የቲክቶክ ይግባኝ ውድቅ መደረጉን ተከትሎ ከአሜሪካ ሊታገድ ነው

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ቲክቶክ ከ 2025 መጀመሪያ ጀምሮ በአሜሪካ ውስጥ እንዲታገድ አልያም እንዲሸጥ የሚለውን ሕግ እንዲቀለበስ ያቀረበው የይግባኝ አቤቱታ ውድቅ ተደረገ።
የማህበራዊ ሚዲያው ኩባንያው ለፌደራል ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ሕጉ ኢ ሕገመንግሥታዊ ነው፤ ምክንያቱም በ170 ሚሊዮን አሜሪካውያን ተጠቃሚዎቼ የመናገር ነፃነት ላይ የተጣለ "አስደንጋጭ" ተጽእኖ ነው በሚል ያቀረበው መከራከርያ ተቀባይነት ያገኛል ሲል ተስፋ አድርጎ ነበር ።
ነገር ግን ፍርድ ቤቱ "በኮንግረሱ እና በተከታታይ ፕሬዚዳንቶች የተደረገው ሰፊ የሁለትዮሽ እርምጃ መጨረሻ ነው" ያለውን ሕግ አጽንቷል።
ቲክ ቶክ ጉዳዩን አሜሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት እወስዳለሁ ብሏል።
አሜሪካ የቲክ ቶክ ባለቤቶች ምንም እንኳ ጉዳዩን ቢያስተባብሉም፣ ከቻይናው ኩባንያ ባይቴዳንስ ጋር ግንኙነት አላቸው በሚል እንዲሸጥ ወይም እንዲታገድ ትፈልጋለች።
ፍርድ ቤቱ ሕጉ "የውጭ ባላጋራ ቁጥጥርን ብቻ ለመቆጣጠር በጥንቃቄ የተቀረጸ እና በቻይና የተጋረጠውን የብሄራዊ ደህንነት ስጋትን ለመከላከል የተደረገው ሰፊ ጥረት አካል ነው" ሲል ውሳኔ አስተላልፏል።
ቲክ ቶክ ግን ይህ ውሳኔ የሚያደርገው ሕጋዊ ትግል መጨረሻ እንዳልሆነ ተናግሯል።
የቲክ ቶክ ቃል አቀባይ በሰጡት መግለጫ "ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአሜሪካውያንን የመናገር መብት የመጠበቅ ታሪካዊ ሪከርድ አለው፣ እናም በዚህ አስፈላጊ ሕገ-መንግስታዊ ጉዳይ ላይ ይህን ያደርጋሉ ብለን እንጠብቃለን" ብለዋል።
ሕጉ "በተሳሳቱ እና መላምታዊ መረጃዎች" ላይ የተመሰረተ መሆኑን እና እገዳው የአሜሪካ ዜጎችን ሳንሱር እንደሚያደርግም ጨምረው ተናግረዋል።
በ2024 የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የዶናልድ ትራምፕ ማሸነፍ ቲክቶክ በአሜሪካ ያለው እስትንፋስ እንዲቀጥል ሊያደርግ ይችላል።
እ.ኤ.አ. በ2020 የመጀመሪያ የስልጣን ዘመናቸው ቲክ ቶክን ለማገድ ያደረጉት ሙከራ ባይሳካላቸውም በሕዳር ወር ምርጫ ላይ ግን የቲክ ቶክ እገዳ ተግባራዊ እንዲሆን እንደማይፈቅዱ ተናግረዋል።
ትራምፕ ሕጉ ቲክቶክ መታገድ አልያም መሸጥ አለበት ካለው ቀን ማግስት፣ ጥር 12 2017 ዓ.ም. ላይ ሥልጣናቸውን ይረከባሉ።
ሆኖም ከምርጫው በፊት የገቡትን ቃል ተግባራዊ ማድረግ አለማድረጋቸው ወደፊት የሚታይ ይሆናል።
የኮርኔል ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ጄምስ ግሪምልማን እንደተናገሩት ተመራጩ ፕሬዝዳንት "ቲክቶክን በአሜሪካ ገበያ ለማቆየት አስቸጋሪውን ውሳኔ ይወስናሉ" ብለዋል ።
"በአሜሪካ ኮንግረስ ውስጥ ያለው ፀረ-ቻይና ስሜት በጣም ጠንካራ ነው፣ ስለዚህ በሁለቱም ወገኖች ውስጥ ቲክ ቶክ ከአሜሪካ ገበያ እንዲገደብ የሚፈልጉ ጠንካራ አካላት አሉ" ሲል ለቢቢሲ ተናግረዋል።
የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ቲክቶክን የሚጠቀሙ እና የመተግበሪያው ተቀናቃኞች በቅርበት የሚከታተሉት ነበር።
የአነስተኛ ንግዶች ተሟጋች እና የቲክቶክ ተጠቃሚዋ ቲፋኒ ሲንቺ በአርብ ዕለቱ ውሳኔ "አልደነገጥኩም" ብላለች።
አክላም ቲክቶኳን ዘግታ እንደ ኢንስታግራም ያሉ ተፎካካሪዎች እንደማትቀይር ለቢቢሲ ተናግራለች።
እርሷ ይህንን ትበል እንጂ ሌሎች መተግበርያዎች ለድህረ-ቲክቶክ የማህበራዊ ሚዲያ መልክዓ ምድር ራሳቸውን እያዘገጃጁ ነው።
የፌስቡክ፣ የኢንስታግራም፣ ዋትስአፕ እና ትሬድስ ባለቤት የሆነው ሜታ በራሱ መተግበርያዎች ውስጥ የቲክ ቶክን አጫጭር ቪዲዮዎች የሚተካ ለመፍጠር ሞክሯል።
እናም በአሜሪካ የቲክቶክ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ጥያቄ ውስጥ በወደቀበት በዚህ ጊዜ ተጠቃሚዎች ከቲክ ቶክ ጋር አመሳስለው የወደዷቸውን ለውጦችን አድርጓል ።
የኤሌክትሮኒክስ ማርኬቲንግ ዋና ተንታኝ የሆኑት ጃስሚን ኤንበርግ የቲክቶክ ይግባኝ በጠቅላይ ፍርድ ቤት ውድቅ ከተደረገ እና እገዳው ተግባራዊ ከሆነ ገበያው ላይ "ትልቅ ግርግር" እንደሚኖር ተናግረዋል።
"ይህ ለሜታ፣ ዩቲዩብ እና ስናፕ የሚጠቅም ቢሆንም፣ በመተግበሪያው ላይ ኑሯቸውን ለመሰረቱ ይዘት ፈጣሪዎች እና አነስተኛ ንግዶችን የሚጎዳ ነው" ብለዋል።
ነገር ግን ቲክቶክ በቀላሉ አይተካም የሚሉት ደግሞ የኤፒስትሮፊ ካፒታል ምርምር ዋና የገበያ ስትራቴጂስት ኮሪ ጆንሰን ናቸው።
ጆንሰን "እንዲህ ያለውን ውስብስብ የሰው ሰራሽ አስተውህሎት እና ትልቅ የዳታ ቅንብርን በቲክቶክ ልክ ማንቀሳቀስ ግዙፍ እና ውድ የሆነ የቴክኒክ መሠረተ ልማት ያስፈልገዋል" ባይ ናቸው።












