የእስልምና ምክር ቤት የኮሮናቫይረስን ለመከላከል መደረግ ያለበትን ለእምነቱ ተከታዮች ይፋ አደረገ
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የዑለማዎች ምክር ቤት የኮሮናቫይረስን ለመከላከል የዕምነቱን ሕግጋት መሰረት ያደረገ ውሳኔ (ፈትዋ) ማስተላለፉን አስታወቀ።
የዑለማዎች ምክር ቤቱ ባወጣው መግለጫ ላይ እንዳመለከተው የኮሮናቫይረስ ስርጭት አስጊ በመሆኑ ከጁምዓና ከጀመዓ ሶላት መቅረት በሸሪዓው የተፈቀደ በመሆኑ የዕምነቱ ተከታዮች "በቤታቸው ውስጥ መስገድ ይቻላሉ" ብሏል።
በተጨማሪም በኮሮናቫይረስ የተያዘ ወይም የተጠረጠረ ማንኛውም ሰው ለጁምዓም ሆነ ለጀመዓ ሶላት እንዲሁም ለሐይማኖታዊ ትምህርት ወደ መስጂድም ሆነ ሕዝብ ወደሚሰበሰብበት ቦታ መምጣት የተከለከለ መሆኑን አመልክቷል።
ምክር ቤቱ ሁሉም "ወደ አላህ እንዲመለስና ምህረት እንዲለምን" ጥሪ ያቀረበ ሲሆን፤ የጤና ጥበቃ ተቋማትና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት የሚሰጡትን ምክርና መመሪያ በመቀበል በሥራ ላይ ማዋል የሁሉም ሐይማኖታዊ ግዴታ እንደሆነ ገልጿል።