የጋዛ ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ሊያበቃ ቢቃረብም ለማራዘም ጥረት እየተደረገ ነው
ዛሬ ሰኞ በእስራኤል እና በሐማስ መካከል ለአራት ቀናት የተደረሰው ጦርነት ጋብ የማድረግ ስምምነት የሚያበቃበት ዕለት ቢሆንም ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ተኩስ አቁሙ እንዲራዘም ግፊት እያደረገ ነው።
ባለፉት ሦስት ቀናት ሐማስ ከእስራኤል አግቶ ከወሰዳቸው ሰዎች መካከል የለቀቀ ሲሆን እስራኤል ደግሞ በእስር ቤቶቿ ውስጥ የነበሩ በርካታ ፍልስጤማውያንን ፈትታለች።
ከዚህም ባሻገር ለሳምንታት በእስራኤል ጥቃት ምክንያት በመሠረታዊ አቅርቦቶች እጦት ሲሰቃዩ ለቆዩት የጋዛ ነዋሪዎች ሰብዓዊ እርዳታ እና ነዳጅ መግባት ችሏል።
ይህ ለቀናት የቆየው ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ዛሬ ሌሊት ከማብቃቱ በፊት እንዲራዘም ጥረት እየተደረገ ነው። የኔቶው ዋና ፀሐፊ የንስ ስቶልተንበርግ እና የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ፖሊሲ ኃላፊ ጆሴፍ ቦሬል ጥሪ ካቀረቡት መካከል ናቸው።
የመጀመሪያው ስምምነት እንዲደረስ ወሳኝ ሚና የነበራት ኳታር፣ ግብፅ፣ አሜሪካ፣ የአውሮፓ ኅብረት እና ስፔን፤ እስራኤል እና ሐማስ ጋዛ ውስጥ የደረሱት ጊዜያዊ ተኩስ አቁሙ እንዲራዘም ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን የፍልስጤም ብሔራዊ ባለሥልጣን ሪያድ አል-ማሊኪ ተናግረዋል።
የግብፅ የደኅንነት ምንጮች ለሮይተርስ ዜና ወኪል እንደተናገሩት ጦርነት የቆመበት ፋታ በቀናት ለማራዘም የሚደረገው ጥረት ወደ ስምምነት እየተጠጋ መሆኑን አመልክተዋል።
ሐማስ የተኩስ አቁሙ እንዲራዘም እና ተጨማሪ ታጋቾችን ለመልቀቅ ፍላጎት እንዳለው ያሳወቀ ሲሆን፣ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁም ስምምነቱ እንዲራዘም የማድረግ ዕድል እንዳለ ገልጸው፣ ነገር ግን ከስምምነቱ ማብቃት በኋላ በጋዛ ውስጥ ሠራዊታቸው የሚያካሂደው ዘመቻ በሙሉ ኃይል እንደሚጀመር ተናግረዋል።