የኢራን አብዮታዊ ዘብ ኩዌት በሚገኝ የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈር ላይ ጉዳት ማድረሱን ገለጸ
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ዛሬ ሐሙስ ጠዋት ኩዌት ውስጥ በሚገኘው አሊ አል-ሳሌም የአሜሪካ አየር ኃይል ጦር ሰፈር ላይ ፈጸምኩት ባለው ጥቃት ጉዳት ማድረሱን አስታወቀ።
በጥቃቱ የእሳት ቃጠሎ ተነስቶ ሁለት የድሮኖች መጠለያዎች እንዲሁም ለወታደራዊ አውሮፕላኖች እና ሄሊኮፕተሮች የሚውል የነዳጅ ማከማቻ እንደወደመ ገልጿል።
ነገር ግን እስካሁን ይህን የአብዮታዊ ዘቡን ጥቃት እና አደረስኩት ያለውን ጉዳት በተመለከተ ከኩዌትም ሆነ ከአሜሪካ ባለሥልጣት ወይም ከገለልተኛ ወገን የተሰጠ ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ የለም።
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ጥቃቱ “ዘመቻ ናስር 2” የተባለ መሆኑን እና የአሜሪካ ኃይሎች በቀጣናው ለመኖራቸው የተሰጠ ምላሽ መሆኑን ገልጿል።
ነገር ግን ለጥቃቱ ጥቅም ላይ ስለዋሉት የጦር መሳሪያ ዓይነቶች፣ ስለደረሰው የውድመት መጠን ወይም በሰው ላይ ስለደረሰ ጉዳት ምንም ዝርዝር መረጃ አልሰጠም።
አብዮታዊ ዘቡ በኩዌት ሰሜን ምዕራብ ክፍል ውስጥ በሚገኘው የአሜሪካ ኃይሎች በሚገኙበት አሊ አል-ሳሌም አየር ኃይል ሰፈር ላይ ቀደም ሲል ጥቃት ፈጽሞ በአሜሪካ መገልገያዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሱን ገልጾ ነበር።
ኢራን በአሜሪካ ለሚፈጸምባት ጥቃት በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠራዊት ሰፈሮች ላይ ተደጋጋሚ የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው።
በተለይም በዮርዳኖስ፣ ኩዌት እና ባህሬን ውስጥ ያሉት የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ከባድ ጉዳት ያደረሱ ጥቃቶች እንደተፈጸሙባቸው ተዘግቧል።