በሱዳን ጦርነት ኢትዮጵያዊያንን ጨምሮ የተለያዩ አገራት ቅጥረኛ ተዋጊዎች እንዳሉ ተነገረ

በሱዳን እየተካሄደ ባለው የእርስ በርስ ጦርነት ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ አገራት የመጡ ቅጥረኛ ተዋጊዎች እንደሚሳተፉ የሱዳን ባለሥልጣናት ተናገሩ። የሱዳን ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግም የሱዳን ጦር ኃይልን በመቀናቀን ከሚዋጋው የፈጥኖ ደራሽ ኃይል ጋር ተሰልፈው ሲዋጉ ነበር ባላቸው ከ120 በላይ የውጭ አገር ቅጥረኛ ወታደሮች ላይ ክስ መሥርቷል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በደቡብ አፍሪካ በደረሰ የመኪና አደጋ ወደ ትምህርት ቤት የሚጓዙ 13 ሕፃናት ሕይወታቸው አለፈ

    በደቡብ አፍሪካዋ ጆሀንስበርግ ከተማ የትምህርት ቤት ሚኒባስ ከጭነት መኪና ጋር ተጋጭቶ 13 ሕፃናት ሕይወታቸው ማለፉ ተሰምቷል።

    በአከባቢው ሰዓት አቆጣጠር ሰኞ ጥዋት 1፡00 አደጋው መድረሱን ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    11 ሕፃናት አደጋው በደረሰበት አካባቢ ሲሞቱ ሁለቱ ደግሞ በኋላ ላይ ሕይወታቸው ማለፉ ታውቋል። ሁለት ተጨማሪ ሕፃናት በአስጊ ሁኔታ ላይ እንዳሉም ተዘግቧል።

    ሁለት መኪናዎችን ደርቦ ለማለፍ ሲሞክር የነበረው የሚኒባስ ሹፌር ከጭነት መኪና ጋር መጋጨቱን የፖሊስ ቃል አቀባይ ማቬላ ማሶንዶ ተናግረዋል።

    የሚኒባሱ ሹፌር በሆስፒታል ሕክምና እያገኘ እንደሆነ የጉዋቴንግ ግዛት ትምህርት ቢሮ ያስታወቀ ሲሆን የጭነት መኪና ሹፌር ሁኔታ እስካሁን አልታወቀም።

    በደቡብ አፍሪካ በመኪና አደጋ ምክንያት ባለፈው የአውሮፓውያኑ ዓመት 2025 ከ11 ሺህ በላይ ሰዎች መሞታቸውን መረጃዎች ያሳያሉ።

    የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎዛ የሰኞው አደጋ “በጣም የሚያሳዝን ነው” ብለዋል።

  2. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኖቤል ሽልማት ባለማግኘታቸው ለኖርዌይ ደብዳቤ ጻፉ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ የተለያዩ ጦርነቶችን ማስቆማቸውን የሚገልጸውን አቋማቸውን በድጋሚ በማንጸባረቅ ከዚህ በኋላ ለሰላም ብቻ ብለው የሚያደርጉት ነገር እንደሌለ ለኖርዌይ ጠቅላይ ሚኒስትር በጻፉት ደብዳቤ ገለጹ።

    የኖቤል የሰላም ሽልማትን ባለማግኘታቸው ቅሬታቸውን የገለጹት ትራምፕ “8 ጦርነቶችን ባስቀርም አገርዎ የኖቤል የሰላም ሽልማትን ላለመስጠት በመወሰኗ፤ ከዚህ በኋላ ለሰላም ብቻ የመሥራት ግዴታ እንደሌለብኝ ይሰማኛል” ብለዋል።

    የኖርዌይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዮናስ ጋህር ስቶር ለትራምፕ ደብዳቤ በሰጡት ምላሽ የኖቤል የሰላም ሽልማት ኖርዌይ እንደ አገር የምትሰጠው ሳይሆን የገለልተኛ ኮሚቴ ምርጫ ነው ብለዋል።

    ትራምፕ ስምንት ጦርነቶችን አስቁሚያለሁ ማለታቸው ከዚህ በፊት ጥያቄ የቀረበበት እና የተተቸ ጉዳይ መሆኑ ይታወቃል። ነገር ግን ይህንን ጉዳይ በተደጋጋሚ እየጠቀሱት ነው።

    በኢትዮጵያ እና ግብፅ መካከል ሊኖር የሚችል ግጭትን ጨምሮ ጽፈህት ቤታቸው ፕሬዝዳንቱ አስቆሙ ያለውን የእስራኤል እና ሐማስ፣ የኢራን እና የእስራኤል፣ የፓኪስታን እና የሕንድ፣ የሩዋንዳ እና ዲሞክራቲክ ኮንጎ፣ የታይላንድ እና የካምቦዲያ፣ የአርሜኒያ እና የአዘርባጃን እንዲሁም የሰርቢያን እና ኮሶቮን ጦርነችን ዘርዝሯል።

    በኢትዮጵያ እና በግብፅ መካከል ጦርነት ያልነበረ ከመሆኑ በተጨማሪ ከተጠቀሱት ሌሎች “ጦርነቶች” አብዛኞቹ ለጥቂት ቀናት የተካሄዱ ናቸው።

  3. አሜሪካ ኃይሏ ከዓለም አቀፍ ሕግ የበለጠ ዋጋ እንዳለው ታምናለች - የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፤ አሜሪካ ያለ ምንም ተጠያቂነት እየተንቀሳቀሰች ነው፤ ኃይሏም ከዓለም አቀፍ ሕግ የበለጠ ዋጋ እንዳለው ታምናለች ሲሉ ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ዋና ጸኃፊው ከቢቢሲ ሬዲዮ 4 ‘ቱዴይ’ ፕሮግራም ላይ በነበራቸው ቃለ መጠይቅ፤ አሜሪካ የባለብዙ ወገን መፍትሔዎች ጥቅም አልባ ናቸው የሚል "ግልጽ ድምዳሜ” ይዛለች ሲሉ ተችተዋል።

    በአሁኑ ወቅት ያለው የዋሽንግተን ፖሊሲ፤ "የአሜሪካን ኃይል እና ተጽእኖ መጠቀም፤ አልፎ አልፎ ደግሞ ዓለም አቀፍ ሕግችን ማክበር" የሚል ነው ብለዋል።

    ጉቴሬዝ ይህንን አስተያየት የሰጡት፤ አሜሪካ ቬንዙዌላ ውስጥ ባካሄደችው ዘመቻ የቀድሞውን ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮን ከያዘች ከሳምንታት በኋላ እንዲሁም ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን ለመጠቅለል ደጋግመው እየዛቱ ባለበት ወቅት ነው።

    እንደ የአባል አገራት እኩልነት ያሉ የተባበሩት መንግሥታት ምስረታ መርሆዎች በአሁን ሰዓት በአደጋ ላይ ናቸው ብለው እንደሚያምኑ ጉቴሬዝ ገልጸዋል።

    ከዚህ ቀደም ፕሬዝዳንት ትራምፕ በተባበሩት መንግሥታት ላይ ጠንካራ ትችቶችን ሲያሰሙ ቆይተዋል።

    ባለፈው መስከረም በተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ባደረጉት ንግግሩም የድርጅቱ መኖር ዓላማ ጥያቄ አንስተዋል። "ሰባት ሊቋጩ የማይችሉ ጦርነቶችን" ለብቻቸው ማቆማቸውን የተናገሩት ትራምፕ፤ የተባበሩት መንግሥታት ግን "በየትኛውም [ግጭት የማስቆም ጥረት] ውስጥ ለመርዳት እንኳ አልሞከረም" ሲሉ ተደምጠዋል።

    "ኋላ ላይ የተባበሩት መንግሥታት ለእኛ እንዳልነበረ ተረዳሁ" ሲሉም በኒውዮርኩ ስብሰባ ላይ ተናግረዋል።

    ይህ ጉዳይ የተነሳላቸው ጉቴሬዝ፤ የሚመሩት ድርጅት አባል አገራት በተባበሩት መንግሥታት ቻርተር ላይ ለተዘረዘሩ ዓለም አቀፍ ሕጎች እንዲገዙ የማድረግ ፈተና እንደገጠመው አምነዋል።

    ድርጅቱ ዋና ዋና ዓለም አቀፍ ግጭቶችን ለመፍታት "በከፍተኛ ሁኔታ ተሳታፊ" እንደነበረ በአጽንኦት ያነሱት ጉቴሬዝ፤ "ነገር ግን የተባበሩት መንግሥታት የማስገደድ አቅም የለውም፤ ይልቁንም ትልልቅ ኃያላን አገራት የበለጠ ጠንካራ የማስገደድ አቅም አላቸው" ብለዋል።

    ይህ የበለጠ የማስገደድ አቅም ለግጭቶች ትክክለኛ እና ዘላቂ መፍትሔዎችን ለማምጣት እየዋለ ነው ወይስ ለጊዜያዊ መፍትሔዎች ብቻ ነው? ሲሉም ጠቅዋል። "በሁለቱ ነገሮች መካከል ትልቅ ልዩነት አለ" ብለዋል።

    አክለውም፤ የመንግሥታቱ ድርጅት 193ቱ አባል አገራት የሚገጥሟቸውን "ከፍተና ችግሮች እና ተግዳሮቶች" ለመወጣት ማሻሻያ እንደሚያስፈልገው ተናግረዋል።

    ዋና ጸኃፊው፤ "የሕግ የበላይነት በኃይል የበላይነት መተካት አለበት ብለው የሚያምኑ አሉ" ሲሉም ወቀሳቸውን አሰምተዋል።

  4. የቻይና የሕዝብ ብዛት በከፍተኛ ሁኔታ አሽቆለቆለ

    በዓለም በሕዝብ ብዛት ቀዳሚ የነበረችው ቻይና ያላት የወሊድ መጠን ለአራተኛ ተከታታይ ዓመት በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን የአገሪቱ መንግሥት መረጃ አመለከተ።

    በተጠናቀቀው የአውሮፓውያን ዓመት የሕዝብ ቁጥሯ በከፍተኛ ሁኔታ በማሽቆልቆል የአገሪቱ ገዢ ኮሚዩኒስት ፓርቲ ሥልጣን ከያዘበት ከ1949 ወዲህ ከፍተኛው ቅናሽ ሆኖ ተመዝግቧል።

    ለዓመታት ስትተገብር የቆየችውን የአንድ ልጅ ፖሊሲ በማንሳት ለወላጆች ማበረታቻ እየሰጠች ያለችው ቻይና በዕድሜ የገፉ ዜጎቿ ቁጥር እየጨመረ ነው። ምጣኔ ሀብቷ እየተቀዛቀዘ ከመሆኑም ጋር በተያያዘ ወጣቶቿ አግብተው ልጆች እንዲወልዱ እያበረታታች ነው።

    ቻይና ከሦስት ዓመት በታች የሆኑ ልጆች ላሏቸው ወላጆች በእያንዳንዳቸው ወደ 500 ዶላር የምትስጥ ሲሆን፣ አንዳንድ ግዛቶችም ተጨማሪ ክፍያዎችን በመፈጸም እና የተራዘመ የወሊድ ፈቃድ በመስጠት ወላጆችን ያበረታታሉ።

    ቻይና ልጆችን ለማሳደግ ከፍተኛ ወጪ ከሚወጣባቸው አገራት መካከል አንዷ በመሆኗ በዓለም ላይ ዝቅተኛ የወሊድ መጠን ካላቸው አገራት አንዷ ናት።

    የተባበሩት መንግሥታት ባለሙያዎች የቻይና ሕዝብ ቁጥር እየቀነሰ እንደሚቀጥል እና በአውሮፓውያኑ 2100 የሕዝብ ብዛቷ ከግማሽ በላይ ሊቀንስ ይችላል ብለው ያምናሉ።

    ይህ የአዛውንቶች መብዛት እና የሕዝብ ቁጥር ማሽቆልቆል በአገሪቱ ምጣኔ ሀብት ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ይኖረዋል ተብሎ ተስግቷል።

    ለረጅም ዘመናት በዓለም በሕዝብ ብዛት ቀዳሚ የነበረችው ቻይና የሕዝብ ቁጥሯ በማሽቆልቆሉ ባለፉት ዓመታት ሕንድ የመጀመሪያውን ቦታ ይዛለች።

  5. “አውሮፓን ማስገደድ አይቻልም”- የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር

    የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሜቴ ፍሬድሪክሰን “አውሮፓን ማስገደድ አይቻልም” ሲሉ ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛቻ ምላሽ ሰጡ።

    ትራምፕ፤ አሜሪካ ግሪንላንድን ለመጠቅለል የምታደርገውን ሙከራ የሚያሰናክሉ ከሆነ ስምንት የአውሮፓ አገራት ታሪፍ እንደሚጣልባቸው ዝተዋል።

    ትራምፕ ከፊል ራስ ገዝ የሆነችው የዴንማርክ ግዛት ግሪንላንድን እንደሚጠቀልሉ መግለጻቸውን ተከትሎ፤ ዕቅዳቸውን የማይቀበሉ አገራት ላይ ታሪፍ እንደሚጥሉ ማስታወቃቸው በአውሮፓ ውዝግብ አስከትሏል።

    ታሪፍ ይጣልባቸዋል የተባሉት ስምንት አገራት በጋራ ባወጡት መግለጫ የትራምፕ ዕቅድ “አደገኛ አካሄድ ነው” ሲሉ ኮንነዋል።

    “ታሪፍ ለመጣል መዛት ግንኙነትን ያሻክራል። ዴንማርክን እንዲሁም የግሪንላንድ ሕዝብን ሙሉ በሙሉ እንደግፋለን” ብለዋል።

    የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃልኪዳን (ኔቶ) አባል አገራቱ “የአርክቲክን ደኅንነት ለመጠበቅ ቁርጠኛ ነን” ሲሉም አቋማቸውን ገልጸዋል።

    የአሜሪካ አጋር የሆኑት ዴንማርክ፣ ፊንላንድ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ኔዘርላንድስ፣ ኖርዌይ፣ ስዊድን እና ዩናይትድ ኪንግደም በጋራ ካወጡት መግለጫ ባሻገር የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር በተናጠል ባስተላለፉት መልዕክት የትራምፕን ዕቅድ አጥብቀው አውግዘዋል።

    በፌስቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍም “ግጭት የፈለግነው እኛ አይደለንም። እኛ ትብብር ነው የምንሻው። የተቀረው አውሮፓ ስለደገፈን ደስተኛ ነኝ። አውሮፓን ማስገደድ አይቻልም” ብለዋል።

  6. በግሪንላንድ ጉዳይ ከአሜሪካ ጋር የተፋጠጡት የአውሮፓ መሪዎች ለአጸፋ ምላሽ እየተዘጋጁ መሆኑ ተገለጸ

    የአውሮፓ ኅብረት አምባሳደሮች፤ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በአውሮፓ አጋሮች ላይ ሊጥሉ ያሰቡትን የታሪፍ ዕቅድ እንዲተዉ ለማሳመን የሚያደርጉትን ጥረት ለማጠናከር ስምምነት ላይ መድረሳቸውን አስታወቁ።

    ታሪፉ ተግባራዊ የሚሆን ከሆነ ኅብረቱ የአጸፋ እርምጃ ለመውሰድ እየተዘጋጀ መሆኑን እሑድ ዕለት እንደተናገሩ የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘግቧል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቅዳሜ ዕለት በሰጡት መግለጫ፤ አሜሪካ ግሪንላንድን እንድትገዛ እስካልተፈቀደላት ድረስ ከአውሮፓውያኑ የካቲት 1 ጀምሮ በአውሮፓ ኅብረት አባላት በሆኑ አገራት ላይ ተከታታይ የታሪፍ ጭማሪዎችን እንደሚያደርጉ ዝተዋል።

    የታሪፍ ጭማሪ ይደረግባቸዋል የተባሉት አገራት ዴንማርክ፣ ስዊድን፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ኔዘርላንድስ እና ፊንላንድ ናቸው።

    የአውሮፓ ኅብረት አገራት በበኩላቸው እርምጃውን በማስፈራራት የማስገደድ ዘዴ እንደሆነ በመግለጽ ኮንነውታል።

    የኅብረቱ መሪዎች፤ አሜሪካ ላይ እርምጃ ለመውሰድ ምን ዓይነት አማራጮች እንዳሏቸው ለመወያየት ለመጪው ሐሙስ አስቸኳይ ስብሰባ ጠርተዋል።

    ከቀረቡት አማራጮች አንዱ ወደ አውሮፓ በሚገባው እና 107.7 ቢሊዮን ዶላር ዋጋ እንዳላቸው በሚገመቱት የአሜሪካ ምርቶች ላይ ታሪፎችን መጣል ነው።

    እስካሁን ድረስ ጥቅም ላይ ውሎ የማያውቀው አውሮፓ ኅብረት "የፀረ-ማስገደድ" እርምጃም (Anti-Coercion Instrument) በሌላ አማራጭነት ቀርቧል።

    ይህ እርምጃ፤ አሜሪካ በአውሮፓ ኅብረት ውስጥ ትርፍ በምታገኝባቸው የዲጂታል አገልግሎቶች፣ የኢንቨስትመንት፣ የባንክ ሥራዎች ወይም የንግድ አገልግሎቶች ላይ ገደብ የሚጥል ነው።

    እንደ ሮይተርስ ዘገባ፤ አሁን ባለው ሁኔታ ከዚህ ይልቅ ታሪፎችን መጣል ሰፊ ድጋፍ ያለው አማራጭ እንደሆነ የአወሮፓ ኅብረት ምንጮች ገልጸዋል።