ሳዑዲ አረቢያ በኢራን ጦርነት ወቅት ምስጢራዊ ጥቃቶችን መፈጸሟን ሮይተርስ ዘገበ
ሳዑዲ አረቢያ በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ወቅት ይፋ ያልሆኑ በርካታ ጥቃቶችን ኢራን ላይ መፈጸሟን ሁለት ምዕራባውያን እና ሁለት የኢራን ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ሮይተርስ ዘገበ።
ሳዑዲ አረቢያ የአየር ድብደባዎቹን የፈጸመችው ለኢራን ጥቃቶች ምላሽ ለመስጠት ነው ተብሏል።
የሳዑዲ ወታደራዊ እርምጃ ከዚህ በፊት ያልተሰማ ሲሆን ኢራን ላይ በቀጥታ ጥቃት መፈጸሟ በይፋ የታወቀው ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
የሳዑዲ አየር ኃይል ጥቃቱን የፈጸመው በመጋቢት ወር መጨረሻ አካባቢ መሆኑ ሁለት የምዕራባውያን ምንጮች ለሮይተርስ ተናግረዋል።
ሳዑዲ ኢራን ለፈጸመቻቸው ጥቃቶች ምላሽ ለመስጠት ድብደባዎቹን ማካሄዷን ጨምረው ተናግረዋል።
ሮይተርስ ሳዑዲ አረቢያ ዒላማ ያደረገቻቸው የኢራን ስፍራዎች የትኞቹ እንደሆኑ ማረጋገጥ አልቻለም።
የሳዑዲ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለሥልጣን ስለጉዳዩ ተጠይቀው በቀጥታ አገራቸው ጥቃት ስለመፈጸሟ ከመናገር ተቆጥበዋል።
ሮይተርስ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ ቢጠይቅም ምላሽ ማግኘት አልቻለም።
ሳዑዲ አረቢያ ከአሜሪካ ጋር ጥብቅ ግንኙነት ያላት ሲሆን ከዚህ ቀደም የዩኤስ ወታደራዊ ከለላ ላይ ትተማመን ነበር።
ነገር ግን 10 ሳምንት በቆየው የኢራን ጦርነት ወቅት ለጥቃቶች የበለጠ ተጋላጭ መሆኗን አሳይቷል።
የሳዑዲ ጥቃት በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት መስፋፋቱን አሳይቷል። አሜሪካ እና እስራኤል የካቲት 21 2018 ዓ.ም. የጀመሩት ጦርነቱ ለሕዝብ ይፋ ባይደረግም በርካታ አገራትን ማሳተፉን አመላክቷል።
ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ኢራን ስድስት የባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ የሚሳዔል እና የድሮኖች ጥቃት ፈጽማለች።
በአሜሪካ ጦር ሠፈሮች፣ በአውሮፕላን ማረፊያዎች፣ በነዳጅ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃቶችን ከመፈጸም አልፋ የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት የዓለም ንግድ እንዲስተጓጎል አድርጋለች።
ሰኞ ዕለት ዎል ስትሪት ጆርናል እንደዘገበው ዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ ቴህራን ላይ ጥቃት ፈጽማለች። የሳዑዲ እና የኤሜሬትስ በጦርነቱ ውስጥ መሳተፍ የግጭቱ ትክክለኛ መልክ የተደበቀ መሆኑን አጋልጧል።
ዩኤኢ ቴህራን ለድርጊቷ ተገቢውን ዋጋ እንድትከፍል የሚል ጠንካራ አቋም ያላት ሲሆን ውስን ዲፕሎማሲያዊ ውይይቶችን ከኢራን ጋር አካሄዳለች።
አንድ የሳዑዲ ከፍተኛ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለሥልጣን ከኢራን ጋር ጦርነቱን የማርገብ ስምምነት ተደርሶ እንደሆን ተጠይቀው ሳይመልሱ ቀርተዋል።
ነገር ግን “ሳዑዲ አረቢያ ለቀጣናው መረጋጋት፣ ደህንነት፣ ብልጽግና እና ለሕዘብ ደህንንት በሚል ውጥረትን በመቀነስ ላይ ያለንን የማያቋረጥ አቋም ላረጋግጥ እችላለሁ” ብለዋል።
ለሮይተርስ መረጃውን የሰጡ የኢራን እና ምዕራባውያን ባለሥልጣናት ሳዑዲ አረቢያ ጥቃት እንደምትፈጸም ቴህራን እንድታውቅ ተደርጓል ብለዋል።