃዎች ፊት የሚታይ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, ለዓመታት በዘለቀው የተለያዩ ኃይሎች እየሳተፉበት ባለው የየመን የእርስ በርስ ጦርነት አገሪቱ ከባድ ውድመት ደርሶባታል

    በየመን የሚካሄደው ጦርነት ሞቅ ቀዝቀዝ እያለ ለዓመታት ቆይቷል። በዚህም በኢራን የሚደገፉት ሁቲ ታጣቂዎች እና ሳዑዲ በምትመራው ጥምረት የሚደገፈው የአገሪቱ መንግሥት የመንን ለሁለት ተካፍለው የበላይነት ለመያዝ ሲፋለሙ ቆይተዋል።

    ሁለቱ ወገኖች ለዓመታት በተለያዩ አጋጣሚዎች እየተዋጉ የቆዩ ቢሆንም ካለፈው ዓመት አጋማሽ ወዲህ ግን ግጭቱ እየተባባሰ ነው።

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር ጦርነት ውስጥ መግባቷ እና ሳዑዲ አረቢያ ለየመን መንግሥት የምታደርገው ድጋፍ መጠናከርን ተከትሎ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ፍጥጫ ሰፍቷል።

    ሳዑዲ የሁቲ ተቀናቃኝ የየመን ኃይሎችን ከመደገፍ ባሻገር ባለፉት ወራት የሁቲ ይዞታዎችን በአየር ማጥቃቷ ከሁቲ ኃይሎች ተከታታይ የአጸፋ ጥቃትን አስከትሎባታል።

    በአሁኑ ጊዜ ሁቲዎች እየተጠናከሩ በሳዑዲ የሚደገፈውን የየመን መንግሥትን በማዳከም ወሳኝ የባሕር ዳርቻዎችን እና ደሴቶችን እየተቆጣጠሩ ነው።

    ለመሆኑ በዚህ የየመን ቀውስ ውስጥ ዋነኛ ተዋንያኑ እነማን ናቸው?

    “አንሳር አላህ” የሁቲ ኃይሎች

    የኢራን አጋር የሆኑት ሁቲዎች ዋና ከተማዋን ሰነዓን ጨምሮ ሰፊ የአገሪቱን ግዛቶች የሚቆጣጠሩ ናቸው። ሁቲዎች ሚሳዔሎችን እና ድሮኖችን የታጠቁ ሲሆን፣ በቀይ ባሕር ላይ ጉልህ ተጽእኖን ማሳደር የሚችሉ መሆናቸውን አሳይተዋል። ከየመን አልፈውም በቀይ ባሕር ላይ፣ በሳዑዲ አረቢያ እና አስከ እስራኤል የሚደርስ ጥቃት የመፈጸም አቅም አላቸው።

    ሳዑዲ አረቢያ

    የየመን ተጎራባች የሆነችው ሳዑዲ የአረብ አገራትን ወደታራዊ ጥምረት በመምራት ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያለውን የየመን መንግሥት ለመደገፍ በግጭቱ ውስጥ ተሳታፊ ናት። በዚህም ሳቢያ ከሁቲ ኃይሎች ጋር በየመን ውስጥ እና ድንበር ተሻጋሪ ግጭት ውስጥ ገብታለች።

    ፕሬዝዳንታዊ ምክር ቤት

    ፀረ ሁቲ የሆነው እና የሳዑዲ እና የሌሎችም አገራት ዕውቅና ያለው የየመን መንግሥት ነው። በአገሪቱ የሚካሄደውን ጦርነት ለማስቆም በየመን ፖለቲከኞች እና ወታደራዊ መኮንኖች የሚመራ ነው። ነገር ግን የሁቲ ታጣቂዎችን ለመቆጣጠር የተሳ ሲሆን ባለፉት ሳምንታት በታጣቂዎቹ በደረሰበት ጫና በርካታ አካባቢዎችን በሁቲ ኃይሎች ተነጥቋል።

    የኢስላህ ፓርቲ

    ሌላኛው ፀረ ሁቲ ቡድን ኢስላህ ፓርቲ ከየመን መንግሥት ጋር የሚሠራ ሲሆን፣ በየመን ፖለቲካዊ እና ወደታራዊ ቀውስ ውስጥ የራሱ ሚና አለው።

    የየመን ብሔራዊ ኃይሎች

    ይህ ናሽናል ሬዚስራንስ ፎርስስ የሚባለው ኃይል በሳዑዲ የሚደገፍ የወታደራዊ ኃይሎች ስብስብ ነው። አቋሙ ፀረ ሁቲ ሲሆን ከሌሎች የየመን ፖለቲካዊ ኃይሎች ጋር የሚሠራ ነው።

    በጥቅሉ ሲታይ በየመን ውስጥ የተለያዩ ኃይሎች ያሉ ቢሆንም ከሁቲ ታጣቂዎች በስተቀር ቀሪዎቹ አቋማቸው በአንድ ሊጠቃለል የሚችል የፖለቲካ እና ወታደራዊ ስብስቦ ችናቸው። ስለዚህም ሁቲዎች የሚፋለሙት ተመሳሳይ ዓላማ እና ድጋፍ ካላቸው ኃይሎች ጋር ነው ሊባል ይችላል።

  2. የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል የአሜሪካ መርከቦች ወደ ሆርሙዝ እንዳይጠጉ አስጠነቀቀ

    የኢራን ባሕር ኃይል ጀልባ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል ምክትል አዛዥ አሊ ሞሐመዲ፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሆርሙዝ ወሽመጥን እቆጣጠራለሁ ማለታቸውን በመጥቀስ፣ የአሜሪካ መርከቦች ወደ ኢራን የባሕር ክልል እንዳይቀርቡ አስጠንቅቀዋል።

    የአብዮታዊ ዘቡ ከፍተኛ ባለሥልጣን እንዳሉት፣ “የአሜሪካኖች መርከቦች ከቀረቡ የኢራን ተዋጊዎች ምላሽ እንደሚሰጧቸው ያውቃሉ” በማለት ምንም ዓይነት በዝርዝር ሳይሰጡ “የዚህ ዓይነት ሁኔታ ባለፉት ቀናት ተከስተው ነበር” ሲሉ ተናግረዋል።

    ባለሥልጣኑ በማሽሃድ ከተማ ውስጥ በተደረገ የመንግሥት ደጋፊዎች የምሽት ሰልፍ ላይ እንደተናገሩት “ዛሬ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ፣ በኦማን ባሕር እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የአሜሪካ ወታደሮች የሉም፤ በእነዚህ አካባቢዎችም የአሜሪካ ወታደራዊ መሳሪያዎችም አልተሰማሩም። አሜሪካኖች ወደ ተከለከለው ቀጠና ከቀረቡ ምን እንደሚደርስባቸው ራሳቸው ያውቃሉ” ብለዋል።

    የአብዮታዊ ዘቡ ምክትል አዛዥ ጨምረውም “ከኩዌት እና ከባህሬን የሚነሳ ማንኛውም መርከብ ያለ ልዩነት በባሕር ኃይሉ ክትትል ሥር ነው፤ ሕግ ወይም ደንብ መጣሱ ከተረጋገጠ ደግሞ እርምጃ ይወሰድበታል” በማለት አስጠንቅዋል።

  3. የየመን ሁቲዎች በሳዑዲ ወታደራዊ ማዕከል ላይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት መፈጸማቸውን አስታወቁ

    የሁቲ ወደታሮች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የየመን ሁቲ ኃይሎች በደቡባዊ ሳዑዲ አረቢያ በሚገኝ አንድ ወታደራዊ ማዕከል ላይ በባለስቲክ ሚሳዔሎች እና በድሮኖች ጥቃት መፈጸማቸውን አስታወቁ።

    የሁቲዎች ወታደራዊ ቃል አቀባይ ያህያ ሳሬ በኤክስ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ እንደጻፉት፣ ጥቃቱ የተፈጸመው በደቡባዊ ሳዑዲ አረቢያ በሚገኘው የሻሩራ ወታደራዊ ጣቢያ ላይ ነው።

    እንደ ቃል አቀባዩ ገለጻ፣ ጥቃቶቹ የሳዑዲ አረቢያን “የጦር መሣሪያ ማከማቻዎች እና የዕዝ እና ቁጥጥር ማዕከላት” ዒላማ አድርገዋል።

    ነገር ግን ሳሬ ጥቃቱ በትክክል መቼ እንደተፈጸመ አልገለጹም። ሆኖም ሳዑዲ ዐረቢያ በየመን ላይ የምታደርገውን ወታደራዊ እርምጃ ከቀጠለች፣ ወደ ግዛቷ ወደ ውስጥ ዘልቀው በመግባት የሚፈጸሙ የበለጠ ሰፊ እና ጠንካራ ጥቃቶች እንደሚከተሉ አስጠንቅቀዋል።

  4. የሳዑዲው ልዑል አሜሪካ በሁቲዎች ላይ ጥቃት እንድትፈጽም ጠይቀው ተቀባይነት አለማግኘታቸው ተዘገበ

    ልዑል ቢን ሳልማን እና ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ልዑል ቢን ሳልማን እና ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    የሳዑዲ አረቢያው ልዑል ሞሐመድ ቢን ሳልማን ሐሙስ ዕለት ሁለት ጊዜ ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ስልክ ደውለው በየመን በሚገኙት የሁቲ ታጣቂዎች ላይ አሜሪካ የአየር ጥቃት እንድትፈጽም መጠየቃቸው ተዘገበ።

    አክሲዮስ የተባለው የአሜሪካ የዜና ድረ ገጽ ሁለት የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ጠቅሶ እንደዘገበው ጥያቄውን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ውድቅ አድርገውታል፤ የአሜሪካ ባለሥልጣናትም አስተዳደሩ በአሁኑ ወቅት በሁቲዎች ላይ ቀጥተኛ ወታደራዊ እርምጃ የመውሰድ ዕቅድ እንደሌለው ገልጸዋል።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል ሳዑዲ የአየር ጥቃቱን ስለመጠየቋ ለማጣራት ለአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት ዋይት ሐውስ እና በዋሽንግተን ላለው የሳዑዲ ኤምባሲ ጥያቄ ቢቀርብም ወዲያውኑ ምላሽ አላገኘም።

    እንደ አክሲዮስ ዘገባ፣ አሜሪካ በየመን ውስጥ በፈጣን ሁኔታ እየተባባሰ ያለውን ግጭት በከፍተኛ ስጋት እየተከታተለችው ሲሆን፣ ነገር ግን ቀጥተኛ ወታደራዊ እርምጃ ውስጥ ላለመግባት ለሳዑዲ አረቢያ የምትሰጠውን ድጋፍ እያጠናከረች ነው።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ አድሚራል ብራድ ኩፐር ሐሙስ ዕለት ለአስቸኳይ የቅንጅት ውይይት ወደ ሳዑዲ አረቢያ መጓዛቸውም ተዘግቧል።

    ዘገባው ጨምሮም የአሜሪካ ወታደራዊ እና ሲቪል ባለሥልጣናት ባለፉት ሳምንታት ለሳዑዲ አቻዎቻቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕ የሰጡት መመሪያ፣ የአሜሪካ ኃይሎች ትኩረታቸውን በኢራን እና በሆርሙዝ ወሽመጥ የመርከብ እንቅስቃሴን በመጠበቅ ላይ እንዲያደርጉ፣ ሌላ የወታደራዊ ግጭት ግንባር ከመክፈት እንዲቆጠቡ የሚል መሆኑን ገልጸዋል።

    የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ዒላማ የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ መርከቦቿ በቀይ ባሕር ደቡባዊ ክፍል በኩል እንዳያልፉ በቡድኑ እገዳ የተጣለባቸው ሲሆን፣ የሁቲዎችን ጥቃት ለመከላከልም ከቱርክ እና ከፓኪስታን ጋር ጥምረት ከመመሥረቷ በተጨማሪ ምዕራባውያን የቀይ ባሕርን ደኅንነት በመጠበቅ እንዲተባበሩ ጥሪ አቅርባለች።

    በኢራን እንደሚደገፉ የሚነገርላቸው ሁቲዎች በሳዑዲ በሚመራው ጥምረት የሚደገፈውን የየመን መንግሥት በማዳከም የአገሪቱን ሰፊ አካባቢ እየተቆጣጠሩ ነው።

    ባለፉት ቀናትም ይዞታቸውን እያሰፉ ወደ ቀይ ባሕር የሚሰስገባውን የባብ ኤል መንደብ መተላለፊያ ወሽመጥን ለመቆጣጠር የሚሰስችሏቸውን የየመን ወደቦች እና የባሕር ዳርቻዎችን በእጃቸው አስግበተዋል።

  5. በሁቲ ኃይሎች ተተኮሰ የተባለ ተወንጫፊ ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ ሁለት ሰዎችን አቆሰለ

    የሁቲ ሚሳዔሎች

    የፎቶው ባለመብት, Almasirah

    የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ወደ የሳዑዲ አረቢያ ተኮሱት ባተባሉ ተወንጫፊ ምክንያት ሁለት ሰዎች መቁሰላቸውን የአገሪቱ ባለሥልጣናት አስታወቁ።

    የሳዑዲ ባለሥልጣናት እንደገለጹት፣ ቅዳሜ ዕለት በሁቲ ኃይሎች የተተኮሰ አንድ ተወንጫፊ በየመን ድንበር አቅራቢያ በሚገኝ የሳውዲ አረቢያ ደቡባዊ አካባቢ በመውደቁ ነው ሰዎች ላይ ጉዳት ያደረሰው።

    የሳዑዲ የሲቪል መከላከያ ክፍል እንዳለው ጥቃቱ የደረሰው ጃዛን በተባለ ግዛት ውስጥ በሚገኘው የአል ተዋል አውራጃ ሲሆን የአካባቢው ኃይሎች ለጥቃቱ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ከየመን በኩል የተተኮሰው ተወንጫፊ ሁለት ሰዎችን ከማቁሰሉ በተጨማሪ አንድ መስጊድ፣ በርካታ ሕንፃዎች እና በርካታ ተሽከርካሪዎች ላይ ጉዳት ማድረሱ ተገልጿል።

    ይህ ጥቃት የተፈጸመው የሳዑዲ ባለሥልጣናት በሁቲ ኃይሎች ላይ አዳዲስ ጥቃቶች ሊፈጸሙ እንደሚችሉ ማስጠንቀቂያ ከሰጡ ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ነው።

    በየመን ውስጥ ቁጥጥራቸውን እያሰፉ ያሉት የሁቲ ኃይሎች በሳዑዲ አረቢያ ላይም ድንበር ተሻጋሪ ጥቃት ሲፈጽሙ ቆይተዋል።

    ሳዑዲ አረቢያም በበኩሏ የሁቲ ተቀናቃን የሆኑ የየመን ቡድኖችን ከመደገፍ አልፋ በታጣቂዎቹ ይዞታዎች ተደጋጋሚ የአየር ድብደባዎችን ትፈጽማለች።

  6. በመርከቦች ላይ የሚፈጸመው ጥቃት መቀጠል እና የሳዑዲ ነዳጅ ማስተላለፊያ መዘጋት የፈጠረው ስጋት

    ነዳጅ ጫኝ መርከብ ባሕር ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ቅዳሜ ዕለት በሆርሙዝ የባሕረ ወሽመጥ በመርከቦች ላይ በተፈጸመ ጥቃት እና የሳዑዲ አረቢያ ዋነኛ የነዳጅ ማስተለላፊያ ቧንቧ ለጊዜው ከሥራ ውጭ በመሆኑ በዓለም የነዳጅ አቅርቦት ላይ ተጨማሪ ስጋት ተፈጥሯል።

    ባለፉት ወራት በአሜሪካ እና በኢራን ጦርነት የተነሳ የሆርሙዝ ወሽመጥ ዝግ ሆኖ በቆየበ ትጊዜ፣ የሳዑዲ አረቢያ የምሥራቅ-ምዕራብ ግዙፍ የነዳጅ መስተላለፊያ ቧንቧ በየቀኑ ከ4 እስከ 5 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ ሲያጓጉዝ ቆይቷል፤ ይህም ከዓለም አቀፍ የነዳጅ አቅርቦት ከ4 እስከ 5 በመቶ የሚሆነውን የሚሸፍን ነው።

    ቅዳሜ ዕለት በተፈጸመ የድሮን ጥቃት ምክንያት ሳዑዲ አረቢያ ይህንን ወሳኝ የነዳጅ ቧንቧ መስመር ለጊዜው ዘግታለች።

    ኢራቅ እና ሳዑዲ እንደገለጹት፣ በቧንቧው ላይ ጥቃቱ የተፈጸመው በኢራን የሚደገፉ ታጣቂ ቡድኖች ከሚንቀሳቀሱበት ኢራቅ ውስጥ ከሚገኝ ስፍራ ነው።

    በተመሳሳይም የብሪታንያ የባሕር ንግድ ትራንስፖርት ተቋም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሲያልፍ የነበረ አንድ መርከብ በተወንጫፊ መመታቱን አስታውቋል።

    በተጨማሪም የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ወደ ቀይ ባሕር መግቢያ እና መውጫ በሆነው የባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ ዙሪያ የሚገኙ የባሕር ዳርቻ አካባቢዎችን መቆጣጠራቸውን ተከትሎ ከሳዑዲ ጋር ግንኙነት ያላቸው መርከቦች በወሽመጡ እንደማልፉ አሳውቀዋል።

    ከእነዚህ ክስተቶች በኋላ የኃይል ዋጋ የበለጠ ሊጨምር ይችላል የሚለው ስጋት ተጠናክሯል፤ የዓለም ነዳጅ ዋጋ መተመኛ የሆነው የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋም በድጋሚ በአንድ በርሜል ከ100 ዶላር በላይ ደርሷል።

  7. የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ያጠላበት የብሪክስ ጉባዔ

    ፑቲን፣ ሞዲ እና ጂንፒንግ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ ፕሬዝዳንት ዢ ጂንፒንግ እና ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤሽኪያንን ጨምሮ የብሪክስ አባል አገራት መሪዎች በሕንድ የሚካሄደውን ጉባዔ እየታደሙ ይገኛሉ።

    በአሜሪካ እና የተቀሩት ምዕራባውያን አገራት መካከል ያለውን ጥምረት በመገዳደር የተመሠረተው ብሪክስ 18ኛ ጉባዔው በሕንድ፣ ኒው ደልሒ ዛሬ እና ነገ ይከናወናል።

    የብሪክስ ጉባዔ ዋነኛ ፈተና የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት እንደሆነ ተገልጿል።

    ብሪክስ ከምዕራባውያን አገራት ስብስቦች በተለየ ሁኔታ ያለውን የፖለቲካ እና ምጣኔ ሃብት አቋም የሚያንጸባርቅበት ጉባዔ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።

    የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በብሪክስ አባል አገራት መካከል ውጥረት አስከትሏል። ለምሳሌ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የኢራን ጥቃቶች ዒላማ ሆናለች።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ለምታደርሰው ጥቃት ቴህራን የአጸፋ ምላሽ የምትሰጠው በባሕረ ሰላጤው አገራት በሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት በመፈጸም ነው።

    የብሪክስ ጉባዔ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    ባለፉት ስድስት ወራት የብሪክስ ውይይቶችን ተከትሎ የጋራ መግለጫ አልወጣም። ለዚህም ምክንያቱ በአባል አገራቱ መካከል ያለው ጠንካራ አለመስማማት እንደሆነ ይገለጻል።

    በኢራን ጦርነት እና ከእስራኤል ጋር ያለውን ውዝግብ በተመለከተ አገራቱ አለመስማማታቸው ተመልክቷል።

    ሌላው ጉዳይ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በብሪክስ አባል አገራት ላይ የንግድ ታሪፍ ለመጣል መዛታቸው ነው።

    ዋይት ሀውስ አንዳንድ የብሪክስ ዕቅዶችን “ፀረ አሜሪካ” ሲል የገለጻቸው ሲሆን፤ የትራምፕን አስተዳደር ማስቆጣት ዋጋ የሚያስከፍል መሆኑም እርግጥ ነው።

  8. ዮርዳኖስ፣ ባሕሬን እና ኳታር በሳዑዲ አረቢያ ላይ የተፈጸመውን የድሮን ጥቃት አወገዙ

    የተፈጸመው የድሮን ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Planet Labs PBC

    ዮርዳኖስ፣ ባሕሬን እና ኳታር በሳዑዲ አረቢያ ላይ የተፈጸመውን የድሮን ጥቃት አውግዘዋል።

    ሳዑዲ በተፈጸመባት የድሮን ጥቃት ወሳኝ የሆነው የነዳጅ ማስተለላፊያ ቧንቧዋ ከተመታ በኋላ እንዲዘጋ አድርጋለች።

    የዮርዳኖስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፤ ጥቃቱ የሳዑዲ አረቢያን ሉዓላዊነት “ክፉኛ የሚጥስ ነው” ሲል አውግዟል።

    የተፈጸመው የድሮን ጥቃት ለሳዑዲ “የደኅንነት እና መረጋጋት” ስጋት እንደፈጠረ እንዲሁም “የዓለም አቀፍ ሕግ እና የተባበሩት መንግሥታት ስምምነት ጥሰት” እንደሆነ ተገልጿል።

    የባሕሬን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥቃቱ “የከፋ የዓለም አቀፍ ሕግ እና የተባበሩት መንግሥታት ስምምነት ጥሰት” ነው ሲል አውግዟል።

    የተፈጸመው ጥቃት “የጥሩ ጎረቤታሞችን መርሕ” የጣሰ ነው ብሏል።

    የኳታር መንግሥት “ንጹኃንን እና የምጣኔ ሃብት መሠረተ ልማትን ዒላማ ማድረግ መወገዝ ያለበት ድርጊት ነው። ግልጽ የዓለም አቀፍ መርሕ ጥሰት ነው” ብሏል።

    የድሮን ጥቃቱ የቀጣናውን ደኅንነት እና መረጋጋት የሚያውክ እንዲሁም ውጥረትን የሚያባብስ መሆኑንም ጠቅሷል።

    ጥቃቱ ከኢራን ድንበር አጠገብ በሚገኝ ግዛቷ እንደተፈጸመ ቴህራን አረጋግጣለች። ከዚሁ ጋር በተያያዘ ወታደራዊ አዛዥ ከኃላፊነት ተነስተው ምርመራ እንደተጀመረ አስታውቃለች።

    1,200 ኪሎሜትር የሚረዝመው የነዳጅ ማስተለላፊያ በዓለም ትልቋ ድፍድፍ ነዳጅ ላኪ የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ የሆርሙዝ ወሽመጥ ከተዘጋ በኋላ ምርቷን ለገበያ ለማቅረብ አማራጭ አድርጋው ነበር።

  9. ጠ/ሚ ዐቢይ እና የኢራን ፕሬዝዳንት “በቀይ ባሕር አካባቢ ባሉ ወቅታዊ ሁነቶች” ዙርያ መወያየታቸው ተገለጸ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና የኢራኑ ፕሬዚዳንት መስዑድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Abiy Ahmed Ali

    የምስሉ መግለጫ, ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና የኢራኑ ፕሬዚዳንት መስዑድ ፔዜሽኪያን

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከኢራኑ ፕሬዝዳንት መስዑድ ፔዜሽኪያን ጋር መወያየታቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው አስታወቁ።

    ሁለቱ መሪዎች በሕንድ፣ ኒው ደልሒ እየተካሄ ባለው 18ኛው የብሪክስ ጉባዔ ላይ ተገናኝተው “በቀይ ባሕር አካባቢ ባሉ ወቅታዊ ሁነቶች እና አጠቃላይ በቀጣናው የደኅንነት ሁኔታ ላይ ያተኮረ ውይይት” ማድረጋቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

    የብሪክስ ጉባዔ ዛሬ እና ነገ የሚካሄድ ይሆናል። ከጉባዔው ጎን ለጎን የተገናኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እና ፕሬዚዳንት ፔዜሽኪያን “የውይይትን አስፈላጊነት እና የቀጣናውን መረጋጋት እውን ማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ” መምከራቸው ተገልጿል።

    ሕንድ አራት ጊዜ ጉባዔው አስተናግዳለች። ዘንድሮ ብሪክስ የተመሠረተበት 20ኛ ዓመት ነው።

    ብሪክስ፤ ኢትዮጵያ፣ ብራዚል፣ ቻይና፣ ግብፅ፣ ሕንድ፣ ኢንዶኔዥያ፣ ኢራን፣ ሩሲያ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እና ደቡብ አፍሪካ ይገኙበታል።

  10. ሳዑዲ አረቢያ በተፈጸመባት የድሮን ጥቃት ወሳኝ የነዳጅ ማስተላለፊያ ቧንቧዋን ዘጋች

    የነዳጅ ማስተላለፊያ ቧንቧ

    የፎቶው ባለመብት, Copernicus Sentinel-3/Reuters

    ሳዑዲ አረቢያ በተፈጸመባት የድሮን ጥቃት ወሳኝ የሆነው የዘይት ማስተለላፊያ ቧንቧዋ ከተመታ በኋላ እንዲዘጋ አድርጋለች፤ ይህም በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ግጭት እየሰፋ መሄዱን ያሳያል እየተባለ ነው።

    ይህ ጥቃት ከኢራን ድንበር አጠገብ ከሚገኝ ግዛቷ እንደተፈጸመ ኢራን አረጋግጣ፣ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ወታደራዊ አዛዥ ከኃላፊነት ተነስቶ ምርመራ እንደተጀመረ አስታውቃለች።

    1,200 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ይህ የነዳጅ ማስተለላፊያ ቧንቧ፣ በዓለም ትልቋ ድፍድፍ ነዳጅ ላኪ የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ፣ የሆርሙዝ ወሽመጥ ከተዘጋ በኋላ ምርቷን ለገበያ ለማቅረብ አማራጭ ሆኗት ነበር።

    ይህ ክስተት፣ በኢራን የሚደገፉት የየመን ሁቲ አማጺያን ወሳኝ ድል በማግኘት የቀይ ባሕር ዳርቻዎችን በተቆጣጠሩበት ወቅት የተከሰተ ሲሆን፣ የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት ወደ ሰባተኛ ወሩ በገባበት በአሁኑ ጊዜ በዓለም የነዳጅ ዝውውርን አስተጓጉሏል።

  11. ነዳጅ የጫኑ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል በተወሰነ ሰዓት እንዲያልፉ አሜሪካ መጠየቋ ተዘገበ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚተላለፉ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ወታደራዊ ጥበቃቸው እንዲረጋገጥ በተወሰነ ሰዓት ብቻ እንዲያልፉ አሜሪካ መጠየቋን ፋይናንሽያል ታይምስ ዘገበ።

    አሜሪካ ጥያቄውን ያቀረበችው ምሽት ላይ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ላይ ኢራን የምታደርሰው ጥቃት እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ መሆኑ ተገልጿል።

    ዘገባው እንደሚያሳየው፤ ከግንቦት ጀምሮ በኦማን ባሕር ዳርቻ ማለትም በሆርሙዝ ወሽመጥ ደቡባዊ ክፍል ለማለፍ የሚሞክሩ መርከቦችን አሜሪካ በአየር ኃይሏ አማካኝነት ከለላ ስትሰጥ ቆይታለች።

    የአሜሪካ የባሕር ኃይል ትብብር ማዕከል ለባሕር ኃይል አማካሪዎች የላከውን ኢሜል የሚጠቅሰው የፋይናንሻል ታይምስ ዘገባ እንደሚያሳየው፤ ከመስከረም ጀምሮ አሜሪካ ለመርከቦች የምትሰጠው ከለላ በቀን ውስጥ ወደ ሁለት ጊዜ እንዲቀንስ ተደርጓል።

  12. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገው ጦርነት ለመስከረም 11 ጥቃት ምላሽ የተገባ ቃል መሆኑን ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት በፔንታገን የመስከረም 11 ጥቃት 25ኛ ዓመት መታሰቢያ ላይ ባደረጉት ንግግር ጥቃቱን አገራቸው አሁን ከኢራን ጋር ከገባችበት ጦርነት ጋር ለማያያዝ ሞክረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ “ዛሬ ከሩብ ምዕተ ዓመት በፊት በእነርሱ [በጥቃቱ ሰለባዎች] ስም የፈጸምነውን ቃል ኪዳን እንደገና እናድሳለን። በፍጹም መቼም አንረሳውም። ለዚህ ነው ዛሬም የምንዋጋው” ሲሉ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት ጠቅሰዋል።

    “እንደ መስከረም 11 ባሉ ቀናት አንድ አገር በእውነት ከምን እንደተሠራች እንማራለን። አሁንም ከምን እንደተሠራን እየተማርን ነው፤ ጠንካራም መሆን አለብን፣ ብልሆችም መሆን አለብን” ሲሉ አክለዋል።

    “እንዲሁም ዛሬ በተግባር የዓለም ቁጥር አንድ የሽብርተኝነት ደጋፊ ተብላ የምትገለጸው እስላማዊ ሪፐብሊክ ኢራን በፍጹም ኒውክሌር መሣሪያ እንዳታገኝ እየሠሩ ያሉትን የጦር ኃይል አባላትን እናከብራለን" ብለዋል።

    ትራምፕ ይህን በመናገር፣ የ9/11 ጥቃቶችን መታሰቢያ ከአሁኑ የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት እና ከኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ጋር በቀጥታ አያይዘውታል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴትም እንደ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሁሉ የመስከረም 11ዱን ጥቃቶች ከዛሬው ቀጣይ ግጭቶች ጋር በግልጽ ሁኔታ አያይዘዋል፤ ነገር ግን ኢራንን በስም በግልጽ አልጠቀሱም።

  13. ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና የቀድሞ ፕሬዝዳንቶች የመስከረም 11 ጥቃት መታሰቢያ ላይ

    በአሜሪካ ላይ የተፈጸመውን የመስከረም 11ዱን የሽብር ጥቃት 25ኛ ዓመት ለመዘከር አሜሪካውያን፣ ፕሬዝዳንት ትራምፕ፣ የአገሪቱ ባለሥልጣናት እና የቀድሞ ፕሬዝዳንቶች ኒው ዮርክ ውስጥ ተገኝተዋል።

    አሜሪካውያን በጥቃቱ የሞቱ ሰዎችን ለማሰብ ተሰብስበዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, አሜሪካውያን በጥቃቱ የሞቱ ሰዎችን ለማሰብ ተሰብስበዋል
    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከባለቤታቸው ጋር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከባለቤታቸው ጋር
    የኒው ዮር ክንቲባ ዞህራን ማምዳኒ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኒው ዮር ክንቲባ ዞህራን ማምዳኒ
    የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ከባለቤታቸው እና የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ከባለቤታቸው እና የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽ
    የቀድሞዎቹ ፕሬዝዳንቶች ቢል ክሊንተን እና ባራክ ኦባማ ከባለቤቶቻቸው ጋር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የቀድሞዎቹ ፕሬዝዳንቶች ቢል ክሊንተን እና ባራክ ኦባማ ከባለቤቶቻቸው ጋር
  14. ከ25 ዓመት በፊት መስከረም 11 አሜሪካ ውስጥ የተከሰተው ምንድን ነበር?

    ሐዘናቸውን የሚገልጹ ታዳሚ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ የዛሬ 25 ዓመት በኒው ዮርክ መንትያ ሕንጻዎች ላይ በተፈጸመ ጥቃት የተጀመረውን የመስከረም 11 ጥቃት መታሰቢየን እየዘከረች ነው።

    የአልቃኢዳ አባላት የጠለፏቸውን የሕዝብ ማመላለሻ አውሮፕላኖችን ከሕንጻዎች ጋር በማላተም በፈጸሟቸው የሽብር ጥቃቶች በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል።

    ይህ ክስተትም አሜሪካ እና በዓለም ዙሪያ ያሉ አጋሮቿ “ጦርነት በሽብር ላይ” የሚል ዘመቻ ከፍተው በኢራቅ እና በአፍጋኒስታን ጦርነቶች ተካሂደው የዓለምን ገጽታ የቀየረ ሆኗል።

    አሜሪካ ዛሬ አስባ በምትውለው የጥቃቱ 25ኛ ዓመት ዝክር ላይ የአገሪቱ ዜጎች፣ ከቀድሞ ፕሬዝዳንቶች እና ባለሥልጣናት ኒው ዮርክ ውስጥ ታድመዋል።

    ኒው ዮርክ ማንሃተን ውስጥ በሚገኘው የጥቃቱ መታሰቢያ ስፍራ የመጀመሪያው አውሮፕላን ከመንትያዎቹ ሕንጻዎች መካከል ከሰሜኑ ክፍል ጋር በተጋጨበት ደቂቃ በተደወለ ደወል በስፍራው የተገኙ ሰዎች የሕሊና ጸሎት አድርገዋል።

    በዕለቱ ም ንተከሰተ?

    በአውሮፓውያኑ ማክሰኞ መስከረም 11 ቀን 2001 (መስከረም 1/1994 ዓ.ም.)፣ በአሜሪካ ምሥራቃዊ ክፍል ሰማይ ላይ የሚበሩ አራት አውሮፕላኖች ከአል ቃኢዳ ጋር ግንኙነት ባላቸው አጋቾች ተጠለፉ።

    ከዚያም እነዚህን አውሮፕላኖችን እንደ አውዳሚ መሳሪያ በመጠቀም በኒው ዮርክ እና በቨርጂኒያ ከሚገኙ ታዋቂ ሕንጻዎች ላይ ተጋጩ። ሁለት አውሮፕላኖች በኒው ዮርክ የሚገኙትን የዓለም ንግድ ማዕከል መንታ ሕንጻዎችን ሲመቱ፣ ሁለተኛው ጥቃት ከመጀመሪያው 17 ደቂቃዎች በኋላ ተከሰተ።

    ሕንጻዎቹ በእሳት ተቃጠሉ፤ በሕንጻዎቹ ውስጥ የነበሩ ሰዎች መውጫ አጥተው ቀሩ፣ ኒው ዮርክ ከተማም በጭስ ተሸፈነች። ከሁለት ሰዓታት ባነሰ ጊዜ ውስጥ፣ 110 ፎቅ ያላቸው ሁለቱም ሕንጻዎች በግዙፍ የአቧራ ደመና ውስጥ ፈራርሰው ወደቁ።

    ሦስተኛው አውሮፕላን ደግሞ ከዋሽንግተን ዲሲ አቅራቢያ ከሚገኘው የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር ዋና መሥሪያ ቤት ፔንታገን ምዕራባዊ ክፍል ጋር ተጋጨ።

    አራተኛው አውሮፕላን ደግሞ ተሳፋሪዎች አጋቾቹን ለመቆጣጠር ከሞከሩ በኋላ በፔንሲልቬኒያ ግዛት ውስጥ ባለ አንድ ሜዳ ላይ ተከሰከሰ። አጋቾቹ በዚህ አውሮፕላን ዋሽንግተንን የሚገኘውን የአሜሪካ ምክር ቤት ሕንጻ - ካፒቶል ሂልን ለማጥቃት አስበው እንደነበር ይታመናል።

    በእነዚህ ጥቃቶች በአጠቃላይ 2,977 ሰዎች ሕይወታቸውን ያጡ ሲሆን፣ ይህም 19ኙን አጋቾች አይጨምርም።

    አብዛኞቹ ሟቾች በኒው ዮርክ ውስጥ የነበሩ ሲሆን፣ 441 የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ሕይወት ለማዳን ሲጥሩ ሕይወታቸውን አጥተዋል። ይህም በአሜሪካ ታሪክ በአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ላይ የደረሰ ከፍተኛው የሞት ጉዳት ነው።

  15. የሁቲዎች ይዞታ በቀይ ባሕር ላይ መጠናከር በነዳጅ እንቅስቃሴ ላይ ያለው ተጽእኖ

    ነዳጅ ጫኝ መርከብ እና የሳዑዲ ካርታ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ እና ኢራን እያካሄዱት ባለው ጦርነት የሆርሙዝ ወሽመጥ ለረጅም ጊዜ ከተዘጋ በኋላ፣ ሳዑዲ አረቢያ የነዳጅ ኤክስፖርቷን በቀይ ባሕር በኩል ለማጓጓዝ ግዛቷን ከምሥራቅ ወደ ምዕራብ የሚያቋርጠውን የነዳጅ ዘይት ቧንቧን እየተጠቀመች ነው።

    ይህንንም ተከትሎ ከፍተኛ ነዳጅ ዘይት አምራች የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ በኩል ይላክ ከነበረው ድፍድፍ ነዳጅ እስከ 70 በመቶ የሚደርሰውን ወደ ቀይ ባሕር ወደቧ ያንቡ በቧንቧ በማስተለላፍ አቅጣጫውን ቀይራ ነበር።

    በዚህ የነዳጅ ዘይት ማስተላለፊያ ቧንቧ አማካኝነት፣ ሳዑዲ አረቢያ ነዳጅ ወደ የእስያ አገራት ለመላክ፣ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በቀይ ባሕር በኩል ወደ ደቡብ አቅጣጫ በመሄድ በባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ በኩል ያቋረጡ ነበር።

    ነገር ግን፣ የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ባለፉት ቀናት በቀይ ባሕር ዳርቻ የሚገኙ የየመን ወደቦችን ዛሬ አርብ ደግሞ ፔሪም ወይም ማዩን የተባለችውን ደሴት በመቆጣጠራቸው፣ ወሽመጡን ለሁለት ከምትከፍለው ከዚች ደሴት ላይ ሆነው ከሳዑዲ የሚነሱ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በማገድ የነዳጅ ንግዷን ሊያደናቅፉ ይችላል።

    ሁቲዎች ከዚህ ቀደም እንደሚሉት፣ ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የተያያዙ መርከቦችን ካልሆኑ በቀር በበዓለም አቀፍ የመርከብ ጉዞ ላይ ምንም ስጋት አይፈጥሩም።

    ባለፈው ነሐሴ ወር ሁቲዎች በቀይ ባሕር በኩል በሚያልፉ ከሳዑዲ በሚነሱ መርከቦች ላይ በጣሉት እገዳ ምክንያት በርካታ መርከቦች ወደ ደቡብ አቅጣጫ እንዳያልፉ በመከልከላቸው ለመመለስ ተገድደዋል።

    ካርታ
  16. የሁቲ ታጣቂዎች በባብ ኤል መንደብ ላይ የምትገኝ ወሳኝ ደሴትን ተቆጣጠሩ

    የሁቲ ታጣቂዎች

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    ዓለም አቀፍ እውቅና ያለው የየመን መንግሥት ኃይሎች ካፈገፈጉ ከኋላ በወሳኙ የባሕር መተለላፊያ ባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ መግቢያ ላይ የምትገኘው ስትራቴጂካዊቷ ማዩን (ፕሪም) ደሴት በሁቲዎች ቁጥጥር ስር እንደዋለች ሪፖርቶች አመለከቱ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል የየመን መንግሥት ምንጮች ጠቅሶ እንደዘገበው፣ የአገሪቱ መንግሥት ኃይሎች ከማዩን ደሴት አፈግፍገዋል።

    አንዳንዴ “የባብ ኤል መንደብ” ተብላ የምትጠራው ማዩን ወይም ፕሪም ደሴት፣ ከፍተኛ የንግድ መርከቦች በሚንቀሳቀሱበት የባሕር ወሽመጥ መሃል ላይ ትገኛለች፤ በዚህም ደሴቷ መተላለፊያውን ለሁለት የምትከፍል ወሳኝ ቦታ ናት።

    የሁቲ ታጣቂዎች በቁልፍ የመንግሥት ይዞታዎች ላይ ጥቃት ከከፈቱበት ካለፈው ሳምንት ወዲህ በቀይ ባሕር ዳርቻ ላይ የሚገኙትን ሞካ እና ዱባብ የተባሉ የወደብ ከተሞችን ተቆጣጥረዋል።

    ይህም ሁቲዎች በጠላትነት ለፈረጇት ለሳዑዲ አረቢያ የዘይት ኤክስፖርት እጅግ ወሳኝ የሆነውን የባብ ኤል መንደብ ወሽመጥን ታጣቂዎቹ ለመቆጣጠር ያስችላቸዋል።

    በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች፣ በሰሜናዊ የመን ሰፊ አካባቢዎችን የሚቆጣጠሩ ሲሆን፣ ባለፈው ሳምንት በሳዑዲ አረቢያ በሚደገፉት የየመን መንግሥት ኃይሎች ላይ ሰፊ ወታደራዊ ዘመቻ ከፍተው እየገሰገሱ ነው።

    በሌላ በኩል፣ ከሁቲዎች ጋር ግንኙነት ያላቸው መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት፣ ሳዑዲ አረቢያ በየመን ላይ በርካታ የአየር ድብደባዎችን ፈጽማለች።

    በቅርብ ጊዜ በተፈጸሙት ጥቃቶችም ሁቲዎች ሐሙስ ዕለት በቁጥጥራቸው ስር ያስገቧትን የሞካ አየር ማረፊያን ሁለት ጊዜ ዒላማ አድርጋለች ብለዋል።

  17. አሜሪካ ከየመን ሁቲዎች ጋር ለተፋጠጠችው ሳዑዲ አረቢያ ከ100 በላይ አማካሪዎችን ላከች

    ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የሁቲ ታጣቂዎች በየመን ውስጥ ቁልፍ ቦታዎችን እየተቆጣጠሩ በሳዑዲ ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት እያጠናከሩ ባሉበት በአሁኑ ጊዜ አሜሪካ የሳዑዲን ሠራዊት የሚደግፉ ከ100 በላይ አማካሪዎችን በአገሪቱ ውስጥ ማሰማራቷ ተዘገበ።

    ሲኤንኤን ቴሌቪዥን በጉዳዩ ላይ መረጃ ያላቸው አምስት ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ከ100 በላይ አሜሪካውያን አማካሪዎች በሳዑዲ አረቢያ ውስጥ እየሠሩ ይገኛሉ። አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ደግሞ በተልዕኮው ውስጥ የተሰማሩ ሠራተኞች ቁጥር ወደ 200 የሚጠጋ መሆኑን ገልጿል።

    ይህ የአሜሪካ ወታደራዊ አማካሪዎች ድጋፍ ስምሪት የተሰማው የሳዑዲ መንግሥቱ ከየመኑ የሁቲ ታጣቂዎች የሚፈጸምበት ጥቃት እየተጠናከረ በመጣበት ጊዜ ነው።

    እነዚህ አማካሪዎች የሁቲዎችን እንቅስቃሴ ለመግታት በቅርቡ በተቋቋመ የጋራ የዕዝ ማዕከል ውስጥ እያገለገሉ መሆናቸው ተነግሯል። ይህ ማዕከል የተቋቋመው ኢራን ለየመኑ ቡድን የምታደርገውን ድጋፍ እያሳደገች እንደሆነ የሚጠቁሙ ምልክቶች ከታዩ በኋላ ነው። ይህ ቡድን ወደ ሳዑዲ ግዛት ሚሳይሎች እና ድሮኖችን ሲያስወነጭፍ ቆይቷል።

    የአሜሪካ ድጋፍ የወታደራዊ መረጃ ትንተናን እና የሳዑዲ አዛዦች በጦር ሜዳ ላይ የሚደርጉት እንቅስቃሴን በቀጥታ እንዲከታተሉ የሚያስችላቸውን ቴክኖሎጂ እንደሚያካትት ተዘግቧል። እንዲሁም አሜሪካውያኑ ዒላማዎችን ለመለየት እና ለመገምገም የሚረዳ መረጃ እያቀረቡ መሆኑም ተገልጿል።

    ምንም እንኳን አሜሪካ ከሳዑዲ ጋር ያላት ትብብር ትብብሩ እየተጠናከረ ቢሆንም፣ ወታደሮቿ በጥቃቶች ውስጥ በቀጥታ አይሳተፉም።

    ተልዕኮው በዋናነት የሳዑዲ ኃይሎች የዕቅድ ዝግጅት፣ የቅንጅት ሥራ እና የአፈጻጸም ብቃታቸውን ማሳደግ ላይ ያተኮረ ነው። ምንጮች ስምሪቱ በሁለቱ አገራት መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየው ወታደራዊ አጋርነትን የማጠናከር አካል እንደሆነ ገልጸዋል።

    በአሁኑ ጊዜ የየመኑ ታጣቂ ቡድን ጥቃት እየተጠናከረ በሳዑዲ የድንበር አካባቢ ጥቃት እና ውጊያዎች እየተባባሱ፣ ቀይ ባሕርን ከኤደን ባሕረ ሰላጤ ጋር የሚያገናኘው ጠባብ የባሕር መተላለፊያ የባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ ላይ የደኅንነት ስጋት እየተጨመረ ነው።

  18. የየመን የባሕር ዳርቻዎችን በመቆጣጠር በቀይ ባሕር ላይ ስጋት የደቀኑት ሁቲዎች እና የኢራን ጥሪ

    የሁቲ ተዋጊዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ወደ ቀይ ባሕር በሚስገባው ወሳኙ የባብ ኤል መንደብ መተላላፊያ አቅራቢያ የሚገኙ ወደቦችን እየተቆጣጠሩ ባሉበት በአሁኑ ወቅት ኢራን ድርድር እንዲጀመር ጥሪ አቀረበች።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአገሪቱ አጋር የሆኑት ሁቲ ታጣቂዎች በየመን ውስጥ እያካሄዱት ባለው ጦርነት እየታየ ያለውን ለውጥ በመጥቀስ ባወጣው መግለጫ የመን ላይ የተጣለው ወታደራዊ ከበባ እንዲነሳ እና ድርድር እንዲጀመር ጥሪ አቅርቧል።

    በኢራን መንግሥታዊ የዜና ወኪል ኢርና በኩል ይፋ የተደረገው መግለጫ፣ “የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ፣ የሙስሊሙን ሕዝብ ጥቅም መጠበቅ አስፈላጊነትን እያሳሰበች፣...በአሜሪካ ድጋፍ እየተስፋፋ ያለውን የጽዮናዊው ሥርዓት ጥቃት እና መስፋፋት በምትጋፈጥበት ወቅት፣ የየመን ችግር በከበባ እና በወታደራዊ ጥቃት ሊፈታ እንደማይችል ታሳስባለች” ብሏል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጨምሮም የየመን ኃይሎች “በተስማሙበት የሰላም ፍኖተ ካርታ መሠረት ውይይቱ በአስቸኳይ እንዲቀጥል እና ስምምነት የተደረሰባቸው ጉዳዮች መተግበራቸው” አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥቶ፣ ኢራንም “ማንኛውንም ጥረት ለመደገፍ ዝግጁ ናት” ብሏል።

    ይህ የኢራን መግለጫ የወጣው፣ ሁቲዎች በየመን የሚገኘውን የሞካ ወደብን ጨምሮ አንዳንድ የአገሪቱን አካባቢው በመቆጣጠር እየገሰገሱ እና በሳዑዲ አረቢያ የሚደገፉት የየመን መንግሥት ኃይሎች እያፈገፈጉ መሆናቸው እየተዘገበ ባለበት ጊዜ ነው።

    ትናንት ሐሙስ ጳጉሜ 5 በሳዑዲ አረቢያ ድጋፍ የሚያገኙት የየመን ኃይሎች እና አጋሮቻቸው ዱባብ ከተባለችው ሌላ ወደብ መውጣታቸውም ተዘግቧል።

    የሞካ ወደብ በሁቲዎች እጅ መውደቁ፣ በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች የነዳጅ እና የሸቀጦች ዋነኛ መተላለፊያ በሆነው የቀይ ባሕር መስመር ላይ ያላቸውን ቁጥጥር ያጠናክራል።

    ይህ ወደብ ቀይ ባሕርን ከሕንድ ውቅያኖስ በሚያገናኘው የባብ ኤል መንደብ ባሕር ወሽመጥ አካባቢ የሚገኝ በመሆኑ ለባሕር ላይ እንቅስቃሴ ወሳኝ ነው።

    በተጨማሪም የፈረንሳይ ዜና ወኪል ኤኤፍፒ ሐሙስ ዕለት አንድ ወታደራዊ ምንጭን ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ሁቲዎች “ሮኬቶች እና ታጣቂዎችን በጫኑ ጀልባዎች በመጠቀም በፈጸሙት ወረራ” በደቡባዊ ቀይ ባሕር የሚገኘውን ዛቅር የተባለውን ደሴት ተቆጣጥረዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የሁቲ ታጣቂዎች እንደ ዋነኛ ጠላት የሚመለከቷት የሳዑዲ አረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፋይሳል ቢን ፋርሃን ከኢራኑ አቻቸው አባስ አራግቺ ጋር በየመን ስላለው ሁኔታ በስልክ ተወያይተዋል።

    ሳዑዲ ዓለም አቀፍ እውቅና ያለውን የየመን መንግሥት እና ሌሎች ፀረ ሁቲ ታጣቂዎችን የምትደግፍ ሲሆን፣ ኢራን ደግሞ የሁቲዎች አጋር መሆኗ ይታወቃል።

    በውጊያ የወደመ መኪና

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  19. የየመን ሁቲ ታጣቂዎች ሞካ የተባለ ወደብን መቆጣጠራቸው ተዘገበ

    የሁቲ ታጣቂዎች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በሳዑዲ ከሚደገፈው የየመን መንግሥት ጋር ከባድ ውጊያ ውስጥ የሚገኙት የሁቲ ታጣቂዎች ሞካ የተባለውን በቀይ ባሕር ላይ የምትገኘው ሞካ የተባለችውን ወደብ መቆጣጠራቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል የየመን መንግሥት ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ዘገበ።

    እየተካሄዱ ባሉ ውጊያዎች ሁቲዎቹ በቀይ ባሕር ላይ የሚገኙ ስትራቴጂያዊ ወደቦችን ለመቆጣጠር እየጣሩ ሲሆን፣ ይህም መርከቦች ከሕንድ ውቅያኖስ ወደ ቀይ ባሕር የሚገቡበትን ወሳኙን የመርከቦች መተላለፊያ በር ባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ ላይ ላይ ያላቸውን ቁጥጥር የበለጠ እንዲያጠናክሩ ያስችላቸዋል።

    ከዚህ ቀደም በሳዑዲ አረቢያ የሚደገፉ ኃይሎች እና በሁቲዎች መካከል በየመን የተፈጠረው ከባድ ግጭት፣ ጦርነቱ የበለጠ እንዳይሰፋ ስጋት አስከትሎ ነበር።

    ሁቲዎች በመርከቦቿ ላይ በጣሉት የእንቅስቃሴ ዕገዳ እና በመሠረተ ልማቶቿ ላይ ለተፈፀሙ ጥቃቶች ምላሽ ሳዑዲ በየመን ውስጥ በርካታ ቦታዎችን በአየር ደብድባለች።

    በሁቲዎች ጥቃት ምክንያት ውጥረት እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ፣ በደቡብ ምዕራብ ሳዑዲ አረቢያ በምትገኘው የካሚስ ሙሻይት ከተማ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁ ተሰምቷል።

  20. የአሜሪካ እና የኢራን ጦርነት እንዴት ሊቆም ይችላል?

    ቴህራን ውስጥ የጦርነቱ ቅስቀሳ ግዙፍ ፖስተር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ እና የኢራንን ጦርነት ለማስቆም ተጨባጭ የሆነ ስምምነት ላይ ይደረሳል የሚለው ተስፋ ደብዝዞ ይታያል፤ ሁለቱ ተፋላሚ ወገኖች ጥቃቶችን በመፈጸም እና የማይለሳለሱ አቋሞችን በማንጸባረቅ ላይ ናቸው።

    እነዚህ ጥቃቶች የተከሰቱት አሜሪካ ወደ አዲስ ምዕራፍ እየገባች መሆኗን ከገለጸች ከቀናት በኋላ ነው፤ በኢራን እና ከኢራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራት ላይ ያነጣጠረ ሰፊ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ይፋ አድርጋለች።

    የአሜሪካ ዓላማ ኢራንን ወደ ድርድር ማምጣት እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የምትፈጽማቸውን ጥቃቶች እንድታቆም ማስገደድ ነበር። ይህ ለዓለም ንግድ በጣም ወሳኝ የሆነው የመርከብ መተላለፊያ መስመር፣ አሜሪካ እና እስራኤል ግጭቱን ባለፈው የካቲት ወር ከጀመሩ ወዲህ በተግባር ተዘግቶ ቆይቷል።

    ሁለቱ ወገኖች በሰኔ ወር የፈረሙት እና በ60 ቀናት ውስጥ ወደ ቋሚ የተኩስ አቁም እና የሰላም ስምምነት ሊያመራ የነበረው የመግባቢያ ሰነድ ጊዜው አልፏል።

    ግጭቱ ወደ ሰባተኛ ወሩ ሲገባ፣ በቀጣይ እንዴት ሊቀጥል ይችላል የሚለውን በተመለከተ ሦስት ባለሙያዎች አስተያየት ሰጥተዋል። ዝርዝሩን እዚህ ያንብቡ የአሜሪካ እና የኢራን ጦርነት እንዴት ሊቆም ይችላል? የሦስት ተንታኞች ዕይታ