ሰሜን ኮሪያ የኒውክሌር ፕሮግራሟ “በፍጹም ለድርድር” እንደማይቀርብ አስታወቀች
የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂንፒንግ ሰሜን ኮሪያን ከመጎብኘታቸው አንድ ቀን ቀደም ብሎ ፒዮንግያንግ የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ከማምረት ወደኋላ እንደማትል አስታወቀች።
የሰሜን ኮሪያው መሪ እህት ኪም ዮ ጆንግ እሁድ ዕለት ለታተመው የአገሪቱ ጋዜጣ፣ ጎዶንግ ሲንሙን “በኒውክሌር ኃይል ላይ ያለን አቋም ፈጽሞ ለድርድር የማይቀርብ ነው” ብለዋል።
ጆንግ በሰሜን ኮሪያ እንደ ቁልፍ የኮሙኑኬሽን እና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ ይታያሉ።
አክለውም “አገራችን ራሷን ለመከላከል የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ፕሮግራሟን ለማጠናከር የወሰነችው ውሳኔ የመጨረሻ እና የማይቀለበስ ነው" ብለዋል።
ሰሜን ኮሪያ የመጀመርያ የኒውክሌር ሙከራዋን ይፋ ያደረገችው እአአ በ2006 ሲሆን በ2023 ደግሞ በሕገ መንግሥቷ ላይ ራሷን እንደ ኒውኬሌር ኃያላን አገር አስቀምጣለች።
በዚህ ሳምንት መጀመርያ ላይ ዩራኒየምን ጦር መሣሪያ ለማምረት በሚያስችል ደረጃ የሚያብላላ አዲስ ተቋም ይፋ አድርጋለች።
ኪም ስፍራውን የጎበኙ ሲሆን የአገሪቱን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ብዛትት “በከፍተኛ ሁኔታ” የሚጨምር እንደሚሆን ተናግረዋል።
ተንታኞች አዲሱ የኒውክሌር ተቋም ኪም እና ዢ በሚኖራቸው ድርድር ላይ አቅም ይፈጥራል ሲሉ ተናግረዋል።
ኪም ሌላ የጦር መሣሪያ ማምረቻ ጎብኝተው የአገሪቱ የሚሳዔል ማምረት አቅም በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት በእጥፍ እንዲያድግ ማዘዛቸውን የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።