ጣልያን፡ ድልድይ ላይ ቡና ያፈሉት ቱሪስቶች ተቀጡ

ድልድይ ላይ ቡና ያፈሉት ቱሪስቶች ተቀጡ

የፎቶው ባለመብት, Comune Venezia

ታትሟል

ጣልያን፣ ቬነስ የሚገኘው ሪላቶ ድልድይ ላይ ቡና ሲያፈሉ እጅ ከፍንጅ የተያዙ ሁለት ጀርመናውያን ቱሪስቶች 950 ዩሮ (28 ሺህ 500 ብር ገደማ) ተቀጡ።

የ32 እና 35 ዓመቶቹ ጀርመናውያን ቱሪስቶች በጀርባ ቦርሳቸው በሸከፉት ማሽን ቡና ያፈሉት ሪላቶ ድልድይ ደረጃ ላይ ነበር። በአካባቢው ይዘዋወሩ የነበሩ ፖሊሶች ከበርሊን ወደ ቬነስ ያቀኑት ቱሪስቶች ድልድዩ ላይ ቡና ሲያፈሉ ይዘዋቸዋል።

ቬነስ ከተማ ውስጥ ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው አካባቢዎች መመገብ በሕግ የተከለከለ ነው።

የከተማዋ ከንቲባ ሉይግ ብሩጋኖ "በከተማችን ውስጥ እንዳሻቸው መሆን የሚፈልጉ ሰዎች ቬነስ መከበር እንዳለባት መገንዘብ አለባቸው" ብለዋል።

ፖሊስ የቀጣቸው ጀርመናውያን ማንነት ለአገራቸው ኤምባሲ ይፋ እንደሚደረግ ተገልጿል።

በየዓመቱ ወደ 30 ሚሊዮን ቱሪስቶች ከተማዋን ይጎበኛሉ። ከተማዋን መጎብኘት የሚፈልጉ ቱሪስቶች 10 ዩሮ እንዲከፍሉ የሚያደርግ ሕግ ከወራት በፊት መጽደቁ ይታወሳል።